

በብሔራዊ የግብርና ባዮ ቴክኖሎጂ ምርምር ማዕከል በዘረ መል ምሕንድስና የተገኘው የእንሰት ዝርያ ችግኞች የፍተሻ ምርምር ክፍል ውስጥ
ማኅበራዊ እንሰት አውዳሚ በሽታን በአዲስ የዘረመል ምሕንድስና ዝርያ ማጥፋት መቻሉ ተገለጸ
ቀን: February 4, 2024
ብሔራዊ የግብርና ባዮ ቴክኖሎጂ ምርምር ማዕከል ‹‹አጠውልግ›› በሚል ስያሜ ለሚታወቀው የእንሰት ተክልን ሙሉ ለሙሉ ለምግብ እንዳይውል ከጥቅም ውጭ የሚያደርገውን በሽታ፣ በዘረመል ምሕንድስና ባገኘው አዲስ ዝርያ ማጥፋት መቻሉን አስታወቀ፡፡
በኢትዮጵያ ግብርና ምርምር ተቋም በዘርፉ ተመራማሪ በነበሩት ዳኛቸው ይርጉ (ዶ/ር) በ1968 ዓ.ም. ተክሉን ውስጡን አሞቅሙቆ የሚያበላሸው የባይክቴሪያ ዓይነት ተለይቶ መታወቁን ተናግረዋል፡፡
ተጠሪነቱ ለተቋሙ የሆነው በኦሮሚያ ክልል ሆለታ ከተማ የሚገኘው የባዮ ቴክኖሎጂ ምርምር ማዕከል የእንሰት ተክል በሽታን ሙሉ ለሙሉ መቋቋምና መከላከል የሚያስችለውን ዘረመል፣ በተለምዶ ‹‹የፈረንጅ ቃሪያ›› በሚል መጠሪያ ከሚታወቀው ተክል ተለይቶና ተመርጦ ከተወሰደ የዘረመል ክፍል ጋር በማዳቀል፣ በበሽታው የማይጠቃ የእንሰት ዓይነት መፍጠር መቻሉ ተነግሯል።
የዘረመል ምሕንድስና ግኝቱ ባለቤት የሆኑት ተመራማሪው አቶ ኢብሳ ፊጤ በሽታው በደቡብ ኢትዮጵያ ጉራጌ፣ ዳውሮና ሲዳማ አካባቢዎች የተከሰተውን ድርቅ እንዲባባስ ካደረጉት ዋነኛ ምክንያቶች መካከል እንደሆነ ጠቁመዋል።
ከኢትዮጵያ ሕዝብ ሃያ በመቶው ማለትም ከ20 ሚሊዮን በላይ፣ በተለይም በደቡብና ደቡብ ምዕራብ የአገሪቱ አካባቢዎች የሚኖሩ ሰዎች እንሰት ዋነኛ የምግብ ምንጫቸው መሆኑን ጥናቶች ያሳያሉ።
የምርምር ማዕከሉ በዘረመል ምሕንድስና የሚፈጥራቸውን አዳዲስ የሰብል ዝርያዎች በአርሶ አደሮች ጥቅም ላይ እንዲውል ከመፈቀዱ በፊት፣ በኢትዮጵያ የአካባቢ ጥበቃ ባለሥልጣን ቁጥጥር እየተደረገበት ተገምግሞ በየደረጃው ፈቃድ እየተሰጠው የሚቀጥልበት ሦስት ደረጃዎች እንዳሉ የኢትዮጵያ የደኅንነተ ሕይወት ማሻሻያ አዋጅ (Bio Safety Proclamation) ድንጋጌ ያሳያል።
የመጀመሪያው ደረጃ በቤተ ሙከራ ምሕንድስናው በሚከናወንበት ዝርያና ተለይቶና ተመርጦ ስለሚዳቀለው ዘረመል ምርምር ይካሄዳል፡፡ በመቀጠል አዲስ የተገኘው ዝርያ በታቀበና በተወሰነ የምርምር አካባቢ ተተክሎ ዝርያው ጥራቱ የተሻለ፣ ደኅንነቱ የተጠበቀና የመጀመሪያ ዝርያ ባህሪውን ያለቀቀ መሆኑ ይጠናል፡፡ ይህም ማስቀጠል የሚያስችል አዎንታዊ ውጤት ካስመዘገበ በአካባቢ ጥበቃ ባለሥልጣንና በጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት ሥር ባለው ብሔራዊ ባዮ ሴፍቲ አማካሪ ኮሚቴ በኩል ተገምግሞ ሲፈቀድለት፣ ወደ ታቀበ ፍተሻ ማድረጊያ ምርምር ክፍል ቀጥሎም ወደ መስክ ፍተሻ ያመራል።
አጠውልግ በሽታን የሚቋቋመው አዲሱ ዝርያ ግምገማዎቹን አልፎ በቀጣይ መኸር ወቅት ከግንቦት ወር ጀምሮ በሆለታና በሐዋሳ የመስክ ፍተሻ ለማካሄድ ዝግጅታቸውን እያጠናቀቁ መሆኑን፣ የምርምር ማዕከሉ ዋና ኃላፊ ለታ ቱሉ (ዶ/ር) ገልጸዋል።
በአሁን ወቅትም በታቀበና በተዘጋ የምርምር አካባቢ የእንሰት ዝርያው ተተክሎ የሚገኝ መሆኑን ሪፖርተር ተመልክቷል።
በሌላ በኩል ማዕከሉ በቡና ላይ በሚያደርገው ምርምር ለአገሪቱ አርሶ አደሮች በብዛት ለማዳረስ አስቸጋሪ ነው የተባለውን የቡና ዲቃላ (Coffee Hybrid) ዝርያ በቤተ ሙከራ በፍጥነት በማባዛት፣ ከቤተ ሙከራ ወጥቶ በአርሶ አደሮች ማሳ ላይ የምርት ውጤታማነቱን ለመፈተሽ በሆለታ ከተማ አካባቢ ለሚገኙ ሦስት ወረዳዎች አርሶ አደሮች ስለአጠቃቀሙና መከተል ስለሚያስፈልጉ የእንክብካቤ ሒደቶች ሥልጠና እየተሰጠ መሆኑም ተጠቅሷል።
ለታ (ዶ/ር)፣ ‹‹በአርሶ አደሮች ጥቅም ላይ ከዋለው የቡና ዲቃላ ቅጠል ላይ ቁርጥራጮችን በመውሰድና በቤተ ሙከራ በፍጥነት በማሳደግ በአጭር ጊዜ ውስጥ ዘሩን በብዛት ለማባዛት የሚያስችሉ አሠራሮችን ተጠቅመን ውጤት ተገኝቷል፤›› ብለዋል። የምርምሩ ዋና ዓላማ የቡና ዘር በአርሶ አደሩ በሚፈለገው ልክ የሚተከል ብዛት ያለው ችግኝ ማቅረብ መቻል እንደሆነ አብራርተዋል።
‹‹በየዓመቱ አዲስ የቡና ዲቃላ ዘር እንደ አዲስ ተባዝቶ ነው ለአርሶ አደር መቅረብ ያለበት፡፡ ዲቃላ ስለሆነ ዘንድሮ የተባዛውን ችግኝ በቀጣይ ዓመት መተከል አይችልም፡፡ የምርቱ መጠን በሰፊው ይቀንሳል። በመደበኛ ምርምር በተፈለገው መጠን የየዓመቱን አዲስ ችግኝ በብዛት ማድረስ አይቻልም፡፡ በቤተ ሙከራ ግን በባዮ ቴክኖሎጂ በፍጥነት ይደርሳል ብለዋል።
የማዕከሉ ተመራማሪ አቶ ኢብሳ በበኩላቸው የቡና ቁርጥራጮቹ በቤተ ሙከራ ውስጥ በፍጥነት ለማደግ በሚያስችላቸው በትንንሽ ብልቃጦች ውስጥ በሚደረግ ሰው ሠራሽ ኬሚካል ድብልቅ ውስጥ እንዲተከሉ ከተደረገ በኋላ፣ በሌላ የቤተ ሙከራ ክፍል ተክሉ የሚያስፈልገውን ዓይነት የአየር ሁኔታና ሰው ሠራሽ የፀሐይ ብርሃን (UV light) በቀን ለ16 ሰዓታት እንዲያገኝ በማድረግ ተክሉን በችግኝ መትከያ በተፈጥሮ አፈር ውስጥ ጨምሮ ለማፍላት የሚያስችለው ሥር እንዲያወጣ ከተደረገ በኋላ፣ ከቤተ ሙከራ ወደ ታቀበ ፍተሻ ምርምር ክፍል እንደሚዘዋወር አስረድተዋል።
‹‹የተክሉ ችግኝ ዕድገት ሒደቱ በተፈጥሯዊው መንገድ ጊዜውን ጠብቆ በማፍላት ለአርሶ አደሩ ዘሩ ይዳረስ ቢባል እጥረት ይፈጠራል፤›› ሲሉ አቶ ኢብሳ ገልጸዋል፡፡