July 10, 2023 – BBC Amharic

ቻይና መዋለ ሕጻናት

ከ 3 ሰአት በፊት

በቻይናዋ ደቡብ ምስራቅ ግዛት ጓንግዶንግ በተፈጸም የስለት ጥቃት ስድስት ሰዎች ተገደሉ።

ከሟቾቹ በተጨማሪም አንድ ሰው መቁሰሉንም ፖሊስ ለቢቢሲ ተናግሯል።

ከጥቃቱ ጋር በተያያዘ አንድ የ25 ዓመት ወጣትን ፖሊስ ማሰሩን ገልጿል።

በጥቃቱ ሕይወታቸው ያለፈው አንድ አስተማሪ፣ ሁለት ወላጆች እና ሦስቱ ደግሞ ተማሪዎች ናቸው ተብሏል።

ጥቃቱ ዛሬ [ሰኞ] ማለዳ ላይ የተፈጸመ ሲሆን ፖሊስ ጥቃት አድራሹን በደቂቃዎች ልዩነተ በቁጥጥር ሥር አውሏል።

ፖሊስ ጥቃቱ “ሆን ተብሎ የተፈጸመ ነው” ብሏል።

በቻይና እንደዚህ አይነት ጥቃቶች በብዛት የሚፈጸሙ አልነበሩም። በዚህ ዓመት ግን በተለይ የስለት ጥቃት በትምህርት ቤቶች ጨምሮ በተለያዩ የአገሪቱ ግዛቶች በብዛት ተከስቷል።

ባለፈው ዓመት ነሐሴ ወር አንድ ግለሰብ መዋዕለ ሕጻናት ግቢ ውስጥ በስለት በፈጸመው ጥቃት ሦስት ሰዎች ሲገደሉ፣ ስድስት ሰዎች ደግሞ ቆስለው ነበር።

በፈረንጆቹ 2021 በተመሳሳይ ጥቃት ቤይሉ በተባለች የቻይና ከተማ 2 ሕጻናት ተገድለው 16 ሰዎች ቆስለው ነበር።