January 9, 2024 – Konjit Sitotaw
ለአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ሰራተኞች የተሰጠው ፈተና ውጤት ይፋ ሆኗል።
በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ እና በኮተቤ የትምህርት ዩኒቨርሲቲ የተዘጋጀው እና ለአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ሰራተኞች ሲሰጥ የነበረው ፈተናን በሚመለከት በዛሬው ዕለት መግለጫ ተሰጥቷል።
በዚህ መግለጫም ፤ ፈተናውን የወሰዱት የከተማ አስተዳደሩ የቴክኒክና ባህሪ ብቃት ፈተና ለአመራሮች፣ ለባለሙያዎችና ሰራተኞች ቁጥር 15 ሺህ 151 መሆኑ ተገልጿል።
ከዚህ ውስጥ የአመራሩ ቁጥር 4 ሺህ 213 ሲሆን የፈተውን ማለፊያ ውጤት ያመጡት 1 ሺህ 422 ናቸው። ይህም 34 በመቶው አመራሮች አልፈዋል። አመራሩ ለማለፍ ከ60 በመቶ በላይ ማምጣት ይጠበቅባቸዋል።
ፈተናውን የወሰዱ የሠራተኞች ቁጥር 10 ሺህ 257 ሲሆኑ ያለፉት 5 ሺህ 95 ናቸው ተብሏል። ይህም 50 በመቶ ነው። ሰራተኞች ለማለፍ ከ50 በመቶ በላይ ማምጣት አለባቸው።
ለፈተና ከተቀመጡት አጠቃላይ ቁጥር 681 የሚሆኑት በተለያየ የስነ ምግባር ጥሰት ከፈተና ውጪ መሆናቸውን እና 441 የሚሆኑት ደግሞ በፈተና ስፍራ ያልተገኙ መሆናቸው ተገልጿል።