እናት ፓርቲ በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ላይ የንብረት ወይም የጣሪያ ግድግዳ ግብርን አስመልክቶ ለመሠረተው ክስ የፌደራሉ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ረቡዕ ጥቅምት 14 ከቀትር በኋላ ብይን እንደሚሰጥ ገልጧል።
ፓርቲው ዛሬ ባሠራጨው መረጃ፣ ለክሱ ብይኑን የሚሰጠው የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ አስተዳደር ችሎት እንደኾነ ገልጧል፡፡
ክሱ የአዲስ አበባ ከተማ ሕዝብ እንዲኹም መላው የኢትዮጵያ ሕዝብ ጉዳይ መኾኑን የጠቀሰው ፓርቲው፣ የመገናኛ ብዙኀንና ሌሎች የሚመለከታቸው አካላት በፍርድ ቤቱ የሚደረገውን ክርክርና አጠቃላይ ሂደቱን ተከታትለው ለሕዝቡ እንዲያሳውቁ ጠይቋል፡፡
ፓርቲው በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ላይ ባለፈው ዓመት ሐምሌ የመሠረተው ክስ፣ የንብረት ወይም የጣሪያ ግብሩ ሕጋዊ መሠረት እንደሌለውና ፍርድ ቤቱም ውሳኔ እስኪሰጥበት ድረስ የግብር መመሪያውን እንዲያግደው የሚጠይቅ ነበር።
