19 ሺህ የአፍሪካ ህብረት ጦር በቀጣዩ ዓመት ከሶማሊያ እንሚወጡ ይጠበቃል (ፎቶ ከፋይል)
የምስሉ መግለጫ,19 ሺህ የአፍሪካ ህብረት ጦር በቀጣዩ ዓመት ከሶማሊያ እንሚወጡ ይጠበቃል (ፎቶ ከፋይል)

ከ 5 ሰአት በፊት

ባለፈው ሰኔ ወር በሶማሊያ በሚገኘው የአፍሪካ ህብረት ወታደራዊ ሰፈር ላይ አልሸባብ ጥቃት በፈጸመበት ወቅት የሸሹ ሁለት የኡጋንዳ የጦር መኮንኖች ጥፋተኝነታቸው በወታደራዊ ፍርድ ቤት ከተረጋገጠ በኋላ ከስራ ተሰናብተዋል።

የሻለቃ ማዕረግ ያላቸው ዛዶክ አቦርና ጆን ኦሉካ አልሸባብ ሞቃዲሾ ደቡባዊ ክፍል በሚገኝ የጦር ሰፈር ላይ ጥቃት ማድረስ ሲጀምር ‘እግሬ አውጪኝ’ ብለው ሸሽተዋል።

በዚያ ጥቃት 50 የኡጋንዳ ወታደሮች ተገድለዋል።

ኡጋንዳ በሶማሊያ ከአልቃይዳ ጋር ግንኙነት ያለውን አልሸባብን ለመውጋት የተቋቋመው የአፍሪካ ህብረት ኃይል ውስጥ አባል ነች።

የጦር መኮንኖቹ የሸሹበት ጥቃት ባለፈው ዓመት ከተጀመረውና አልሸባብ ላይ ከተከፈተው ዘመቻ በኋላ በአፍሪካ ህብረት ወታደራዊ ሰፈር ላይ የተፈጸመ አስከፊው ነው።

ክስተቱን ተከትሎ የኡጋንዳው ፕሬዝዳንት ዮዌሬ ሙሴቪኒ ወታደሮቻቸው የሰጡን ምላሽ ተችተዋል።

የጦር መኮንኖቹ ጥቃት እንደሚፈጸም ቀድሞ የተነገራቸው ቢሆንም ጥቃቱን ለመመከላከል አለመቻላቸውን የኡጋንዳ የጦር ፍርድ ቤት ጠቅሷል።

የአልሸባብ ታጣቂዎች ወታደራዊ ሰፈሩን ማጥቃት ሲጀምር የጦር መኮንኖቹ ወታደሮቻቸውን አስተባብረው ጥቃቱን ከመመከት ይልቅ ወደ ሌላ የጦር ሰፈር ሮጦ መሸሽን መርጠዋል።

በዚህም ሳቢያ ሁለቱም መኮንኖች ከስራ ተባረዋል።

በተጨማሪም አራት ማዕረግ የሌላቸው ወታደሮች ወታደራዊ ቁሶችን መጠበቅ አልቻሉም በሚል ጥፋተኛ ተብለዋል።

እንደ አውሮፓውያኑ በ2007፣ 19 ሺህ ጠንካራ የተባለ የአፍሪካ ህብረት ጦር ወደ ሶማሊያ የተላከ ሲሆን አልሽባብ ከተለያዩ ከተሞች እንዲወጣ ረድቷል።

ይህ ጦር ኃላፊነቱን ለሶማሊያ የጸጥታ ኃይሎች አስረክቦ በሚቀጥለው ዓመት ከሶማሊያ ይወጣል ተብሎ ታቅዶ ነበር።

ሆኖም አልሸባብ ላይ የሚፈጽመው ዘመቻ የተቋረጠ ሲሆን አልሸባብ በርካታ ገጠራማ አካባቢዎችን እየተቆጣጠረ ይገኛል።