December 9, 2023 

ኢሰመጉ፣ በኦሮሚያ ክልል በታጣቂዎች በሚፈጸሙ “ዘርፈ ብዙ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶች” ሳቢያ ሕዝቡ ለአካላዊ፣ ስነ ልቦናዊና ኢኮኖሚያዊ ቀውስ ተጋልጧል ሲል አዲስ ባወጣው መግለጫ አስታውቋል።

ኢሰመጉ፣ የኦሮሚያ ክልል ጸጥታ አካላት ወንጀል ሠርቶ ተጠያቂ ያለመኾን ባህል እንዲቀር ወንጀለኞች ለሕግ የሚቀርቡበትን ሥርዓት እንዲዘረጉ አሳስቧል።

የክልሉ መንግሥት በቅርቡ በአርሲና ቄለም ወለጋ ዞኖች በበርካታ ንጹሃን ላይ ግድያ የፈጸሙና የአካል ጉዳት ያደረሱ አካላትን በሕግ ተጠያቂ እንዲያደርግም ኢሰመጉ ጠይቋል።

በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል አማሮ ኬሌ ወረዳም፣ ታጣቂዎች ኅዳር 17 ቀን በኹለት ሰላማዊ ሰዎች ላይ በፈጸሙት ጥቃት፣ አንዱን መግደላቸውንና ሌላኛው በሽሽት ላይ ሳለ የመንግሥት ጸጥታ ኃይሎች አግኝተው ደብድበው እንደገደሉት መረዳቱን ኢሰመጉ ጨምሮ ገልጧል።