EthiopianReporter.com 

አቶ ካሱ ከበደ የወርልድ ቪዥን ኢትዮጵያ የውጭ ግንኙነት ተባባሪ ዳይሬክተር

ማኅበራዊ ከስድስት ሚሊዮን በላይ ሕፃናት ለከፋ ረሃብና ለተመጣጠነ የምግብ ዕጦት መጋለጣቸው ተነገረ

ከስድስት ሚሊዮን በላይ ሕፃናት ለከፋ ረሃብና ለተመጣጠነ የምግብ ዕጦት መጋለጣቸው ተነገረ

አበበ ፍቅር

ቀን:

January 28, 2024

በኢትዮጵያ ከስድስት ሚሊዮን በላይ ሕፃናት ለከፋ ረሃብና የተመጣጠነ የምግብ ዕጦት መጋለጣቸውን፣ ወርልድ ቪዥን ኢትዮጵያ የተሰኘ ግብረ ሰናይ ድርጅት አስታወቀ።

 ድርጅቱ በከፋ ችግር ውስጥ ናቸው ያላቸውን ሕፃናት ለመርዳትና ካሉበት ችግር ለማውጣት የሚያስችል ዘመቻ ለማድረግ እንቅስቃሴ መጀመሩን፣ ሐሙስ ጥር 16 ቀን 2016 ዓ.ም. ባዘጋጀው ውይይት ነው ያስታወቀው፡፡

ዘመቻው የሕፃናትን ረሃብና ያልተመጣጠነ ምግብ እጥረትን ለመቀነስ ያለመ መሆኑን፣ የወርልድ ቪዥን ኢትዮጵያ የውጭ ግንኙነት ተባባሪ ዳይሬክተር አቶ ካሱ ከበደ ተናግረዋል፡፡

‹‹በቃ›› በሚል መሪ ቃል ይጀመራል የተባለው ዘመቻ የሚካሄደው በወርልድ ቪዥን ኢትዮጵያ ብቻ ሳይሆን፣ የመንግሥትና የሌሎች አጋር ድርጅቶች ዕገዛ እንዳለበት ተባባሪ ዳይሬክተሩ አስታውቀዋል፡፡

በድርቅ፣ በጦርነት፣ እንዲሁም ቀደም ሲል ተከስተው በነበሩ የአንበጣ መንጋና የኮቪድ 19 ወረርሽኝ ሕፃናትን ለከፋ ችግር መጋለጣቸው ተጠቁሟል፡፡

በድርቅ፣ በጦርነትና በመፈናቀል ምክንያት ለረሃብ የተጋለጡ ሕፃናት ቁጥር ከፍተኛ ነው ያሉት አቶ ካሱ፣ ከእነዚህ ውስጥ ስድስት ሚሊዮን ለሚሆኑት ሕፃናት ልዩ ልዩ ድጋፍ ለማድረግ ከመንግሥት ጋር በመሆን የልየታ ሥራ ለማከናወን መዘጋጀታቸውን አብራርተዋል፡፡

ዘመቻው በሁሉም የአገሪቱ አካባቢዎች የሚደረግ መሆኑንና የሦስት ዓመት ቆይታ እንደሚኖረው ተባባሪ ዳይሬክተሩ ገልጸዋል፡፡

ፕሮጀክቱ በቀጣይ ሦስት ዓመታት ለሚያደርገው ድጋፍ 9.3 ሚሊዮን ዶላር በጀት መያዙን አቶ ካሱ ተናግረዋል፡፡

ረሃብ በጠናባቸው አካባቢዎች ቀድሞ በመድረስ ችግሮችን ከመፍታት ባሻገር፣ ሠርተው መለወጥና ከረሃብ መለቀቅ ለሚችሉ ወላጆች የገንዘብ ድጋፍና የብድር አገልግሎት እንደሚሰጥ የተናገሩት ተባባሪ ዳይሬክተሩ፣ ድርቅ በተከሰተባቸው አካባቢዎች ቀድመው እንደሚደርሱ ገልጸዋል፡፡

በድርቅ ምክንያት በብዙ አካባቢዎች ሰዎች እየተቸገሩ ነው ያሉት ተባባሪ ዳይሬክተሩ፣ ድርቅ ብቻ ሳይሆን ግጭቶች ችግር አባባሽ በመሆናቸው ሰዎች መሥራት ካልቻሉ ነገሮች እየተበላሹ ስለሚሄዱ ችግሮቹን በመለየት በትኩረት ሊሠራባቸው ይገባል ብለዋል፡፡

‹‹ዘመቻው አገሪቱ ያለውን ችግር ሊፈታ ይችላል ተብሎ አይታሰብም፡፡ ምክንያቱም ያለው ችግርና ወርልድ ቪዥን የያዘው በጀት አይመጣጠንም፡፡ ነገር ግን ስድስት ሚሊዮን ሕፃናትን ከችግር ማውጣት ትልቅ አበርክቶ ነው፤›› ሲሉ አቶ ካሱ አክለዋል፡፡

ከግብርና ሚኒስቴር፣ ከጤና ጥበቃ ሚኒስቴር፣ ከሴቶች ሕፃናትና ማኅበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር ጋር በጋራ እንደሚሠሩ የተናገሩት ተባባሪ ዳይሬክተሩ ለችግሩ መነሻዎች የተለያዩ በመሆናቸው ሁሉም አካላት ሊረባረቡ እንደሚገባ አሳስበዋል፡፡

በሕፃናት ላይ እየደረሰ ያለው ጉዳት ሰፊ ከመሆኑ አንፃር የብዙ አካላት ርብርብን እንደሚጠይቅ የተናገሩት፣ በሴቶችና ማኅበራዊ ጉዳይ ሚኒስቴር የሕፃናት መብት ሥርዓት ቀረፃ ዴስክ ኃላፊ አቶ በለጠ ዳኜ ናቸው፡፡

በሰሜኑ የአገሪቱ አካባቢ በተከሰቱ ግጭትና ድርቅ ምክንያት በርካታ ሕፃናት ለከፋ ችግር መጋለጣቸውን የተናገሩት ኃላፊው፣ በቁጥር ደረጃ ይኼን ያህል ሕፃናት ለረሃብ ተዳርገዋል ለማለት ጥናት ይጠይቃል ብለዋል፡፡

በተለያዩ አካባቢዎች የሚፈጠሩ የፀጥታ ሥጋቶች በችግር ውስጥ ለሚገኙ ዕርዳታ ፈላጊዎች፣ በወቅቱና በሚፈለገው ፍጥነት ለማድረስ ፈተና እንደሆነባቸው አቶ በለጠ አስረድተዋል፡፡

ተፈጥሮአዊና ሰው ሠራሽ ችግሮች ሲከሰቱ የመጀመሪያዎቹ ተጎጂዎች ሕፃናት፣ ሴቶችና አረጋውያን ናቸው ያሉት ኃላፊው ለዚህ ደግሞ በተለያዩ የተፈናቃይ መጠለያ ጣቢያዎች ያሉ የኅብረተሰብ ክፍሎችን ማየት ችግሩ በማን ላይ እንደሚጎላ ያሳያል ሲሉ ገልጸዋል፡፡