December 30, 2023 – Konjit Sitotaw
በታሪካዊው ዲማ ጊዮርጊስ ገዳም ጉባኤ ቤት ታህሳስ 13/2016 ዓ. ም በደረሰ የእሳት አደጋ በአጠቃላይ 2.3 ሚሊየን ብር በላይ የሚገመት ውድመት እንደደረሰበት የገዳሙ አበምኔት አባ ወልደ ኢየሱስ መቅጫ ለኢትዮ ኤፍ ኤም ተናግረዋል።
እሳቱ ከኤሌክትሪክ እንደተነሳ የገለፁት አባ ወልደ እየሱስ በገዳሙ ከሚገኙ ሰባት የመንፈሳዊ ትምህርት መስጫ ጉባኤ ቤቶች ውስጥ የመጻሕፍት ትርጓሜ መማሪያ ቤት ላይ ከባድ ጉዳት ማድረሱ አስታዉቀዋል።
በተጨማሪም አስር የተማሪዎች ማረፊያ እና ቤተመጻህፍትን ጨምሮ ለትምህርት አገልግሎት ይውል የነበረ ቤት በእሳቱ መውደሙ ተነግሯል፡፡
በእሳት አደጋዉ ከ1 መቶ ስልሳ በላይ መጻሕፍት ፣የመነኮሳት አልባሳት እንዲሁም ኮምፒውተሮችን ጨምሮ በአጠቃላይ በአሁናዊ የዋጋ ግምታቸው ከ 2 .3 ሚሊዮን ብር በላይ ሚገመት ንብረት መውደሙን የገዳሙ አበምኔት ጨምረው ገልፀዋል።
እሳቱ በአካባቢው በነበሩ ሰዎች ርብርብ ማጥፋት የተቻለ ሲሆን በሰው ላይ ያደረሰው ጉዳት እንደሌለ ተገልጿል።
በጉባኤ ቤቱ ላይ ያጋጠመው እሳት ያስከተለው ጉዳት ከፍተኛ በመሆኑ በመላው ዓለም የሚገኙ ምዕመናን መልሶ ማቋቋሙ ላይ አስፈላጊውን ርብርብ እንዲያደርጉ ጥሪ ቀርቧል፡፡
በአማራ ክልል ምሥራቅ ጎጃም ዞን እነማይ ወረዳ የሚገኘው የታሪካዊው ዲማ ጊዮርጊስ ገዳም በ1297 ዓ.ም እንደተመሰረተ ይነገራል፡፡