
January 24, 2024

የኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ኮሚሽን ኮሚሽነሯን ጨምሮ ሁለት ምክትል ኮሚሽነሮች ከኃላፊነታቸው ተነስተው፣ በሌሎች አዳዲስ ተሿሚዎች መተካታቸው ተረጋገጠ፡፡ ባለፉት ስድስት ዓመታት ውስጥ ለተቋሙ ኮሚሽነሮች ሲሾሙ የአሁኑ ለአምስተኛ ጊዜ መሆኑ ታውቋል፡፡
ኮሚሽኑን ላለፉት ሦስት ዓመታት ያህል የመሩት ሌሊሴ ነሜ የኢትዮጵያ የአካባቢ ጥበቃ ባለሥልጣን ዋና ዳይሬክተር ሆነው መሾማቸውን ምንጮች ለሪፖርተር ጠቁመው ወ/ሮ ሌሊሴ ወደ ባለሥልጣኑ የተዛወሩት፣ የቀድሞውን ዋና ዳይሬክተር ጌታሁን ጋረደው (ዶ/ር) በመተካት ነው፡፡
ወ/ሮ ሌሊሴ ወደ ኢንቨስትመንት ኮሚሽን ከመምጣታቸው በፊት፣ የኢትዮጵያ ኢንዱስትሪ ፓርኮች ልማት ኮርፖሬሽንን በ24 ዓመታቸው በመምራት በዕድሜ ትንሿ ባለሥልጣን እንደነበሩ አይዘነጋም፡፡
በምትካቸው የኢትዮጵያ ፖስታ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ሆነው ሲያገለግሉ የቆዩት ወ/ሮ ሃና አርዓያ ሥላሴ አዲሷ የኢንቨስትመንት ኮሚሽን ኮሚሽነር ሆነው ተሹመዋል፡፡ ወ/ሮ ሃና ባለፈው ሳምንት በጠቅላይ ሚኒስትሩ ከተሾሙ በኋላ፣ ሰኞ ጥር 13 ቀን 2016 ዓ.ም. ከወ/ሮ ሌሊሴ ጋር የሥራ ርክክብ ማድረጋቸውን ማረጋገጥ ተችሏል፡፡
የሕግ ምሩቅ የሆኑት ወ/ሮ ሃና ወደ ኢትዮጵያ ፖስታ ከመዛወራቸው በፊት፣ አሁን ዋና ኮሚሽነር ሆነው በተሾሙበት በኢንቨስትመንት ኮሚሽን የኢንዱስትሪ ፓርኮች ዘርፍ ምክትል ኮሚሽነር ሆነው አገልግለዋል፡፡ ቀደም ሲል በጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት መሥራታቸው ይታወሳል፡፡ ወ/ሮ ሌሊሴና ወ/ሮ ሃና ወደ መንግሥታዊ ተቋም በተሿሚነት የመጡት ከ2010 ዓ.ም. ለውጥ በኋላ ነበር፡፡
በሌላ በኩል ለኢትዮጵያ ፖስታ አዲስ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ባለመሾሙ በምክትል ኃላፊዎች እየተመራ መሆኑ ታውቋል፡፡
ከቦታቸው ለተነሱት የኢንቨስትመንት ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነሮች አዳዲስ ኃላፊዎች የተሰየሙ ሲሆን፣ የተመደቡባቸውን ተቋማት ስም ማወቅ አልተቻለም፡፡ የኮሚሽኑ አንደኛው የቀድሞ ምክትል ኮሚሽነር አቶ ዳንኤል ተሬሳ ግን የሥራና ክህሎት ሚኒስትር ደኤታ ሆነው መሾማቸውን ለማወቅ ተችሏል፡፡