
December 24, 2023 – EthiopianReporter.com

አቶ ጥበቡ ታደሰ
ዜና አገራዊ ምክክር ኮሚሽን በገንዘብ ምክንያት እጄ በውጭ አካላት አይጠመዘዝም አለ
ቀን: December 24, 2023
የኢትዮጵያ አገራዊ ምክክር ኮሚሽን ከመንግሥት ተገቢው በጀት ስለተመደበለት፣ በገንዘብ ፍለጋ ምክንያት ከውጭ አካላት ሊመጣ የሚችል ጫና እንደሌለና እጁ የሚጠመዘዝበት በር ዝግ መሆኑን አስታወቀ፡፡
የኮሚሽኑ ቃል አቀባይ አቶ ጥበቡ ታደሰ ዓርብ ታኅሳስ 12 ቀን 2016 ዓ.ም. ለጋዜጠኞች በሰጡት መግለጫ፣ ከዓለም አቀፉ ማኅበረሰብ ጋር በቅርበት አብሮ እየሠራ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ ይሁን እንጂ ኮሚሽኑ ከአገር ውስጥም ሆነ ከውጭ ካሉ ወገኖች ነፃ ተፅዕኖ የሚንቀሳቀስ ገለልተኛ ነው ብለዋል፡፡
ድጋፍ አድራጊ አካላት ለኮሚሽኑ የሚያቀርቡትን የፋይናንስና የቴክኒክ ድጋፍ ለዚሁ ዓላማ በተከፈተ አንድ ቋት አማካይነት እንደሚገባ ጠቅሰው፣ ይህ አሠራር የኮሚሽኑን ገለልተኝነትና ነፃነት እንዳይጎዳ ይረዳል ብለዋል፡፡ እስካሁን ኮሚሽኑ ምንም ዓይነት የውጭ ጫና እንዳልደረሰበትና መንግሥት ተገቢውን በጀት መድቦለት እየሠራ በመሆኑ፣ ‹‹ለበጀት ፍለጋ ብለን እጃችንን የምንጠመዘዝበት ዕድል ዝግ ነው፤›› ብለዋል፡፡ ይሁን እንጂ አገሪቱ ደሃ በመሆኗ ከውጭም ሆነ ከውስጥ በድጋፍ የተገኘን ሀብት ኮሚሽኑ ቢጠቀም አይጠላም ብለዋል፡፡
አገራዊ የምክክር ኮሚሽኑ በሕግ ጥላ ሥር ያሉ የፖለቲካ እስረኞችም ሆኑ ሌሎች ታራሚዎች፣ እንደ አንድ የኅብረተሰብ ክፍል በውይይትና በምክክር ሒደቱ እንዲሳተፉ መታየት ያለበት ጉዳይ ካለ በቀጣይ የሚወሰን ይሆናል ሲሉ አስረድተዋል፡፡
የኮሚሽኑ ምክር ቤት በጉዳዩ ላይ ተወያይቶ የተሳትፎው ጉዳይ በቀጣይ የሚታዩ መሆኑን፣ የሕግ የበላይነት እንደተጠበቀ ሆኖ የሚቀጥል ሥራ እንደሚሆን አስረድተዋል፡፡
ኮሚሽኑ ወቅታዊ አገራዊ ችግሮችን መፍታት ኃላፊነቱ ባይሆንም፣ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በመነጋገር የሚጠበቅበትን ዕገዛ እንደሚያደርግ ቃል አቀባዩ ተናግረዋል፡፡
ኮሚሽኑ ከተመሠረተ ሁለት ዓመታት ያህል ቢሆኑትምና መዘግየት እንዳለበት ቢነገርም፣ የኮሚሽኑ ቃል አቀባይ ለጋዜጠኞች በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ፣ ሥራው በጥንቃቄና ሁሉን አሳታፊ እንዲሆን ታስቦ እየተሠራ ስለመሆኑ ተናግረዋል፡፡
አጀንዳዎቻቸውን በኃይል አማራጭ ተግባራዊ እናደርጋለን በሚል ወደ ትግል የገቡ ወገኖችን በተመለከተ፣ ‹‹በእኛ እምነት እነዚህ ወገኖች ወደ ኃይል አማራጭ ሲገቡ የሐሳብ ልዩነት ስላላቸው ነው ብለን እናስባለን፤›› ብለዋል፡፡ ስለሆነም አለመግባባቶችን እንዴት እንፍታቸው የሚለው ጉዳይ የኮሚሽኑ ሥራ እንደሚሆን፣ በዚህም ከባለድርሻ አካላት ጋር በመሆን ሥራዎች እየተሠሩ ነው ብለዋል፡፡
በአገሪቱ ካሉ ወረዳዎች ውስጥ 327 የሚሆኑት በአገራዊ ምክክር ላይ የአጀንዳ ሐሳብ የሚሰጡ ተወካዮችን መርጠው ማጠናቀቃቸውን የገለጹት ቃል አቀባዩ በቀጣይ፣ በአገር አቀፍ ደረጃ በምክክሩ የሚሳተፉ ተወካዮችም የሚወከሉት ከእነዚህ መካከል ነው ብለዋል፡፡ በተጨማሪም በተለያዩ ክልሎች የሚገኙ 82 ወረዳዎች የአጀንዳ ሐሳብ የሚሰጡ ተወካዮቻቸውን በመምረጥ ላይ እንደሚገኙ አስረድተዋል፡፡