መርዓዊ ከተማ በከፊል
የምስሉ መግለጫ,መርዓዊ ከተማ በከፊል

2 የካቲት 2024, 15:05 EAT

በአማራ ክልል በአዲሱ ሰሜን ጎጃም ዞን መርዓዊ ከተማ ሰኞ፣ ጥር 20/2016 ዓ.ም በተፈጸመ ጥቃት ከ50 በላይ ሰዎች መገደላቸውን ቤተሰቦች፣ ነዋሪዎች አና የዐይን እማኞች ለቢቢሲ ተናገሩ።

ከክልሉ ዋና ከተማ ከባሕር ዳር በ35 ኪሎ ሜትር ገደማ ርቀት ላይ በምትገኘው መርዓዊ ከተማ በመከላከያ ሠራዊት እና በፋኖ ታጣቂዎች መካከል የተደረገ ውጊያን ተከትሎ በነዋሪዎች ላይ በተፈጸመ ጥቃት፣ በርካታ ሰዎች መገደላቸውን ቢቢሲ ያነጋገራቸው ነዋሪዎች ገልጸዋል።

የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን (ኢሰመኮ) ባሕር ዳር ቢሮ በመርዓዊ ከተማ በንጹሃን ላይ ጥቃት እንደደረሰ ከተለያዩ ምንጮች መረጃው እንደደረሰው፣ ክትትል እና ምርመራም እያከናወነ መሆኑን ለቢቢሲ ገልጿል።

ክስተቱን ተከትሎ ባለፉት ቀናት የሆስፒታል ምንጭን ጨምሮ አምስት ሰዎችን ቢቢሲ ያነጋገረ ሲሆን፣ አብዛኞቹ ነዋሪዎች ግድያው የተፈጸመው በቤታቸው እና በመንገድ ላይ በተገኙ ሰላማዊ ሰዎች ላይ መሆኑን ተናግረዋል።

ሰኞ ጥር 20/2016 ዓ.ም. ከጥቃቱ ቀደም ብሎ ከማለዳው 12 ሰዓት ጀምሮ በመከላከያ ሠራዊት እና በፋኖ ኃይሎች መካከል “ከባድ ውጊያ” እንደነበር የሚናገሩት ነዋሪዎች፣ ያንን ተከትሎ ከ50 እስከ 100 የሚደርሱ ሰዎች “ተረሽነዋል” ብለዋል።

ይህ ጥቃት የተፈጸመው ረፋድ አምስት ሰዓት አካባቢ የፋኖ ኃይሎች ከተማዋን ለቅቀው መውጣታቸውን ተከትሎ “መከላከያ ሠራዊት ቤት ለቤት በመዞር እና መንገድ ላይ ያገኛቸውን ሰዎች መረሸኑን” የተናገሩት የዐይን እማኞች፤ ጥቃቱ እስከ ምሽት አንድ ሰዓት የዘለቀ ነበር ብለዋል።

በቀን ሥራ ይተዳደር የነበረ የአራት ልጆች አባት የሆነ ወንድማቸው እንደተገደለባቸው የሚናገሩ ነዋሪ “መጀመሪያ እኔ ቤት መጥተው ሲፈትሹ ‘የቤተ-ክርስትያን ሰው ነኝ’ ስላቸው ወጥተው ሄዱ። ቀጥለው ወንድሜ ቤት ገብተው ይዘውት ሄዱ።”

ወንድማቸው ለጥያቄ ተወስዶ ይመለሳል ብለው እየጠበቁ የነበሩት ነዋሪ፣ ከሌሎች ጋር በሰደፍ እና በቆመጥ እየተደበደቡ ሲወሰዱ እና ሲገድሏቸው መመልከታቸውን ገልጸዋል።

“አንዱን ልጅ በአምስት ጥይት እዚያው ሰፈራችን ኮብሉ ላይ ገድለው ጣሉት። እነሱን [ወንድማቸውንና ሌሎች ሰዎችን] ደግሞ ሰብስበው አንድ ላይ 13 ሰዎች ወደ አስፓልት ይዘው ወጥተው ገደሏቸው። …ፊታችን ስለገደሏቸው ነው ያመንነው” ብለዋል።

ይህንኑ ክስተት በተመለከተ አንድ የህክምና ባለሙያ 13ቱ ሰዎች ከአስፓልት ዳር መገደላቸውን እንደሚያውቁ ለቢቢሲ አረጋግጠው፣ በአጠቃላይ በከተማዋ ውስጥ በዚያ ዕለት 85 ሰዎች መገደላቸውን ተናግረዋል።

ሌላ ስማቸውን መጥቀስ ያልፈለጉ እና ታናሽ ወንድማቸው እንደተገደለባቸው የሚናገሩት የመንግሥት ሠራተኛ ወንድማቸው ከልጁ እቅፍ ተነጥሎ ተወስዶ “በጭካኔ ተረሽኖብኛል” ብለዋል።

“ወንድሜን ልጁን ይዞ ከተቀመጠበት ቤቱ ተወስዶ ነው የተገደለው። ባለቤቱ ‘ህጻኑን ተቀበይ ተብዬ ተገደድኩ፤ ህጻኑን ተቀበልኩት።…ዐይኔ እያየ ነው ግንባሩ ብለው መንገድ ላይ የገደሉት። አብሮት የነበረውንም ጓደኛውን ገድለውታል’ ብላ ነግራኛለች።”

ከወንድማቸው ባሻገርም በዕለቱ መንገድ ላይ 50 የሚሆኑ ሰዎችን አስከሬን መመልከታቸውን ተናግረዋል። ሆኖም “በየመንገዱ እና በየጥሻው” በርካታ ሰው ሳይገደሉ እንዳልቀረ ገምተዋል።

ሌላ የዐይን እማኝ ደግሞ በበርካታ ቀብሮች ላይ መገኘታቸውን ጠቅሰው የሟቾችን ቁጥር ከ100 በላይ አድርገዋል።

ጥቃቱ በተፈጸመ ማግስት ጥር 21/2016 ዓ.ም. ጠዋት ላይ 48 አስከሬን መቆጠራቸውን የሚናገሩ የመርዓዊ ከተማ ነዋሪ፤ “ከማርዘነብ ሆቴል እስከ በረድ ወንዝ ድረስ ግራ እና ቀኝ አስከሬን ብቻ ነበር” ብለዋል።

የሟቾችን ቁጥር 115 ገደማ የሚያደርሱ አንድ የዐይን እማኝ መከላከያ ከተማዋን ከተቆጣጠረ በኋላ ስታዲየም እና ጤና ጣቢያ በተባሉ ሰፈሮች “ከስድስት ዓመት ህጻን እስከ 75 ዓመት አዛውንት” ድረስ ግድያ ተፈጽሟል ይላሉ።

የሆስፒታል ሠራተኛ የሆኑት የዐይን እማኝ በከተማዋ የመጀመሪያ ደረጃ ሆስፒታል የስድስት ወር ነፍሰ ጡርን ጨምሮ 25 ሰዎች ቆስለው መጥተው “የተረፈ የለም” ይላሉ።

“24ቱ ሆስፒታል የመጡት ሞተው ነው። አንዲት የስድስት ወር ነፍሰ ጡር ሴት ከነ ነፍሷ መጥታ ሆስፒታል እንደደረሰች አርፋለች። አጠቃላይ 25 ነበር የመጡት” ብለዋል።

መከላከያ ሠራዊት ከቤት ለቤት አሰሳው ባሻገር የአብነት ተማሪዎችን ጨምሮ መንገድ ላይ የተገኙ ሰዎችን እና የቀን ሠራተኞችን “በበቀል አንበርክኮ” ረሸኗል ሲሉ ነዋሪዎች፣ ቤተሰቦች እና የዐይን እማኞች ተናግረዋል።

በከተማዋ ውስጥ በሁለት ስፍራ ላይ ሰፍሮ ከሚገኘው የመከላከያ ሠራዊት አባላት መካከል በከተማዋ አስተዳደር ህንጻ ውስጥ በነበሩት ላይ የፋኖ ታጣቂዎች ሰኞ ጠዋት ለፈጸሙት ድንገተኛ ጥቃት ምላሽ የተወሰደ “የበቀል እርምጃ” ለበርካታ ሰዎች ግድያ ምክንያት መሆኑን ነዋሪዎች ተናግረዋል።

“ፋኖን አሳድራችኋል፤ ያስጠቃችሁን እናንተ ናችሁ፤ ፋኖን ትቀልባላችሁ” እያሉ “እየዛቱ” ነበር ያሉ አንድ ቤታቸው የተፈተሸ ነዋሪ፤ “ከመሞት መሰንበት” ብለን ዝም አልን ሲሉ ጥቃቱ የበቀል ነበር ብለዋል።

በርካታ ሰዎች በተለያዩ ቦታዎች ላይ ተገድለው ተጥለው በመቆየታቸው ዘግናኝ ሁኔታ መመልከታቸውን ነዋሪዎች ለቢቢሲ ገልጸው “የተገደሉ ሰዎች አስከሬንን ለመለየት እንኳ አስቸጋሪ ነበር” ይላሉ።

“አብዛኛው ሰው በአለባበሱ፣ በሰውነት ቅርጹ ነበር የሚለየው። አስከሬኖች በጥይት ክፉኛ ከመበሳሳታቸው በተጨማሪ፣ ማንሳት አይቻልም ተብሎ አንድ ቀን አሳድረዋቸዋል” ያሉ አንድ እማኝ መለየት አስቸጋሪ በመሆኑ በጅምላ ቀብር እንደተፈጸመ ለቢቢሲ ተናግረዋል።

“እንደ ባህሉ እና ሥርዓቱ ለተገደሉት ሰዎች ተገቢው ቀብር አልተፈጸመም” ያሉት ነዋሪዎች፤ ሐዘን መቀመጥ እና ለቅሶ መድረስ አይታሰብም በማለት “የተፈጸመው ከግፍም በላይ ግፍ” ሲሉ ጥቃቱን ገልጸውታል።

በመከላከያ ሠራዊት እና በፋኖ ታጣቂዎች መካከል በተካሄደው ውግያ በአካባቢው ሁለት አብያተ ክርስቲያናት “በከባድ መሳሪያ ጉዳት ደርሶባቸዋል” የተባለ ሲሆን፣ የግል ንብረቶች እና 15 የሚሆኑ ባለ ሦስት እግር ተሽከርካሪዎች (ባጃጅ) ሆን ተብለው እንዲቃጠሉ መደረጋቸውን ነዋሪዎች ገልጸዋል።

ይህ በርካታ ሰዎች በተገደሉበት ጥቃት በከተማዋ በደማቅ ሁኔታ በየዓመቱ ጥር 21 የሚከበረው የማርያም ንግስ በዓል ዋዜማ በመከሰቱ ምክንያት ከተማዋ በሐዘን ተውጣ በዓሉ እንዳልተከበረም ነዋሪዎቹ አክለው ተናግረዋል።

ጥቃቱ ከተፈጸመ አምስት ቀን ያለፈው ቢሆንም አሁንም ከተማዋ በእጅጉ መቀዝቀዟን የሚናገሩት ነዋሪዎች፣ ባንኮች እና የንግድ ተቋማት ዝግ በመሆናቸው “እንቅስቃሴ የለም” ብለዋል።

ከክልሉ እና ከዞኑ መስተዳደር እንዲሁም ከአካባቢው ኮማንድ ፖስት ስለክስተቱ ማብራሪያ እና ምላሽ ለማግኘት ቢቢሲ ያደረገው ጥረት አልተሳካም።

በአማራ ክልል የተለያዩ አካበቢዎች ካለፈው ዓመት ጀምሮ በመንግሥት ኃይሎች እና በፋኖ ታጣቂዎች መካከል በሚካሄደው ግጭት በሰላማዊ ሰዎች ላይ ጉዳት እየደረሰ መሆኑን ከዚህ በፊት መዘገባችን ይታወሳል።

የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን (ኢሰመኮ) ጥቅምት 19/2016 ዓ.ም. ባወጣው ከሐምሌ ወር 2015 ዓ.ም. ጀምሮ በአማራ ክልል በሁሉም ዞኖች ውስጥ በተለያየ ደረጃ እና ጊዜ የትጥቅ ግጭት መካሄዱን ገልጾ በዚህም ሳቢያ በርካታ ሲቪሎች እንደተገደሉ እና የአካል ጉዳት እንደደረሰባቸው አመልክቶ ነበር።