EthiopianReporter.com 

ማኅበራዊ ከኦሮሚያ ንብረታቸውን ጥለው የተፈናቀሉ ዜጎች ተገቢውን ካሳ ለመጠየቅ እየተመዘገቡ መሆኑ ተገለጸ

አበበ ፍቅር

ቀን: December 17, 2023

ከኦሮሚያ ክልል ተፈናቅለው በአማራ ክልል ደብረ ብርሃን ከተማ የሚገኙ ተፈናቃዮች፣ ይኖሩበት ከነበረው አካባቢ ጥለውት የመጡትን ንብረት የመመዝገብና መረጃን የማሰባሰብ ሥራን እየሠራ መሆኑን የደብረ ብርሃን ከተማ አስተዳደር አስታወቀ፡፡

የጠፋባቸውን ንብረት ለማወቅና ንብረታቸው ካልተገኘ ተገቢውን ካሳ ለመጠየቅ ተፈናቃዮች በሚሰጡት ግርድፍ መረጃ እየሰበሰቡ መሆኑን፣ የከተማ አስተዳደሩ የሥነ ሕዝብ ባለሙያና የተፈናቃዮች አስተባባሪ አቶ አንተነህ ገብረእግዚአብሔር ለሪፖርተር ተናግረዋል፡፡

መሬት ነበራቸው? ካላቸውስ ለመንግሥት ግብር በአግባቡ ይከፍሉ ነበር? የሚለውን መረጃ ጨምሮ በከተማ ወይም በገጠር ቤት ከነበራቸውና ሌሎች ንብረቶች ስለመኖር አለመኖራቸው እንዲሁም ከጠፉ በግምት ምን ያህል ይሆናሉ የሚሉትን ጠቅለል ያለ መረጃ እንዲያስመዘግቡ መደረጉን አቶ አንተነህ ገልጸዋል፡፡

ተፈናቃዮቹ ከሦስት ዓመት በላይ እንዳስቆጠሩ የተናገሩት አስተባባሪው፣ ከመስከረም 2016 ዓ.ም. ወዲህ እንኳን ከኦሮሚያ ክልል ተፈናቅለው ወደ ከተማዋ የገቡ ተፈናቃዮች ከ400 በላይ እንደሆኑ አክለዋል፡፡

ይሁን እንጂ በመንግሥትም ሆነ በተለያዩ ግብረ ሰናይ ድርጅቶች ይሰጥ የነበረው ድጋፍ በመቋረጡ፣ ቀደም ሲል የነበሩ ተፈናቃዮችን ጨምሮ ከሸገር ከተማና ከሌሎች የኦሮሚያ አካባቢዎች እየመጡ ያሉ ተፈናቃዮች ችግር ላይ መሆናቸውን አቶ አንተነህ ተናግረዋል፡፡

የሲቪክ ማኅበራት፣ የሃይማኖት ተቋማትና በጎ አድራጎት ድርጅቶች ካለው የኑሮ ውድነትና በክልሉ ካለው የፀጥታ ችግር መንቀሳቀስ ባለመቻላቸው፣ ከመስከረም ወር ጀምሮ ምንም ዓይነት ድጋፍ እያደረጉ እንዳልሆነ አስተባብረው ገልጸዋል፡፡

በመንግሥት በኩል በየወሩ ይሰጥ የነበረው ዕርዳታ ከተቋረጠ ከሁለት ወር በላይ ሆኖታል ሲሉ አክለዋል፡፡ መንግሥት መርዳት ካልቻለ የዓለም ምግብ ፕሮግራም (WFPI) እንዲገባ ቢፈቀድ ሲሉ አቶ አንተነህ ጠይቀዋል፡፡

የፌዴራል ቅድመ ማስጠንቀቂያና ምላሽ በበኩሉ መንግሥት የሀብት ውስንነት መኖሩን ያመነ ሲሆነ፣ ነገር ግን ክልሉ በሚሰጠው የተረጂዎች ቁጥር መሠረተ ድጋፍ እየተደረገ መሆኑን ተናግሯል፡፡

‹‹እኛ ክልሉ በሚሰጠን የተረጂዎች ቁጥር መነሻነት ለክልሉ እየላክን ነው፡፡ ምናልባት የደብረ ብርሃን ተፈናቃዮች በሪፖርቱ ካልተካተቱ የክልሉን መንግሥት መጠየቅ ይኖርባቸዋል፤›› ሲሉ የፌዴራል ቅድመ ማስጠንቀቂያና ምላሽ ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር አቶ ታዬ ጌታቸው ተናግረዋል፡፡

‹‹ምንም እንኳን ዕርዳታ የሚያስገልጋቸው ሰዎች መኖራቸው ቢታወቅም፣ ከክልሉ ጥያቄ ሳይቀርብ መስጠት ተጠያቂ ያደርጋል›› ያሉት አቶ ታዬ፣ በተለይ በክልሉ በመጠለያ ካምፕ የሚገኙ ተፈናቃዮችን መዝግበው እንዲልኩላቸው መጠየቃቸውን ገልጸዋል፡፡

ከጠቅላላው ተረጂ የቅድሚያ ቅድሚያ የሚያስፈልጋቸውን ለይተው እንዲሰጧቸው በጠየቁት መሠረት ቁጥራቸው ተልኮ ከሆነ የማይረዱበት ምክንያት የለም፡፡ ነገር ግን በሪፖርቱ ካልተካተቱ ‹‹ይህ የእኛ ሥራ አይደለም›› ሲሉ ዳይሬክተሩ አክለዋል፡፡

ላለፉት ሦስት ወራት ክልሉ የቅድሚያ ቅድሚያ ተረጂዎች ናቸው ብሎ በሰጠው መረጃ መሠረት፣ በሁለት ዙር ዕርዳታ መሰጠቱን አቶ ታዬ አክለው ተናግረዋል፡፡

ለክልሎቹ ሦስተኛ ዙር ዕርዳታ ለመስጠት መዘጋጀታቸውን የተናገሩት ዳይሬክተሩ፣ በአማራ ክልል አንድ ሚሊዮን ተረጂዎች የተመዘገቡ ሲሆን፣ ከእነዚህ ውስጥ የቀድሚያ ቅድሚያ መሰጠት ላለባቸው እንዲሰጡ ክልሉን መጠየቃቸውን አቶ ታዬ ገልጸዋል፡፡

የክልሉ መንግሥት የቅድሚያ ቅድሚያ ዕርዳታ የሚሰጣቸውን ተረጂዎች በአግባቡ መዝግቦ ለፌዴራል መንግሥት ሪፖርት ማድረግ ለምን አልቻለም የሚለውንና የፌዴራል ማስጠንቀቂያና ምላሽ በበኩሉ እየተሰጠ ነው ያለው ድጋፍ፣ ለተረጂዎች በአግባቡ ለምን አልደረሳቸውም ለሚሉት ጥያቄዎች ከአማራ ክልል አደጋ መከላከልና ምግብ ዋስትና ማብራሪያ ኮሚሽን ምላሽ ለማግኘት የተደረገው ተደጋጋሚ ሙከራ ባለመሳካቱ ምላሻቸውን ሳይካተት ቀርቷል፡፡