BBC Amharic 

የአማራ ሚሊሻ አባላት ባለፈው ዓመት

5 ነሐሴ 2023, 10:10 EAT

በአማራ ክልል በተለያዩ አካባቢዎች በመከላከያ እና በፋኖ ታጣቂዎች መካከል ሲደረጉ የነበሩ ግጭቶች ተባብሰው መቀጠላቸውን ተከትሎ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ተደንግጓል።

አርብ ሐምሌ 28/ 2015 ዓ.ም. በሚኒስትሮች ምክር የተደነገገው የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ የሕዝብን ሰላም እና ደኅንነት ለማስጠበቅ እንዲሁም ሕግ እና ሥርዓት ለማስከበር ያለመ መሆኑ ተገልጿል።

በክልሉ በትጥቅ የተደገፈ ሕገወጥ እንቅስቃሴ በመደበኛ የሕግ ማስከበር ሥርዓት ለመቆጣጠር ወደማይቻልበት ደረጃ የተሸጋገረ በመሆኑ የአስቸኳይ ጊዜ ማወጅ አስፈላጊ መሆኑም ነው የተገለጸው።

በክልሉ የታዩት ግጭቶች የክልሉን ነዋሪ አጠቃላይ የኢኮኖሚ እና የማኅበራዊ እንቅስቃሴ በከፍተኛ ደረጃ ያወኩ እንዲሁም ሕገ መንግሥታዊ ሥርዓቱን አደጋ ላይ የጣሉ እንደሆኑ አዋጁ በመግቢያው ላይ አትቷል።

የክልል ልዩ ኃይሎችን መልሶ ለማዋቀር ከተያዘው ዕቅድ ጋር ተያይዞ የተነሳው ግጭት ከሰሞኑ ተባብሶ በክልሉ የኢንተርኔት አገልግሎት ተቋርጧል፣ ትራንስፖርት ተስተጓጉሏል እንዲሁም እንቅስቃሴዎች ተገድበዋል።

ከሐምሌ አጋማሽ ጀምሮ በርካታ የክልሉ አካባቢዎች በግጭት ላይ መሆናቸውን የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን (ኢሰመኮ) የጠቀሰ ሲሆን፣ በአንዳንድ አካባቢዎች በሲቪል ነዋሪዎች ላይ ጥቃት መፈጸሙን እና የሰላማዊ ሰዎች እና ንብረት ላይ ጉዳት መድረሱንም አመልክቷል።

በአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ወቅትም ሰብዓዊ መብቶች መከበር ቅድሚያ ሊሰጠው እንደሚገባ ኢሰመኮ አስታውሷል።

“የሕዝብን ሰላም እና ደኅንነት ለማስጠበቅ የወጣ የሚኒስትሮች ምክር ቤት የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ” ተብሎ አርብ ዕለት የወጣው ድንጋጌ ዝርዝር አምስት ገጾችን ይዟል።

ለመሆኑ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ምን አካቷል?

አዋጁ በአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግሥት አስተዳደር እንዲሁም በክልሉ አስተዳደር የሕዝብን ሰላም እና ፀጥታ ለማስከበር እንደወጣ ያትታል።

ሆኖም በክልሉ ወይም በአገር አቀፍ ደረጃ ያለውን የፀጥታ ችግር የሚያባብስ ማንኛውንም እንቅስቃሴ ወይም ሁኔታን በሚመለከት እንደ አስፈላጊነቱ በየትኛውም የአገሪቱ አካባቢ ተፈጸሚነት እንደሚኖረውም አካቷል።

የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁን የሚያስፈጽም በብሔራዊ መረጃና ደኅንነት አገልግሎት ዳይሬክተር ጄኔራል የሚመራ የአስቸኳይ ጊዜ ጠቅላይ መምሪያ ዕዝ ተቋቁሟል።

የጠቅላይ መምሪያ ዕዙ አባላት፣ መዋቅር እና አደረጃጀት በጠቅላይ ሚኒስትሩ የሚወሰን ሲሆን፣ ተጠሪነቱም ለጠቅላይ ሚኒስትሩ እንደሚሆን ተጠቅሷል።

በአስቸኳይ አዋጁ የተከለከሉ ተግባራት እና ግዴታዎች

በአስቸኳይ ጊዜ የሚወሰዱ እርምጃዎች

የአስቸኳይ ጊዜ ጠቅላይ መምሪያ ዕዙ ይህን አዋጅ ለማሳካት አስፈላጊ ነው ብሎ ሲያምን የሚያከናውናቸው እርምጃዎች ተዘርዝረዋል።

ተመጣጣኝ ኃይል ስለመጠቀም እና የማይታገዱ መብቶች

የወንጀል ተጠያቂነት

በአማራ ክልል በታወጀው በዚህ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ አፈጻጸም ወቅት የሚፈጸሙ የአዋጁ ጥሰቶች አስከ አስር ዓመታት የሚደርስ እስርን ሊያስከትሉ እንደሚችሉ ተደንግጓል።

የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ በሚኒስትሮች ምክር ቤት ከታወጀበት ጊዜ ጀምሮ ለስድስት ወራት የሚጸና ሲሆን፣ የስድስት ወር ጊዜ ገደቡ ከመጠናቀቁ በፊት የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የአዋጁ ተፈፀሚነት ቀሪ የሚሆንበትን ጊዜ ሊወስን እንደሚችልም ተቀምጧል።