

ቀን:
ከሁለት ዓመታት በላይ የሰላም ሚኒስትር ደኤታ ሆነው ሲያገለግሉ የነበሩትን አቶ ታዬ ደንደአ፣ ‹‹ኢትዮጵያን ለማፍረስ ሠርተዋል›› በሚል ተጠርጥረው ማክሰኞ ታኅሳስ 2 ቀን 2016 ዓ.ም. በቁጥጥር ሥር ውለዋል።የፀጥታና ደኅንነት የጋራ ግብረ ኃይል ማክሰኞ ታኅሳስ 2 ቀን 2016 ዓ.ም. ባወጣው መግለጫ እንዳሳወቀው፣ አቶ ታዬ ‹‹ኢትዮጵያን ለማፍረስ ከሚንቀሳቀሱ ፀረ ሰላም ኃይሎች ጋር በመተሳሰር ለጥፋት ተልዕኮ በኅቡዕ ሲሠሩ ተደርሶባቸዋል፤›› ብሏል፡፡አቶ ታዬ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ለተለያዩ የመገናኛ ብዙኃን በሚሰጧቸው ቃለ ምልልሶችና በማኅበራዊ ትስስር ገጻቸው ከሚያገለግሉት መንግሥት ሌሎች ኃላፊዎች በተቃራኒ፣ አስተያየቶች ሲሰጡና መንግሥትን ሲተቹ እንደነበር ይታወሳል፡፡ሰኞ ታኅሳስ 1 ቀን 2016 ዓ.ም. ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ አህመድ (ዶ/ር) አቶ ታዬን ከሥልጣን ያሰናበቱ ሲሆን፣ አቶ ታዬ በይፋዊ የማኅበራዊ ትስስር ገጻቸው የስንብት ደብዳቤውን አጋርተው ጠቅላይ ሚኒስትሩን በይፋ ዘልፈው እንደነበር የሚታወስ ነው፡፡‹‹ስለነበረን አጭር ቆይታ አመሠግናለሁ፤›› ብለው የስንበት ደብዳቤያቸውን ባጋሩበት የማኅበራዊ ትስስር ገጽ የገለጹት አቶ ታዬ፣ ጠቅላይ ሚኒስትሩን ‹‹በተናገሩት የማይኖሩ ብቻ ሳይሆኑ በሰው ደም የሚጫወቱ አረመኔ መሆንዎን ተረድቻለሁ፤›› ሲሉ ስድብ አዘል ወቀሳ ሰንዝረዋል፡፡አቶ ታዬ በመልዕክታቸው የተሰናበቱበትን ምክንያት ሲያስረዱ፣ ‹‹ነገሩ ገብቶኝ የወንድማማቾች መገዳደል ይቆም ዘንድ ለሰላም በመወገኔ ከሥልጣን አነሱኝ፤›› ብለዋል፡፡የጋራ ግብረ ኃይሉ የሰላም ሚኒስትር ደኤታ የነበሩትን የአቶ ታዬን መኖሪያ ቤት ታኅሳስ 2 ቀን 2016 ዓ.ም. በፈተሸበት ወቅት፣ ‹‹በህቡዕ ለሚያደርጉት ፀረ ሰላም እንቅስቃሴ ሲገለገሉባቸው ነበር›› ያላቸውን በርካታ ቁሳቁሶች እንዳገኘ አስታውቋል፡፡አቶ ታዬ በአገሪቱ የተለያዩ አካባቢዎች ለተፈጸሙ የሽብር ድርጊቶች፣ ‹‹በተለይም ደግሞ ከዕገታ ጋር በተያያዘ›› እጃቸው ያለበት መሆኑን የጋራ ግብረ ኃይሉ እንደደረሰበት በመግለጫው አስረድቷል፡፡‹‹በመንግሥት ቁጥጥር ሥር ሊውሉ እንደሚችሉ ሲገምቱ ታጋይ ለመምሰል በራሳቸውና በተለያዩ የማኅበራዊ ሚዲያ ትስስር ገጾች አፍራሽና ፀረ ሰላም ጽሑፎችን በማናለብኝነት ሲያስተላልፉ ቆይተዋል፤›› ሲል መግለጫው ያትታል፡፡የፌዴራል መንግሥትና ኦነግ ሸኔ ለሁለተኛ ጊዜ ያደረጉት የሰላም ንግግር ያለምንም ስምምነት መጠናቀቁ በኅዳር ወር አጋማሽ ይፋ ተደርጎ ነበር፡፡ አቶ ታዬም ከዚህ የሰላም ድርድር በስምምነት ካለመጠናቀቅ በኋላ በተለያዩ ሚዲያዎችና ማኅበበራዊ ትስስር ገጻቸው፣ ለድርድሩ አለመሳካት መንግሥትን ጨምሮ ሁሉንም ወገኖች ሲወቅሱ እንደነበር አይዘነጋም፡፡