EthiopianReporter.com 

አቶ ሀብታሙ ታደሰ

ዜና የዛይ ራይድ ሜትር ታክሲ አገልግሎት እየሰጡ ያሉ ተሽከርካሪዎች መታሰራቸው ቅሬታ አስነሳ

ሰላማዊት መንገሻ

ቀን: January 7, 2024

የዛይ ራይድ ሜትር ታክሲ አሽከርካሪዎች ‹‹በአዲስ አበባ ከተማ ውስጥ ወንጀል እየተሠራ ነው›› በሚል ምክንያት ተሽከርካሪዎቻችን እየታሰሩ ነው ሲሉ ቅሬታ አቀረቡ፡፡

ስማቸው እንዲጠቀስ ያልፈለጉ የዛይ ራይድ ሜትር ታክሲ አሽከርካሪ፣ ከአንድ ሳምንት በፊት ምሽት ላይ ሦስት የደኅንነት ሠራተኞች መሆናቸውን መታወቂያ በማሳየት ተሽከርካሪውን ከያዙ በኋላ አሽከርካሪው ወደ ቤቱ እንዲሄድ ማድረጋቸውን ገልጸዋል፡፡

በቀጣዩ ቀን ተሽከርካሪውን ለማስመለስ በሚሄዱበት ወቅት መኪናቸው የታሰረበት አበበ ቢቂላ ፖሊስ ጣቢያ በሌሎች መኪኖች ተሞልቶ እንደነበር በማስታወስ፣ ከላይ በመጣ ትዕዛዝ ተሽከርካሪው መታሰሩንና ምርመራ ተደርጎ ከተጣራ በኋላ እንደሚለቀቅ ከፖሊስ ጣቢያው እንደተነገራቸው አስረድተዋል፡፡

‹‹ምርመራ ተደርጎ ይለቀቃሉ የተባለው ከሁለት ቀናት በኋላ የነበረ ቢሆንም፣ የተያዙት ተሽከርካሪዎች ሳይለቀቁ ስምንት ቀናት ሆኗቸዋል፤›› ሲሉ ግለሰቡ ለሪፖርተር ተናግረዋል፡፡

የዛይ ራይድ ሜትር ታክሲዎች ብቻ ተመርጠው የሚታሰሩት እስካሁን ባልፀደቀ መመርያ የኮድ 2 ተሽከርካሪዎች የሜትር ታክሲ አገልግሎት መስጠት የማይችሉ በመሆናቸው ሊሆን እንደሚችል ግለሰቡ ጥርጣሬያቸውን ገልጸዋል፡፡

የኮድ 2 ተሽከርካሪዎች አገልግሎት እንዲሰጡና ታክስ መክፈል የሚችሉበት አሠራር እንዲኖር፣ በአዲስ አበባ ከተማ ትራንስፖርት ቢሮ መፈቀድ የሚያስችል ፕሮፖዛል ቀርቦ፣ የድጋፍ ሰጪ ቡድን እየተመለከተው ይገኛል ሲሉ የዛይ ራይድ መሥራችና ዋና ሥራ አስኪያጅ አቶ ሀብታሙ ታደሰ ለሪፖርተር ተናግረዋል፡፡

ማስፈቀዱ በሒደት ላይ በሚገኝበት በዚህ ወቅት፣ በድርጅቱ ሥር የተመዘገቡ ተሽከርካሪዎች ወንጀል ፈጽመዋል በሚል ምክንያት እየታሰሩ ነው ሲሉ አቶ ሀብታሙ አስረድተዋል፡፡

ከአሽከርካሪዎቹ ሪፖርት መቅረብ የጀመረው ከሳምንት በፊት በመሆኑ፣ ዛይ ራይድ ጉዳዩ በቀጥታ ከሚመለከተው የፌዴራል ፖሊስ ኮሚሽን ጋር ንግግር ማድረጉን ገልጸዋል፡፡

የፌዴራል ፖሊስ ኮሚሽን ከሁለት ሳምንታት በፊት ታኅሳስ 22 ቀን 2016 ዓ.ም. ከሁሉም የሜትር ታክሲ አገልግሎት ሰጪዎች ጋር ስብሰባ ማድረጉን አቶ ሀብታሙ አስታውሰዋል፡፡

በሜትር ታክሲ አገልግሎት ሰጪዎች አማካይነት በአንድ ሳምንት ውስጥ ሦስት ከባድ ወንጀሎች በመፈጸማቸው፣ የአገልግሎት አሰጣጡ ደኅንነት እንዲጠበቅ የተደረገ ስብሰባ ነው ብለዋል፡፡

ለአሽከርካሪዎቹና ለተሳፋሪዎቹ ደኅንነት ጥበቃ ለማድረግ አንዱ መፍትሔ ተሽከርካሪዎች ላይ ካሜራ መግጠም እንደሆነ በስብሰባው መነሳቱን፣ የፌዴራል ፖሊስ ኮሚሽን የኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ዳይሬክተር አቶ ጀይላን አብዲ ለሪፖርተር ተናግረዋል፡፡

‹‹የዛይ ራይድም ሆነ ሌሎች የሜትር ታክሲ ተሽከርካሪዎችን ብቻ በመለየት የሚታሰሩበት ምክንያት የለም፤›› ያሉት አቶ ጀይላን፣ በተጨባጭ መረጃ የተገኘባቸውና ወንጀል ለመሥራታቸው ጥቆማ የቀረበባቸው 35 መደበኛ ታክሲዎችና የሜትር ታክሲ ተሽከርካሪዎች መታሰራቸውን ተናግረዋል፡፡

በፌዴራል ፖሊስ ኮሚሽነር ጄኔራል ደመላሽ ገብረ ሚካኤል የሚመራ፣ ‹አዲስ አበባ ከተማን ከወንጀል ማፅዳት› የሚል ኦፕሬሽን በመጀመሩ፣ በከተማው ውስጥ ፍተሻ በማካሄድ ወንጀል የፈጸሙ እየታሰሩ ነው ሲሉ አቶ ጀይላን ገልጸዋል፡፡

ሁሉንም የሜትር ታክሲ አገልግሎት ሰጪዎችን ወንጀለኛ ለማድረግ ሳይሆን፣ በኮድ 2 በመመዝገብ ወንጀል እየተፈጸመ በመሆኑ ጥንቃቄ መደረግ አለበት ብለዋል፡፡

የዛይ ራይድ ተሽከርካሪዎችን ጉዳይ በተመለከተ የታሰሩበት ምክንያት እንዲገለጽ፣ እንዲሁም በቀጣይ መፍትሔ እንዲያገኙ ድርጅቱ ለፌዴራል ፖሊስ ኮሚሽን ደብዳቤ መላኩን አቶ ሀብታሙ ገልጸዋል፡፡

ደብዳቤ ከመላክ በተጨማሪ ድርጅቱ የተደራጀ መረጃ በመያዝ በፖሊስ የቴሌቪዥን ፕሮግራም መረጃ ለመስጠት ቀጠሮ መያዙን አቶ ጀይላን አስረድተዋል፡፡