
December 10, 2023 – EthiopianReporter.com

ዜና መገናኛ ብዙኃን ነፃነታቸውን ለድርድር ሳያቀርቡ በሥነ ምግባር እንዲሠሩ ጥሪ ቀረበ
ቀን: December 10, 2023
መገናኛ ብዙኃን ነፃነታቸውን ለድርድር ሳያቀርቡ በሥነ ምግባር እንዲመሩና ሥራቸውን በነፃነት እንዲሰሠሩ የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙኃን ምክር ቤት ጥሪ አቀረበ፡፡
ምክር ቤቱ ይህንን ጥሪ ያቀረበው ኅዳር 28 ቀን 2016 ዓ.ም. የሚዲያ የሥነ ምግባር የሚገኝበትን ደረጃ የዳሰሳ ጥናት በቀረበበትና ግብዓት በተሰበሰበበት ወቅት ነው፡፡
የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙኃን ምክር ቤት ሰብሳቢ አቶ አማረ አረጋዊ፣ ሁሉም ሚዲያ ነፃነቱን ለድርድር ሳያቀርብ፣ ከሐሰተኛ መረጃና ከጥላቻ ንግግር እየራቀ ሕዝብን ማገልገል እንዲችል ሥነ ምግባር ሊኖረው ይገባል ብለዋል፡፡
ምክር ቤቱ በዋናነት የመቋቋሙ ዋና ዓላማ ሚዲያው በሥነ ምግባር እንዲመራ ለማድረግ መሆኑን ገልጸው፣ ሥነ ምግባር ያለው ሚዲያ በኢትዮጵያ እንዲኖርና እንዲጠናከር ያስፈልጋል ብለዋል፡፡ ምክር ቤቱ የተቋቋመበት ሌላው ዓላማ ደግሞ ችግሮች ሲገጥሙ ወደ ሕግ ከማምራት ይልቅ፣ ሚዲያው ራሱን በራሱ የሚቆጣጠርበት አካል በብዙ ጥረት ሊቋቋም መቻሉን አስረድተዋል፡፡
ለሚዲያ ተቋማት በሥነ ምግባር ጉዳይ ትኩረት የሚሰጥበት ምክንያት፣ በኢትዮጵያ በሚዲያ የሥነ ምግባር ጉድለቶች ምክንያት የሚደርሰው ጉዳት ከፍተኛ በመሆኑ ነው ብለዋል፡፡
ከሃይማኖትና ከብሔር አንፃር የሚዲያ ሥነ ምግባር ሲፈተሽ፣ ኃላፊነታቸውን ዘንግተው ሥነ ምግባር በጎደለው መንገድ የጥላቻ ንግግርና ሐሰተኛ መረጃ የሚያሠራጩ ሚዲያዎች መብዛታቸውን አስረድተዋል፡፡
በዚህም ምክንያት የአገር ሰላም፣ ፍቅርና አንድነት አደጋ ላይ እንዲወድቅ ካደረጉ ውስጥ መገናኛ ብዙኃን እንደሚገኙበትና ተጠያቂም መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡
በተለያዩ የአገሪቱ አካባቢዎች ስለሚፈጠረው ክስተት ኅብረተሰቡ ትክክለኛ መረጃ ለማግኘት አስቸጋሪ እየሆነበት መምጣቱን ጠቁመዋል፡፡
ለዚህም መነሻ የሆኑት የበይነ መረብ ሚዲያ (የማኅበራዊ የትስስር ገጾች) የሚያወጧቸው መረጃዎች ትክክለኛ አለመሆናቸውን ገልጸው፣ በዚህም ሳቢያ ኅብረተሰቡ በሚደርሱት መረጃዎች ግራ እየተጋባ እንደሚገኝ አክለዋል፡፡
የመገናኛ ብዙኃን ሌሎች ተቋማትን ወቃሽ ብቻ ከመሆን ይልቅ፣ ‹‹እኛስ ተወቃሽ እንዳንሆን ምን ማድረግ አለብን?›› የሚለውን በውይይት አዳብሮ ትክክለኛውን ሚና እንዲጫወቱ በማድረግ፣ ኅብረተሰቡን ማገልገል እንደሚገባ አስረድተዋል፡፡
ላለፉት ስምንት ዓመታት በመምህርነትና በሚዲያ የራሳቸውን ፕሮግራም አዘጋጅተው የሚያቀርቡት ወ/ሮ ምሥራቅ ታረቀኝ፣ በውይይቱ ላይ በኢትዮጵያ የሚዲያ ሥነ ምግባር ላይ የተሠራ የዳሰሳ ጥናት አቅርበዋል፡፡
ጥናቱን ያካሄዱት በተለያዩ ሰባት የሚዲያ አጋዥ ተቋማት ላይ መሆኑን፣ ከእነዚህ ተቋማት የተገኘው መረጃ ሲጠቃለል በኢትዮጵያ በሚጠበቀው ልክ የሚዲያ ሥነ ምግባር እየተተገበረ እንዳልሆነ አመልክተዋል፡፡
በተለያዩ የሚዲያ ተቋማት አሳሳቢ እየሆኑ የመጡ ጉዳዮች ተብለው ከተነሱት መካከል፣ አብዛኛዎቹ ሚዲያ ላይ የሚሠሩ ጋዜጠኞች (ሙያተኞች) አለመሆናቸው፣ ተቋሙ ነፃ አለመሆኑን፣ በተለይ የበይነ መረብ ሚዲያ በማንኛውም ሰው መመራቱ አስቸጋሪ አድርጎታል ብለዋል፡፡
በበይነ መረብ የሚለቀቁ መረጃዎች ሥነ ምግባር የጎደላቸውና ለመቆጣጠርም አስቸጋሪ መሆናቸው በጥናቱ ተገልጿል፡፡