

ዓለምጣሊያን ከአፍሪካውያን ጋር ለመተግበር ያቀደችው ‹‹ማቲ ፕላን››
አፍሪካውያን መሪዎችና የልዑካን ቡድናቸው በጣሊያን ሮም የተካሄደውን የጣሊያን አፍሪካ ጉባዔ ለሁለት ቀናት ታድመዋል፡፡ጥር 19 እና 20 ቀን 2016 ዓ.ም. በተከናወነውና በ‹‹ማቲ ፕላን›› ላይ ባተኮረው ጉባዔም፣ ከ50 በላይ የአፍሪካ መሪዎች፣ ልዑካን ቡድናቸውና የአውሮፓ ኅብረት መሪዎች ተሳትፈውበታል፡፡

ጣሊያን ከአፍሪካ ጋር ያላትን ስትራቴጂክ ግንኙነት ለመከለስ ባለመው ጉባዔም ትኩረት የተሰጠው፣ ጣሊያን ከአፍሪካ አገሮች ጋር በትብብር ለመሥራት ያቀደችው ‹‹ማቲ ፕላን›› ነው፡፡
እ.ኤ.አ. በ1950ዎቹ ጣሊያን የሰሜን አፍሪካ አገሮች ኢኮኖሚያቸውንና የተፈጥሮ ሀብታቸውን ያበለፅጉ ዘንድ፣ በጣሊያናዊው የሕዝብ አስተዳደር ባለሙያ፣ የንግድ ሰው፣ የፖለቲካ ተፅዕኖ ፈጣሪ ባለሙያና የአገሪቱ ነዳጅ ሀብት ባለሥልጣን በነበረው ኤኔሪኮ ማቲ የተዋወቀውን ‹‹ማቲ ፕላን›› ይዘው ብቅ ያሉት፣ የጣሊያኗ ጠቅላይ ሚኒስትር ጆርጂያ ሜሎኒ ናቸው፡፡ ዕቅዱንም ትብብርን የሚያፋጥንና ‹‹አንዱ አንዱን የማይበላበት›› ሲሉ ይገልጹታል፡፡ዕቅዱን የጣሊያን የውጭ ግንኙነት ፖሊሲ አክሊል እንደ ሆነና፣ የአፍሪካ ጣሊያን ግንኙነትን ለማደስ እንደሚያስችልም እምነት ጥለውበታል፡፡ጣሊያን ከተመረጡ የአፍሪካ አገሮች ጋር ለአራት ዓመታት ለመተግበር ላቀደቻቸውና የዕርዳታ ዓይነት ሳይሆን፣ ሁለቱንም ወገን ተጠቃሚ ያደርጋሉ ለተባሉ ፕሮጀክቶች የሚተገብሩበት ‹‹ማቲ ፕላን››፣ በዓመት ሦስት ቢሊዮን ዩሮ የሚያስወጣ ነው፡፡ለመነሻ ያህልም ጣሊያን 5.5 ቢሊዮን ዩሮ ፈንድ የምታደርግ መሆኑንና ከዚህ ውስጥ ለኃይል አቅርቦት፣ ለግብርና፣ ለውኃ፣ ለጤናና ለትምህርት ዘርፎች ፕሮጀክቶች በብድር መልክ እንደሚሰጥ ጠቅላይ ሚኒስትሯ ሜሎኒ፣ ከአፍሪካ መሪዎች ጋር በመከሩበት ወቅት አሳውቀዋል፡፡የኃይል አቅርቦት ትብብር ላይም የሚያተኩረውና ከዚሁ ጎን ለጎን ጤና፣ ትምህርትና ሌሎች ዘርፎችንም የሚነካው ዕቅድ፣ ዋና ዓላማውን ከአፍሪካ ለሚነሳውና በርካቶች በገፍ ለሚያደርጉት ስደት፣ መሠረታዊ ምክንያት የሆነውን ኢኮኖሚያዊ ችግር ማቃለል አድርጓል፡፡መሠረተ ልማት፣ ባህል፣ የምግብ ዋስትናና የሙያ ሥልጠና የተካተተበት ዕቅድ፣ በአፍሪካ ኢንቨስትመንትን ማጠናከርንም ይመለከታል፡፡በ2022 ሥልጣን የያዙት ሜሎኒ፣ በፀረ ስደተኛ አቋማቸው ይታወቃሉ፡፡፡ ጣሊያንንም እንደ ዕቅዱ አበልፃጊ ማቲ፣ አፍሪካንና አውሮፓን የምታገናኝ ቁልፍ አገር ይሏታል፡፡ ‹‹የአፍሪካና አውሮፓን ፍላጎት የሚያስጠብቅ ስትራቴጂ እንዲኖር ከፈለግን፣ ለምሳሌ በኃይል አቅርቦት ላይ አብረን መሥራት አለብን፤›› ይላሉ፡፡አፍሪካ ከፍተኛ የኃይል አቅርቦት ሀብት እንዳላት፣ በአውሮፓ ደግሞ የአቅርቦት ችግር እንዳለ በመጠቆምም፣ በሁለቱም ወገን ጥቅም ሊያስገኝ የሚችል አሠራር መዘርጋት አለበት የሚለውንም አጽንኦት ይሰጡታል፡፡ትብብሮች በዕርዳታ መልክ ሳይሆን፣ ሁለቱንም ወገን ተጠቃሚ በሚያደርጉ ኢንቨስትመንቶች ዙሪያ መሆን አለባቸው የሚል ዓላማ ያለውን ዕቅድ ይዛ ወደ አፍሪካ አገሮች ዳግም የመጣችውና ግንኙነቷን ማጠናከር እንደምትፈልግ ያሳወቀችው ጣሊያን፣ 40 በመቶ ያህል የጋዝ ፍላጎቷን የምታሟላው ከአፍሪካ ነው፡፡ሆኖም በሳህልና በሰሜን አፍሪካ እየጨመረ የመጣውን አለመረጋጋትና የውጭ አገሮች ጣልቃ ገብነት የምታይበት መንገድ ግዴለሽነት የተሞላበት እንደሆነ አፍሪካ ኒውስ አሥፍሯል፡፡ጣሊያን የምታስተናግዳቸው 80 በመቶ ያህል ኢመደበኛ ጉዞዎች ከሰሜን አፍሪካ ወደቦች የሚነሱ ቢሆንም፣ ስደትን ለመቅረፍ ከአፍሪካ አገሮች ጋር ያላት ትብበር ውጤታማ አይደለም፡፡ በመሆኑም ከአፍሪካ አገሮች ጋር ያላትን ግንኙነት ማጠናከር ትፈልጋለች፡፡ከ70 ዓመታት በፊት ዕቅዱን የነደፈው ኤኔሪኮ ማቲ፣ አፍሪካን የወደፊት የምሥራቅና የምዕራብ አገሮች የጦር ሜዳ ሲል ተንብዮላት ነበር፡፡ይህ ትንበያ በተወሰነ መልኩ ዕውን ሆኗል፡፡ ከሱዳን እስከ ማሊ ሩሲያ ያላት ተደማጭነት ጨምራል፡፡ ቻይና በቤልት ኤንድ ሮድ ኢንሺዬቲቯ በአኅጉሪቱ ላይ ያሳደረችው ተፅዕኖም ከባድ ነው፡፡ጣሊያንም ሆነች ምዕራባውያን በአፍሪካ ተጠቃሚነት ላይ ባተኮሩ ኢንቨስትመንቶች ወይም ፍትሐዊ ትብብር ላይ ከማተኮር ይልቅ በዕርዳታ ላይ ማተኮራቸውም ዋጋ አስከፍሏቸዋል፡፡ አፍሪካ የዓለም ኃያላን የሆኑት ቻይና፣ ሩሲያና ህንድ አጀንዳቸውን እያስፋፉባት የምትገኝ አኅጉር ስትሆን፣ አሜሪካ፣ የአውሮፓ ኅብረትና ሌሎችም ከአፍሪካ ጋር ያላቸውን ግንኙነት ለማጠናከር ጉባዔዎችን ሲያካሂዱ ከርመዋል፡፡ጣሊያንም የቀደመውን የአፍሪካና የጣሊያን ግንኙነት መልሳ ለማደስና እኩል ተጠቃሚነት ላይ በማተኮር ከዚሁ ጎራ ተሠልፋለች፡፡የጣሊያን-አፍሪካን ጉባዔ የታደሙት የአፍሪካ ኅብረት ኮሚሽን ሊቀመንበር ሙሳ ፋኪ መሐመት፣ በዕቅዱ ዙሪያ አፍሪካውያን ቅድሚያ የሚሰጧቸው ጉዳዮች እንዲካተቱ ቀድሞ ምክክር ቢደርግ ይመኙ እንደነበር ገልጸዋል፡፡ ከዚህ ቀደም በበርካታ አገሮች የተገቡ ቃሎች በቃላቸው መሠረት እንዳልተፈጸሙ በመጥቀስም፣ ከቃላት ባለፈ ወደ ተግባር እንዲለወጥ ጥሪ አቅርበዋል፡፡በጉባዔው ከአፍሪካ ኢትዮጵያ፣ ኤርትራ፣ ኬንያ፣ ሶማሊያ፣ ሞሪታንያ፣ ሞዛምቢክ፣ ዚምባብዌ፣ አልጄሪያ፣ ቻድ፣ ግብፅና ሌሎችም ከ25 በላይ የአገር መሪዎችና ተወካዮቻቸው ተሳትፈዋል፡፡