
በመንግሥት መዋቅር ውስጥ ያለው የኮንትሮባንድ ተሳትፎ ጥብቅ መፍትሔ ይፈልጋል ተባለ
ቀን:
በሶማሌ ክልል በሁሉም ደረጃ ያሉ የመንግሥት መዋቅሮች በኮንትሮባንድ የሚያደርጉት ተሳትፎ፣ ጥብቅ የሆነ መፍትሔ እንደሚያስፈልገው የጉምሩክ ኮሚሽን አስታወቀ፡፡በተለያዩ ክልሎች የተቋቋሙ ሕገወጥ ኬላዎች በፌዴራል መንግሥት አቅጣጫ መሠረት እንዲነሱ ቢደረግም፣ በምትካቸው መንገድ ላይ ተዘርግተው የነበሩ ገመዶች ወይም እንጨቶች ተነስተው፣ በሚቆሙ ፖሊሶች መተካታቸውን የተናገሩት የጉምሩክ ኮሚሽነሩ አቶ ደበሌ ቀበታ ናቸው፡፡ ይሁን እንጂ ኬላ ሆነው የሚቀርቡ ከሆነ ጥላ ሥር ሆነው አሁንም ተሽከርካሪ እያስቆሙ መሆኑን ገልጸዋል፡፡ኮሚሽነሩ ይህንን የገለጹት የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የፕላን፣ በጀትና ፋይናንስ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ፣ የገቢዎች ሚኒስቴርንና የጉምሩክ ኮሚሽንን የ2016 በጀት ዓመት የመጀመሪያ ሩብ ዓመት ዕቅድ አፈጻጸም ሪፖርት፣ ረቡዕ ኅዳር 26 ቀን 2016 ዓ.ም. ሲገመግም ነው፡፡ኬላ ከመነሳቱ በፊት መንገድ ይጠብቅ የነበረ አካል፣ ኬላው ሲነሳበት ሕገወጥ አዘዋዋሪውን ከድንበር እስኪወጣ ድረስ በረሃውን አሻግሮ የመሸኘት ሥራ ላይ መሰማራቱን ኮሚሽነሩ አስረድተዋል፡፡የኮታ ንግድ በሚል ሽፋን የኮንትሮባንድ ነጋዴዎችን የሚያግዙ አካላት ስለመኖራቸው የተናገሩት አቶ ደበሌ፣ ለአብነት በአንድ ክልል ውስጥ የሌለ የጫት ተጠቃሚ ቁጥር ይጠቀስና ለዚህ አካባቢ ይህን ያህል ጫት ያስፈልገዋል በሚል፣ ትክክል ባልሆነ መረጃ ደብዳቤ የሚጽፉ የንግድ ቢሮዎች እንዳሉ አስረድተዋል፡፡የሶማሌ ክልል ብዙ የተበላሹ ነገሮች አሉበት ያሉት ኮሚሽነሩ፣ ከክልል ጀምሮ የዞንና የወረዳ አመራሮች ድረስ በአንድም ይሁን በሌላ መንገድ ከሕገወጥ አዘዋዋሪዎች ጋር እጅና ጓንት ሆነው እየሠሩ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡ ሕገወጥ አዘዋዋሪዎች ዕድል ገጥሟቸው ከተያዙ ደግሞ፣ እነዚሁ የክልሉ መንግሥት አካላት በሆነ መንገድ ለማስለቀቅ ይረባረባሉ ብለዋል፡፡ አንዳንድ ክልሎች ምን አገባችሁ እንደሚሉም ለቋሚ ኮሚቴው ገልጸዋል፡፡ከኮንትሮባንዱ አዘዋዋሪዎች ጋር እጅና ጓንት ሆኖ የሚሠራ አመራር በሁሉም ደረጃ በተለይ በፀጥታ ኃይል፣ በጉምሩክ ኮሚሽን፣ በፍትሕ አካላት፣ በፌዴራል ፖሊስ ውስጥና በሌሎችም ተቋማት ከላይ እስከ ታች ባሉ መዋቅሮች እንዳሉ ገልጸው፣ የሶማሌ ክልል ችግር ግልጽ የሆነ መፍትሔ ይፈልጋል ብለዋል፡፡ ‹‹የጫት ንግድ ከዚህ ችግር ሊላቀቅ አልቻለም፤›› ብለው የተናገሩት ኮሚሽነሩ፣ ኢትዮጵያ ውስጥ ጫት ወደ ውጭ የሚልኩ አካላት በመዳረሻውም ተቀባዮችም ራሳቸው ስለመሆናቸው አስረድተዋል፡፡የገቢዎች ሚኒስቴር በ2016 በጀት ዓመት አራት ወራት ከጉምሩክ ቀረጥና ከአገር ውስጥ ገቢ 196.3 ቢሊዮን ብር ገቢ ለመሰብሰብ አቅዶ፣ 193.3 ቢሊዮን ብር በመሰብሰብ የዕቅዱን 98 በመቶ ማሳካቱን የገለጹት የገቢዎች ሚኒስትሯ ወ/ሮ ዓይናለም ንጉሤ ናቸው፡፡ ሚኒስትሯ ከዚህ ውስጥ ወደ መንግሥት ግምጃ ቤት 165 ቢሊዮን ብር መግባቱን ተናግረዋል፡፡በተጠቀሰው አራት ወራት ጊዜ ውስጥ የተሰጠው የቀረጥ ነፃ ተጠቃሚነት ዕድል 30 ቢሊዮን ብር ብቻ መሆኑ የተገለጸ ሲሆን፣ ይህም ካለፈው ዓመት ጋር ሲነፃፀር የአንድ ቢሊዮን ብር ቅናሽ ታይቶበታል ብለዋል፡፡በተጠቀሰው ጊዜ 321 የቀረጥ ነፃ አገልግሎት ተጠቃሚ ከነበሩ አካላት መካከል 278 ብቻ ሲጠቀሙ፣ ከቀሪዎች መካከል ደግሞ 42 ከታለመላቸው ዓላማ ውጪ መጠቀማቸው መረጃ በመገኘቱ ተጣርቶ ዕርምጃ ይወሰዳል ብለዋል፡፡ ወደ አገር ውስጥ ከገቡ 1231 የቱሪስት ተሽከርካሪዎች ውስጥ አገልግሎታቸውን ያጠናቀቁ ለታለመላቸው ዓላማ መዋላቸው ተረጋግጦ 250ዎች ወደ መጡበት አገር መመለሳቸው ተገልጿል፡፡ሚኒስትሯ ባለፉት አራት ወራት ብቻ የነበረው የሠራተኛ ፍልሰት ከፍተኛ መሆኑን ጠቅሰው፣ 57 ሠራተኞች መልቀቃቸውን አስረድተዋል፡፡ ይህም ሊሆን የቻለው የፋይናንስ ተቋማት እየበዙ መሆናቸውና የግሉ ዘርፈ የመቅጠር አቅም እያደገ መሄድ ሠራተኞችን እያስኮበለለ መሆኑን አውስተዋል፡፡ቋሚ ኮሚቴው በጹሑፍ ባቀረበው ጥያቄ በወጪ ንግድ አፈጻጸም በተለይ በሕጋዊ መንገድ የሚለካው መጠን እየቀነሰ በሕገወጥ መንገድ ለመላክ የሚደረገው ጥረት እየጨመረ ስለመሆኑ አንስቶ፣ ይህንን ሕገወጥ ንግድ መቆጣጠርና ከመሠረቱ ለምን መፍታት አልተቻለም ሲል ጠይቋል፡፡ የጉምሩክ ኮሚሽኑ በአራት ወራት ውስጥ ከመደበኛ ገቢ ዕቃዎች ፍተሻ ብቻ 29 ቢሊዮን ብር ማዳን መቻሉን የጉምሩከ ኮሚሽነሩ ገልጸዋል፡፡