December 13, 2023 – EthiopianReporter.com 


ዜና
የሲቪክ ማኅበረሰብ ድርጅቶች በሰላም ዕጦት ሳቢያ ሥራቸውን ለማከናወን መቸገራቸው ተገለጸ

አበበ ፍቅር

ቀን: December 13, 2023

በአማራና ኦሮሚያ ክልሎች የሚንቀሳቀሱ የሲቪክ ማኅበረሰብ ድርጅቶች፣ በሰላም ዕጦት ሳቢያ ተዘዋውረው መሥራት አለመቻላቸው ተነገረ፡፡

በአማራና በኦሮሚያ ክልል የፀጥታ ችግር በጣም አሳሳቢ ደረጃ ላይ መድረሱ የተለያዩ በጎ አድራጎት ማኅበራት ሥራቸውን በአግባቡ ለመሥራት ትልቅ ፈተና እንደሆነባቸው፣ የሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶች ምክር ቤት አስታውቋል፡፡

በሰላም መደፍረስ ምክንያት ሥራቸውን ለመሥራት ከተቸገሩት ባሻገር፣ በትግራይ ክልል የሚገኙት የድርጅቱ አባላት የአቅርቦት ችግር እንደገጠማቸው የምክር ቤቱ ፕሬዚዳንት ንጉሡ ለገሰ (ዶ/ር) ገልጸዋል፡፡

ፕሬዚዳንቱ ይህንን የተናገሩት ሰኞ ታኅሳስ 1 ቀን 2016 ዓ.ም. የሲቪል ማኅበረሰብ ተሳትፎ በአሜሪካ ዓለም አቀፍ የልማት ድርጅት (ዩኤስኤአይዲ) ድጋፍ የሚደረግ አራት ዓመት ቆይታ ያለው ፕሮግራም ስምምነት በተደረገበት ወቅት ነው፡፡

በሥነ ሥርዓቱ ላይ ንግግር ያደረጉት ፕሬዚዳንቱ፣ በኦሮሚያ ክልል የሚገኙ ከ90 በላይ የሚሆኑ አባላቶቹ ያሉበት የሰላም ሁኔታ በእጅጉ አሳሳቢ እንደሆነ ተናግረዋል፡፡

‹‹በተደነገገው አዋጅና መመርያ መሠረት ለመሥራት የሚያግደን ነገር የለም፤›› ያሉት ፕሬዚዳንቱ፣ ነገር ግን ትልቅ ፈተና የሆነው የሕግ የበላይነት አለመከበር ነው ብለዋል፡፡

ጉዳዩን ለመንግሥት በተደጋጋሚ ያቀረቡ ቢሆንም በየቦታው የሕግ የበላይነት እየጠፋ ነው ሲሉ አስረድተዋል፡፡

በአዲስ አበባ ዙሪያ በሸገር ከተማ እንደ ጫንጮና ሱሉልታ በመሳሰሉ ቦታዎች ሀብት ያላቸው ሰዎች ከሥጋታቸው የተነሳ አዲስ አበባ መጥተው አድረው እንደሚመለሱ ገልጸው፣ እነዚህና መሰል ችግሮች በየቦታው እየገጠሟቸው በመሆኑ ሥራችውን ለማከናወን መቸገራቸውን ተናግረዋል፡፡

‹‹ከአዲስ አበባ 50 ኪሎ ሜትር ርቀት ለመሄድ ፈተና እየሆነብን ነው፤›› ያሉት ፕሬዚዳንቱ፣ በዚህም ሲቪል ማኅበረሰብን ጨምሮ ሌሎች ሰዎች እየተጎዱና እያለቀሱ ይገኛሉ ብለዋል፡፡

በአማራ ክልል ስላለው ግጭት ከሚመለከታቸው አካላት ጋር ወደ ጦርነት መግባቱ አስፈላጊ አይደለም በሚል ሞግተው እንደነበር ያስታወሱት ንጉሡ (ዶ/ር)፣ ‹‹በወቅቱ ፋኖ አሥርና ሃያ ሊሆን ይችላል፣ ነገር ግን ከአገር ሽማግሌዎችና ከሃይማኖት አባቶች ጋር ተነጋግረን ወደ ሰላም ካልተመለሱ ነገ ሁሉም ፋኖ ሊሆኑ ይችላሉ፤›› በማለት ወደ ግጭት እንዳይገባ ብዙ ሙከራዎችን አድርገው የነበረ ቢሆንም፣ ተቀባይነት ባለማግኘቱ አሁን ያለበት ሁኔታ ላይ ተደርሷል ሲሉ አስረድተዋል፡፡

በሲቪል ማኅበረሰብ በአሜሪካ ዓለም አቀፍ የልማት ድርጅት የገንዘብ ድጋፍ ለአራት ዓመት የሚቆይ ፕሮግራም የተጀመረ ሲሆን፣ ዓላማውም የማኅበረሰቡን የሰላም ግንባታና ተሳትፎ የሚያጠናክር እንደሆነ የተናገሩት የዩኤስኤአይዲ ኢትዮጵያ የፕሮግራም አስተባባሪ አቶ ረሺድ አብዱ ናቸው፡፡

ፕሮግራሙ በዋናነት የሚተገበረው በደሴ፣ በድሬዳዋና በአዲስ አበባ ሲሆን በተጨማሪ በሸገር ከተማና በኦሮሚያ ልዩ ዞን በከሚሴ ከተማ በሒደት እንደሚሆን አቶ ረሽድ ተናግረዋል፡፡