

ከስደት ተመላሾችን መልሶ ማቋቋምና ታዳጊዎችን ከጉልበት ብዝበዛ ለመታደግ፣ ተግባራዊ የሚደረገውን ፕሮጀክት ይፋ በተደረገበት ወቅት
ማኅበራዊ ከስደት ተመላሾችንና ታዳጊዎችን ተጠቃሚ ያደርጋል የተባለ ፕሮጀክት ይፋ ተደረገ
ቀን: December 24, 2023
ከስደት ተመላሾችንና የግለሰቦች ቤት ተቀጥረው ጉልበታቸው የሚበዘበዝ ታዳጊዎችን ተጠቃሚ የሚያደርግ ፕሮጀክት ለመተግበር፣ የሴቶችና ማኅበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴርና ፍሪደም ፈንድ ግብረ ሰናይ ድርጅት ስምምነት ላይ መድረሳቸውን አስታወቁ፡፡
ሁለቱ ተቋማት ይህንን ያስታወቁት ታኅሳስ 12 ቀን 2016 ዓ.ም. በስካይ ላይት ሆቴል በተካሄደው ከስደት ተመላሾችን መልሶ ማቋቋምና ታዳጊዎችን ከጉልበት ብዝበዛ ለመታደግ፣ ለሦስት ዓመታት ተግባራዊ የሚደረገውን ፕሮጀክት ይፋ ባደረጉበት ወቅት ነው፡፡
ከ277 ሚሊዮን ብር በላይ የተመደበለትና በአማራ ክልልና በአዲስ አበባ ከተማ አስተደደር የሚተገበር ፕሮጀክት፣ 65 ሺሕ ሰዎችን ተጠቃሚ ለማድረግ ለአንድ ሰው 4,900 ብር ሒሳብ እንደሆነ የፍሪደም ፈንድ ኢትዮጵያ ኃላፊ አቶ ዳንኤል መለሰ ተናግረዋል፡፡
ከ26,000 በላይ ከስደት ተመላሾችንና በቤት ውስጥ ጉልበታቸው የሚበዘበዝ ታዳጊዎችን ተጠቃሚ የሚያደርግ መሆኑን፣ ይህንን ተግባራዊ የሚያደረጉ አራት የአገር ውስጥ ማዕከላት መመረጣቸው ተገልጿል፡፡
አሁን ተግባራዊ የሚደረገው ፕሮጀክት መከላከልን፣ ከለላንና ጥበቃን መሠረት ያደረገ መሆኑን የገለጹት አቶ ዳንኤል፣ በችግሩ በጉዳዩ ላይ ትምህርት መስጠትና ውጤታማ ሥራ ለማከናወን መታቀዱን አስረድተዋል፡፡
ደኅንነቱ የተጠበቀ የሰዎች ፍልሰት እንዳይኖርና በግለሰቦች ቤት ውስጥ ዕድሜያቸው ሳይደርሰ ሥራ የሚሠሩ ታዳጊዎች ላይ ያተኮረ መሆኑን ገልጸዋል፡፡
በተለይ ከ18 ዓመት በታች የሆኑ ታዳጊዎችን ቀጥረው የሚያሠሩ ሰዎችን ማዕከል በማድረግ ትምህርት ቤት እንዲሄዱ፣ ዕረፍት እንዲያገኙና እንዲጫወቱ ለማድረግ የማስተማርና የማግባባት ሥራ እንደሚከናወን አክለዋል፡፡
ደኅንነቱ የተጠበቀ ፍልሰት ‹‹ኢትዮጵያ ቤቴ፣ ብሩህ ኢትዮጵያና ንጋት ኢትዮጵያ›› የተሰኙ ማዕከላትን መሠረት ያደረገ ፕሮጀክት መሆኑን ገልጸዋል፡፡
የሴቶችና ማኅበራዊ ጉዳይ ሚኒስትር ደኤታ ወ/ሪት ሁሪያ ዓሊ በበኩላቸው፣ ፕሮጀከቱ እ.ኤ.አ 2026 ድረስ ተግባራዊ ይደረጋል ብለዋል፡፡
ከሕገወጥ ስደት በተጨማሪ ዕድሜያቸው ያልደረሱ ታዳጊዎች ላይ የሚደርሰው የጉልበት ብዝበዛን ችግር ለመፍታት፣ ከመንግሥት በተጨማሪ ግብረ ሰናይ ድርጅቶች ትልቅ ሚና አላቸው ሲሉ አስረድተዋል፡፡
በኢትዮጵያ እየተንሰራፋ የመጣውን ከስደተኞች ጋር የተያያዙ ችግሮችን ለመቅረፍ፣ መንግሥታዊ ካልሆኑ ተቋማት ጋር በጋራ መሥራት እንደሚያስፈልግና ከስምምነት የተደረሰውም የዚሁ አካል መሆኑን ገልጸዋል፡፡
ፕሮጀክቱ በሒደት ላይ እያለ እስከ 500 ሚሊዮን ብር የሚደርሱ ተጨማሪ ሥራዎች መኖራቸውን አቶ ዳንኤል አክለዋል፡፡