ግርማ ካሳ

 · ከአዲስ አበባ ማኅበራዊ ንቅናቄ (አማን) የተሰጠ መግለጫ

የአዲስ አበባ ሕዝብ ባለው የአንድነት እሳቤ እና በነበረው የረዥም ጊዜ ነጻነት ለማግኘት ሲያደርግ በነበረው ትግል ምክንያት በገዢዎች ጥርስ ውስጥ እንዲገባ አድርጎታል፡፡

የኢሕአዴግ መንግሥት ምርጫ 97 ተከትሎ ባጋጠመው ሽንፈት በከፍተኛ ቂም በቀል ተነስቶ በከተማዋ ሕዝብ ላይ የሞራልና የፖለቲካ ሥነ ልቦና ስብራት እንዲደርስበት ሆን ተብሎ ተሰርቶበታል፡፡

የአዲስ አበባ ሕዝብ መሬት ጠበበኝ ፣ ኑሮ ተወደደብኝ ፣ ከሌላ ክልል ሌሎች መጡብኝ ሳይል ሁሉንም አቻችሎ የሚኖር የውጭ ሀገር ዜጎችን ጭምር ሳይቀር ከራሱ በላይ ማስተናገድን፣ በፍቅር መቀበልን የሚያውቅ የአብሮነት መምህር የሆነ መተኪያ ያልተገኘለት ሕዝብ ነው።

የአዲስ አበባ ሕዝብ መለያየት ሳይኖርበት አንድነትን እና አብሮነቱን ሳይሸራረፍ ጠብቆ የኖረ ፣ ነጻነቱን ለድርድር ያላቀረበ ፣ ቢከፋውም ቢደላውም ሰላምን በማስቀደም የኢትዮጵያ መተሳሰሪያ የአብሮነት ሰንሰለት አስተሳሳሪ ሆኖ የኖረ ፣ ለወደፊትም የሚኖር ኩሩ ሕዝብ ነው፡

የአዲስ አበባ ሕዝብ ሁሉንም አሜን ብሎ በመቀበሉ በጎጥ መቧደን አለመቻሉ ዘመን ባገነናቸው ገዢዎች እንደ ኃጢአት ተቆጥሮበት ግፍና መከራን እየተቀበለ ይገኛል።

ኢሕአዴግ ተፈረካክሶ ሥልጣኑ ከሕወሓት እጅ ሲወጣ በወቅቱ የለውጥ ሐዋርያ ” ነን ብለው የመጡት ቡድኖች በጠ / ሚሩ አጋፋሪነት የአዲስ አበባን ሕዝብ ውለታ ረስተው የነበረውን በማሳጣት ከድጡ ወደ ማጡ ከተውታል፡፡

የአዲስ አበቤን ማንነት ከሥር መሠረቱ ለማጥፋት ሀሰትን መሠረት ባደረገ የታሪክና የፖለቲካ ትርክት የማጥፋት ሥራ በገዢው መንግሥት ሆን ተብሎ እየተሠራበት ይገኛል።

እንደማሳያ፡- በአዲስ አበባ የሚገኙ ነባር መንደሮችን እያፈራረሱ ፣ የአዲስ አበባ ሕዝብን መውጪያ መግቢያ ለማሳጣት እና አስጨንቆ ለመኖር ዙሪያዋን ሸገር ሲቲ በሚል የዳቦ ስም የከተማዋን መሬት እና የጋራ መኖሪያ ቤቶችን ጭምር ወደ ኦሮሚያ ክልል እያካለሉ ፣ ኅብረተሰቡ አንገቱን ደፍቶ እንዲኖር በኑሮ ውድነት እና በሥራ አጥነት ፋታ እንዳያገኝ እያደረጉት ፣ በእስርና በተለያዩ ስልቶች በማማረር ከተማውን ለቆ እንዲወጣ የማድረግ ከፍተኛ እቅድ ይዘው እየሠሩበት ይገኛል፡፡

የብልጽግና መንግሥት ዋነኛ ጠላቶቼ ብሎ በመጀመሪያ ረድፍ ከያዛቸው እና በቀይ ካሰመረባቸው አንዱና ዋነኛው የአዲስ አበባ ከተማ ነዋሪ እና የከተማዋ ወጣቱ ክፍል ግንባር ቀደም ናቸው፡፡

የአዲስ አበባ ሕዝብ እና የአንድነት አስተሳሰብ ከሚጠፋ ለከተማዋ ስጋት የሆነው አካል መታገል ይገባል ብለን ሳንወድ በግድ ተገደን እኛ አዲስ አበቤዎች ለከፍተኛ ትግል ተሰባስበናል።

ይህ ትግል ህልውናችንን ለማስጠበቅ የሚደረግ ትግል ነው።

ይህ ትግል በሕይወት ለመቆየት የሚደረግ ትግል ነው።

ይህ ትግል የአዲስ አበባን ሕዝብ ፖለቲካዊና ኢኮኖሚያዊ መብት ለማስጠበቅ የሚደረግ ትግል ነው።

ይህ ትግል ነጋችንን የምንወስንበት ትግል ነው።ይህ ትግል ቀጣይ እጣ ፋንታችንን ለመወስን የተረጋገጠ ሰላምን ለማምጣት የሚደረግ ትግል ነው።

ይሄን ትግል ከግብ የምናደርሰው ብልፅግና በሚሰጠን ተስፋ ሳይሆን በተባበረ ክንዳችን ብቻ ነው፡፡

መላው የአዲስ አበባ ሕዝብ እና ኢትዮጵያውያን ሁላችሁም ይህን ንቅናቄ እንድትቀላቀሉና እንድታግዙ ጥሪያችንን እናስተላልፋለን፡፡

መላው የመዲናችን የአዲስ አበባ ነዋሪ ይህን ሕዝባዊ የሕልውና ትግል ከአዲስ አበባ ማኅበራዊ ንቅናቄ ( አማን ) ጋር በመሆን በጽኑ ለመታገል ተዘጋጅታችሁ እንድጠብቁን ጥሪያችንን እናስተላልፋለን።

የአዲስ አበባ ማኅበራዊ ንቅናቄ ( አማን )