
ከ 6 ሰአት በፊት
ዩናይትድ ስቴትስ፣ አውስትራሊያ፣ ባሕሬን፣ ካናዳ እና ኔዘርላንድስ ጦራቸውን አጣምረው የሁቲ አማፂያንን ለመደምሰስ ቆርጠው ተነስተዋል።
ነገር ግን ይህ ጦርነት በቀላሉ የሚወጡት እንዳልሆነ እሙን ነው።
ኢራን በገንዘብ የምትደግፋቸው የሁቲ አማፂያን ካለፈው ኀዳር ወር ጀምሮ ቀይ ባሕርን አቋርጠው በሚጓዙ የንግድ መርከቦች ላይ ከ30 በላይ ጥቃቶች ሰንዝረዋል።
የዩኤስ መከላከያ ባለሥልጣናት አማፂያኑን ሳንደመስስ አርፈን አንቀመጠም እያሉ ነው።
ባለሥልጣናቱ ባለፈው ሳምንት በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ “ቡድን የሚያደርሰውን አደጋ ለመግታትም ሆነ ለማምከን ተጨማሪ እርምጃዎችን ከመወሰድ አንታቀብም፤ የቀይ ባሕር ቀጣና እስኪረጋጋ ድረስ እንቀጥላለን” ብለዋል።
አማፂያኑ የሚወስዱት እርምጃ ዓለም አቀፍ ንግድን ያናወጠ ሲሆን በእስራኤልና ሐማስ መካከል የተነሳው ጦርነት በመካከለኛው ምስራቅ የበለጠ አለመረጋጋት ምክንያት እንዳይሆን ስጋት አለ።
ሳዑዲ አረቢያ ለዘመናት ታግላ ያቃትትን ጦርነት ዩናይትድ ስቴትስ ማሸነፍ ትችል ይሆን?
የሳዑዲ ኪንግደም በቀይ ባሕር ላይ የተነሳውን የሰሞኑን ግጭት አይቶ እንዳላየ ማለፍ መርጧል። በሳዑዲ እና በሁቲ መካከል የሰላም ድርድር እየተካሄደም ይገኛል።

- የተባበሩት መንግሥታት ለጋዛ እርዳታ ማድረግ ያቆሙ አገራትን አወገዘከ 9 ሰአት በፊት
- አላባማ የሞት ቅጣት የተፈደበትን ግለሰብ በናይትሮጂን የገለደችው ለምንድነው?ከ 9 ሰአት በፊት
- ሰሜን ኮሪያ ተደጋጋሚ የክሩዝ ሚሳኤል ሙከራ አደረገች28 ጥር 2024
ዩኬ እና ዩኤስ ለምን የመንን ያጠቃሉ?
የሁቲ አማፂያን ጥቃት ከመጀመራቸው በፊት ዲፕሎማሲያው እምርጃዎች ተሞክረው ነበር። ነገር ግን መጨረሻቸው አላማረም።
በየመን የአሜሪካ ልዩ መልዕክተኛ ቲም ሌንደርኪንግ “ይህ ሳይሳካ መቅረቱ የሚያስቆጭ ነው” ይላሉ።
አብዛኛውን የየመን ክፍል የሚቆጣጠሩት የሁቲ አማፂያን የሚሉት ጥቃቶቹን እያደረሱ ያሉት እስራኤል በጋዛ እያደረሰች ያለችውን ጥቃት በመቃወም እና ከፍልስጤማዊያን ጎን ለመቆም ነው።
ነገር ግን በየመን አቅጣጫ የሚጓዝ የትኛውንም መርከብ ከመምታትና የመርከቦቹን ሠራተኞች አደጋ ላይ ከመጣል ወደኃላ አይሉም።
ዊሊያም ዌችስለር የአትላንቲክ ካውንስል ቲንክ ታንክ አባል ናቸው።
እሳቸው እንደሚሉት ዩኬ እና ዩኤስ ጥቃት ሲሰነዘር ምላሽ ከመስጠት ውጭ ምንም አማራጭ የላቸውም።
“በዓለም አቀፍ ንግድ ስምንት የባሕር ላይ ‘ቾክፖይንትስ’ [አዳጋች የሚባሉ ሥፍራዎች] አሉ። ከእነዚህ መካከል ግማሽ ያክሉ መካከለኛው ምስራቅ ነው የሚገኙት። ይህ ሥፍራ ደግሞ ለዓለም የኢነርጂ አቅርቦት በጣም ወሳኙ ሥፍራ።”
የሁቲ አማፂያን ከእነዚህ ሥፍራዎች መካከል ባብ አል ማንዴብ የተባለውን አካባቢ ባልተመደ መልኩ አስቸጋሪ እንዲሆን አድርገውታል።
“የኢነርጂ አቅርቦት ምን ያህል ለኅልውናችን አስፈላጊ እንደሆነ የሚገባው ሰው፤ ለምጣኔ ሀብታችን አስፈላጊ መሆኑን የሚያውቅ ሰው እኒህን ሥፍራዎች መቆጣጠር አስፈላጊ መሆኑን ይረዳል።”

የሁቲ አማፂያን ምን ያህል ጠንካራ ናቸው?
ቡድኑ ምን ያክል ጠንካራ መሆኑን ያሳየው የሳዑዲ አረቢያን ጦር መቋቋም በቻለ ወቅት ነው።
ለኢራን ድጋፍ ምስጋና ይሁንና አማፂያኑ በሥልጠና እና በጦር መሣሪያ አቅም ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተሻሻሉ መጥተዋል።
“ሁለት ፅናቶች ዓይነቶች አሉ። አንደኛው ፈቃደኝነት ነው። ሌላኛው ደግሞ አቅም ነው። ማንም የሁቲዎችን ጠንካራ ፅናት እሰብራለሁ ብሎ አያስብም። ነገር ግን አቅማቸው እንሰብራለን ብሎ ማሰብ ይቻላል” ይላሉ ዊሊያም።
ምንም እንኳ የሁቲ አማፂያን ጠንካራ ከሚባል ወታደራዊ ኃይል ጋር ተዋግተው አቅማቸውን ቢያሳዩም አሜሪካና አጋሮቿን መግታት ቀላል አይሆንም።
አሜሪካና አጋሮቿ ያላቸው ጉልበት፣ ስትራቴጂ እና ልምድ ከሳዑዲ ሲነፃፀር የትየለሌ ነው።
አሁን ተንታኞች እየጠየቁ ያሉት ጥያቄ አሜሪካ ይህን ጦርነት ለመርታት ምን ያህል ትጓዛላች? ነው።
“ያለን ኃይል ሀያል ነው። ነገር ግን በብልሀት መጠቀም አለብን” የሚሉት ደግሞ የውጭ ጉዳይ ካውንስል የመካከለኛው ምስራቅና አፍሪካ ጥናት ማዕከል ነባር አባል የሆኑት ስቲቨን ኩክ ናቸው።
“የመንን እንውረር አሊያም አገዛዝ እንቀይር ወይም ከዚህ ቀደም የምናደርጋቸውን ነገሮች እናድርግ አይደለም የምንለው። ያናገርኳቸው የአረብ ባለሥልጣናት ሁቲዎችን መነካካት ማቆሚያ የሌለው ማጥ ውስጥ መግባት ነው ብለውኛል። ነገር ሁቲዎች መልሰው ጥቃት እንዳያደርሱ የሚያደርግ እርምጃ መውሰድ እንችላለን።”

አሜሪካና አጋሮቿ መውጫ የሌለው ጦርነት ውስጥ እየገቡ ነው?
አድሚራል ጄምስ ፎጎ የቀድሞው የአፍሪካ እና አውሮፓ ባሕር ኃይል አዛዥ ነበሩ።
በ2000 ዓ.ም. የሆነውን ያወሳሉ። በወቅቱ አራን ታንከር የጫኑ መርከቦችን ስታጠቃ አሜሪካ በምላሹ የአራንን ባሕር ኃይል አጠቃች።
ከዚህ በኋላ ነው የመን የሚገኘው የአሜሪካው ጦር መርከብ ዩኤስኤስ ኮል ጥቃት ደርሶበት 17 የባሕር ኃይል አባላት የተገደሉት።
ምንም እንኳ ይህ ጥቃት በአል-ቃይዳ ነው የደረሰው ቢባልም አሜሪካ ይህ ታጣቂ ቡድን ላይ ምንም ዓይነት እርምጃ አልወሰደችም።
“ከአንድ ዓመት በኋላ ምን ሆነ? የመስከር 11 አደጋ ደረሰ” የሚሉት አድሚራሉ ወታደራዊ እርምጃ መወሰድ እንዳለበት ያምናሉ።
በዚህ ሐሳብ ስቲቨን ኩክም ይስማማሉ፡ “ባሕር ላይ በነፃነት መንቀሳቀስ የአሜሪካ አንዱ ፍላጎት ነው። ይህ ቡድን ጉልበቱን በአካባቢው እንዲያሳይ መፍቀድ ተገቢ አይደለም” ይላሉ።
የኢራን ጣልቃ ገብነት
የሁቲ አማፂያ ከኢራን የገንዘብ ድጋፍ የሚደርግላቸው ቢሆንም ሙሉ በሙሉ በቴህራን ቁጥጥር ሥር አይደሉም።
የሁቲ አማጺያን በሊባኖስ ውስጥ የሚገኘው የሺአው ታጣቂ ቡድን ሄዝቦላህ ጋር ጥብቅ ቁርኝት አላቸው።
ሄዝቦላህም ለሁቲ አማጽያን ከአውሮፓውያኑ 2014 ጀምሮም ሰፊ ወታደራዊ ስልጣናዎችን እየሰጣቸው መሆኑን ሽብርተኝነትን የሚዋጋው ‘ዘ ኮምባቲንግ ቴሬሬዚም ሴንተር’ የተሰኘው የአሜሪካው የምርምር ተቋም አስታውቋል።
ሁቲዎች ኢራንን በአጋርነት የሚያይዋት ሲሆን ሳዑዲ አረቢያም የጋራ ጠላታቸው ናት።
ኢራን ለሁቲ አማጺያን የጦር መሳሪያ ታቀርባለችም የሚሉ ጥርጣሬዎችም ጎልተው ይሰማሉ።
ሁቲዎች በአውሮፓውያኑ 2017 በሳዑዲ መዲና ሪያድ ላይ ያስወነጨፉትን ባለስቲክ ሚሳኤል ያቀረበችው ኢራን ናት በማለት አሜሪካ እና ሳዑዲያ አረቢያ ይከሳሉ። ሚሳኤሉ ተተኩሶበት መውደቁ ይታወሳል።
በተጫማሪም በአውሮፓውያኑ 2019 ሁቲዎች የሳዑዲ ነዳጅ ማምረቻዎችን ለማጥቃት የተጠቀሙባቸውን የክሩዝ ሚሳኤሎች እና ድሮኖችን (ሰው አልባ አውሮፕላኖችን) የሰጠችው ኢራን ናት በሚልም ሳዑዲ አረቢያ ትከሳለች።
ሁቲዎች በአስር ሺዎች የሚቆጠሩ የአጭር ርቀት ሚሳኤሎችን ወደ ሳዑዲ አረቢያ ያስወነጨፉ ሲሆን በተባበሩት አረብ ኤምሬቶች ኢላማዎችም ላይ ጥቃት ሰንዝረዋል።

እነዚህን መሳሪያዎች ለሁቲ አማጽያን ማቅረብ የተባበሩት መንግሥታት በኢራን ላይ የጣለውን የጦር መሳሪያ እገዳን የሚጥስ ቢሆንም ኢራን በጭራሽ ክሱን አትቀበለውም።
ተንታኞች እንደሚሉት የፕሬዝደንት ባይደን መንግሥት ሁቲዎችን ለማዳከም የተነሳ ቢሆንም ኢራንን ቀጥታ ከመጋፈጥ ተቆጥቧል።
ፔንታገን እንደሚለው ከጥር ወር መባቻ ጀምሮ ከ25 በላይ የሁቲ የሚሳዔል መተኮሻዎችና ከ20 በላይ ሚሳኤሎችን ከጥቅም ውጭ አድርጓል።
ጨምሮም ድሮኖችን፣ የራዳር እና የአየር ቁጥጥር መሣሪዎችንና የጦር መሣሪያ ማከማቻወችን አውድሟል።
ጉዳዩን የሚከታተሉ ሰዎች የሁቲ አማፂያን ይህን ጥቃት የምዕራባዊያንን አቅም መቋቋም እንደሚችሉና ከፍልስጤም ጋር እየወገኑ እንዳለ ለየመን ሕዝብ ለማሳየት እየተጠቀሙበት ነው።
የየመን ሁቲ ከሐማስ ጎን ቆመው በኢራን የሚደገፈው አክሲስ ኦፍ ሬዚስታንስ ቡድን አባል በመሆን ዝናቸው በአረቡ ዓለም እየተስፋፋ እንደሆነ ተንታኞች ያምናሉ።
ምንም እንኳ 30 በመቶ የሚሆነው የሁቲ አማፂያን የጦር አቅም ጉዳት እንደደረሰበት ቢታመንም አማፂያኑ ቀይ ባሕር ላይ የሚያደርሱትን ጥቃት ያቆማሉ የሚል እምነት የለም።