
ዜና በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ንብረታቸው ለወደመባቸው ባለሀብቶች የካሳ ጥያቄ የፌዴራል መንግሥት ምላሽ እንዲሰጥ ተጠየቀ
ቀን: January 28, 2024
በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል በነበረው የፀጥታ ችግር ምክንያት በታጣቂዎች ንብረታቸው የወደመባቸው 291 ባለሀብቶች ያቀረቡት የካሳ ጥያቄ፣ የፌዴራል መንግሥት ምላሽ እንዲሰጥ መቅረቡ ተገለጸ፡፡
በክልሉ ተፈጥሮ በነበረው የፀጥታ ችግር በርካታ ሰዎች ሕይወታቸው ማለፉንና ባለሀብቶችም ንብረታቸው ሙሉ ለሙሉ በሚባል ደረጃ መውደሙ ይታወሳል፡፡
ከ2012 ዓ.ም. ጀምሮ ባለሀብቶች በነበረው የፀጥታ ችግር ምክንያት የወደሙባቸውን ንብረቶችና ሌሎች ጉዳዮች አስመልክቶ ክልሉ ለማጣራት ለኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ኮሚሽን መላኩን፣ የቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል የኢንዱስትሪና ኢንቨስትመንት ቢሮ የኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ዳይሬክተር አቶ ጋሻው ሹሞ ለሪፖርተር ተናግረዋል፡፡
የኢንቨስትመንት ኮሚሽን የውጭ ባለሀብቶችን ብቻ እንደሚያስተናግድ፣ የአገር ውስጥ ባለሀብቶችን በተመለከተ የኢንዱስትሪ ሚኒስቴርን እንደሚመለከተው ማስታወቁን አቶ ጋሻው ገልጸዋል፡፡
በክልሉ ንብረታቸው የወደመባቸው ባለሀብቶች ያለውን ችግር ከግምት ውስጥ በማስገባት፣ ከ50 እስከ 55 በመቶ የመሬት ኪራይ ግብር እንዲከፍሉ መደረጉን ጠቁመዋል፡፡
የባለሀብቶችን ጉዳይ በተመለከተ ክልሉ ለኢንቨስትመንት ኮሚሽን ቢልክም፣ ኮሚሽኑ ደግሞ በጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት በኩል ለተቋቋመ ኮሚቴ ማስረከቡን ዳይሬክተሩ አስረድተዋል፡፡
በፀጥታው ችግር ምክንያት ንብረታቸው የወደመባቸው ባለሀብቶች ምን ያህል የካሳ ክፍያ ይከፈላቸዋል? ምን ዓይነት ውሳኔ ይሰጣቸዋል? ለሚለው ግልጽ የሆነ መረጃ ቢሮው እንደሌለው አብራርተዋል፡፡
ቢሮው በአሁኑ ወቅት በስድስት ወራት በተለያዩ ኢንቨስትመንቶች ለተሰማሩ 284 ባለሀብቶች ፈቃድ መስጠቱን ገልጸው፣ እነዚህ ባለሀብቶች ከአራት ቢሊዮን ብር በላይ ማስመዝገባቸውን አስረድተዋል፡፡
በተመሳሳይ ለኢንዱስትሪ ፓርክ የሚሆን 360 ሔክታር መሬት ክልሉ ማዘጋጀቱንና ለኢንዱስትሪ ፓርኮች ኮርፖሬሽን ማስታወቃቸውን ተናግረዋል፡፡
በክልሉ የኢንዱስትሪ ምርት ግብዓትና የመሸጫ ቦታ ችግር መኖሩን ጠቅሰው፣ በአጠቃላይ ንብረታቸው የወደመባቸው ባለሀብቶችም ሆኑ አዳዲስ ባለሀብቶች፣ በአሁኑ ወቅት ወደ ሥራ እንዲገቡ ቢሮው ከባለሀብቶቹ ጋር ውይይት አድርጎ መስማት ላይ መድረሱን አክለዋል፡፡
ከዚህ በፊት በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል በነበረው የፀጥታ ችግር ንብረታቸው የወደመባቸው አብዛኞቹ ኢንቨስተሮች፣ በግብርና ዘርፍ የተሰማሩ መሆናቸውን አቶ ጋሻው ገልጸዋል፡፡
በክልሉ በአሁኑ ወቅት ሰላም እንደሰፈነና ባለሀብቶችም ወደ ሥራ ገብተው የክልሉን ኢኮኖሚያዊ ዕድገት ማቀላጠፍ አለባቸው ብለዋል፡፡
በክልሉ ተሰማርተው ንብረታቸው የወደመባቸው ባለሀብቶች በአጠቃላይ የተሰጣቸው መሬት ምን ያህል እንደሆነ መረጃው እንደሌላቸው አስረድተዋል፡፡
በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል በፀጥታ ችግር ምክንያት ንብረታቸው የወደመባቸው ባለሀብቶች የካሳ ክፍያ ምን ያህል እንደሆነና ሌሎች ጉዳዮችን በተመለከተ፣ የኢንዱስትሪ ሚኒስቴርን ለመጠየቅ ጥረት ቢደረግም አልተሳካም፡፡