EthiopianReporter.com 

ዜና አቶ አብነት ገብረ መስቀል በሼህ አል አሙዲ ላይ ያቀረቡት የ153.66 ሚሊዮን ብር…

ታምሩ ጽጌ

ቀን: February 4, 2024

ሼክ መሐመድ ሁሴን አል አሙዲ የክብር እንግዶች የሆኑትን ከፍተኛ የመንግሥት ባለሥልጣናትን ጨምሮ ዘመዶቻቸው፣ ጓደኞቻቸውና የተለያዩ ግለሰቦች ለሕክምና ወደ አሜሪካ ሲላኩ፣ በቪአይፒ ደረጃ ስለሚላኩ ለሊሞዚን፣ ለሴኪዩሪቲ፣ ለምግብና ለኪስ ገንዘብ የሚሰጡት እሳቸው መሆኑን ጠቅሰው፣ ሦስት ሚሊዮን ዶላር ወይም 153,600,000 ብር እንዲከፈላቸው በፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ያቀረቡት የፍትሐ ብሔር ክስ ወድቅ ተደረገ፡፡

አቶ አብነት ገብረ መስቀል በሼህ አል አሙዲ ላይ ያቀረቡት የ153.66 ሚሊዮን ብር ክስ ውድቅ ተደረገ | Ethiopian Reporter | ሪፖርተር

የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ፍትሐ ብሔር ችሎት ባለፈው ሐሙስ ጥር 22 ቀን 2016 ዓ.ም. ፍርድ የሰጠው አቶ አብነት ያቀረቧቸውን አራት የሰው ምስከሮችና የሰነድ ማስረጃዎችን መርምሮና ከሕግ ጋር አገናዝቦ መሆኑን የፍርድ መዝገቡ ያስረዳል፡፡

የፍርድ መዝገቡ እንደሚያስረዳው፣ አቶ አብነት ከሼክ መሐመድ በ2006 ዓ.ም. 12 የተዘረዘሩ የውክልና ተግባራትን እንዲፈጽሙ የውክልና ውል ተሰጥቷቸዋል፡፡

አቶ አብነት የውክልና ሥልጣኑ የተሰጣቸው በፍትሐ ብሔር ሕግ ቁጥር ጥር 2199 እና 2205(2) ድንጋጌና ሙሉ ውክልና ነው፡፡ በመሆኑም በውክልና ሰነዱ ለአቶ አብነት እጅግ ሰፊና በርካታ ሥልጣን እንደሰጣቸው በመግለጽ፣ ሼክ መሐመድን በመወከል ሰኔ 17 ቀን 2013 ዓ.ም.፣ የሼክ መሀመድ ዕዳ የሚከፈልበትን ሁኔታ ለማረጋገጥ አቶ አብነት ምንም እንኳን የውክልና ሥልጣን ቢኖራቸውም፣ ቀደም ብሎ የነበራቸውን የብድር ውልና የአከፋፈል ስምምነት የማሻሻል (Novation) ሥልጣን በሼክ መሐመድ በኩል የተደረገ ውልም ሆነ ስምምነት አለመኖሩ ተገልጿል፡፡

አቶ አብነት ሰኔ 17 ቀን 2013 ዓ.ም. በፌዴራል የሰነዶች ምዝገባና ማረጋገጫ ኤጀንሲ የመተማመኛ ውል እንደፈጽሙ ቢገለጽና እማኞች ባሉበት እንደተደረገ ቢነገርም፣ በሰነዱ ላይ ምስክርሮቹ እንዳልተገለጹና ፊርማም እንዳላኖሩ ፍርዱ ያብራራል፡፡

አቶ አብነት ሼክ መሐመድን ባለዕዳ ለማድረግና ቀደም ብሎ በ2006 ዓ.ም. የተሰጣቸውን ውል በፍትሐ ብሔር ሥነ ሥርዓት ሕግ ቁጥር 2205 (2) ድንጋጌ መሠረት ለማድረግ ውል ለመለወጥ (Novation) ሥልጣን እንደሌላቸው ፍርዱ ይገልጻል፡፡

አቶ አብነት ግን በ2006 ዓ.ም. ሼክ መሐመድ የሰጧቸው የውክልና ውል የፍትሐ ብሔር  ሥነ ሥርዓት ሕግ ቁጥር 2199 እና 2255 (2) ድንጋጌን መሠረት ያደረገ ውክልና እንደተሰጣቸው በማንሳት፣ የሼክ መሐመድ ዕዳን ለመክፈልም ሆነ ገንዘብ ለመቀበል እንዲሁም ውል ለመፈራረምና ሌሎች በውክልናው የተሰጡ መብቶችን ለመፈጸም፣ የተሰጣቸው ውክልና በቂ መሆኑን በመዝርዘር የቀረበባቸው ተቃውሞ ትክክል አለመሆኑን መግለጻቸውን ፍርዱ ያብራራል፡፡

በጠበቃ የተከወሉት ሼክ መሐመድ በክርክራቸው ያብራሩት ሼክ መሐመድ ከአቶ አብነት ገንዘብ አለመበደራቸውን ነው፡፡ ይህንን ያሉት ደግሞ አቶ አብነት ወደ አሜሪካ ለሚጓዙት የሼክ መሐመድ የክብር እንግዶች ሁሉን ነገር ክፍያ እንዲፈጽሙ ትዕዛዝ የሰጧቸውና ያወጡት ወጪ እንደሚከተለው መናገራቸውን በማስመልከት ነው፡፡  

በአጠቃላይ አቶ አብነት ሼክ መሐመድ አዘዋቸው ወይም እንዲከፍሉ (ወጪ እንዲያደርጉ) ነግረዋቸው፣ ከላይ የተጠቀሰውን ገንዘብ ያህል ወጪ ማውጣታቸው ተገቢ እንዳልሆነና በበቂ ማስረጃ ያልተደገፈ መሆኑን መግለጻቸውን ፍርዱ ያብራራል፡፡

አቶ አብነት በሰነዶች ምዝገባና ማረጋገጫ የፈጸሙት ውል፣ ‹‹የዕዳ መተማመኛ ሰነድ›› መሆኑና ይህም ከሼክ መሐመድ የክብር እንግዶች በተጨማሪ፣ በኢትዮጵያ ውስጥ ካላቸው ድርጅቶች ወደ አሜሪካ አገር ለተለያዩ ሥራ ለሚሄዱ ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎች፣ ባለሙያዎችና ሌሎች ለሆቴል፣ ለትራንስፖርት፣ ለሕክምና፣ ለትምህርትና ለተለያዩ ወጪዎች የተከፈለ መሆኑን ፍርዱ ያብራራል፡፡

ፍርዱ እንደሚያስረዳው፣ በአሜሪካን ከሚገኙ የተለያዩ ባንኮች ወጪ ተደርጎ ክፍያ የተፈጸመ መሆኑን አቶ አብነት በክሳቸው ላይ ዘርዝረው ቢያቀርቡም፣ ፍርድ ቤቱ በያዘው የምርመራ ጭብጥ ያንን የሚያረጋግጥ ማስረጃ አለማግኘቱን ፍርዱ ያብራራል፡፡

የፍርድ ቤቱ ሰኔ 17 ቀን 2013 ዓ.ም. የገንዘብ ዕዳ አከፋፈል በሚል የተደረገው ውል ነው ወይስ የገንዘብ አከፋፈል መተማመኛ ሰነድ ነው? አቶ አብነት የገንዘብ አከፋፈል ውል የፈረሙት ከከሳሽ ባላቸው የውክልና ሥልጣን ገደብ ውስጥ ነው አይደለም? የጥቅም ግጭት አለ ወይስ የለም? ውሉ ሊፈርስ ይገባል ወይስ አይገባም? አቶ አብነት ከፍለዋል ከተባለ ለእነማን ከፈሉ? ለምን ዓላማ ተከፈለ? ወዘተ የሚሉ ጭብጦችን ይዞ ፍርድ ቤቱ ክሱን መርመሩን ፍርዱ ያብራራል፡፡

ፍርድ ቤቱ ምስክሮች አሉኝ ያሉትን የአቶ አብነትን ምስክሮች የሰማ ሲሆን፣ የመጀመሪያ ምስክር የአቶ አብነት ወንድም ሲሆኑ፣ አቶ አብነት ለሼክ መሐመድ የክብር እንግዶች በአሜሪካ ላወጡት ወጪ መተማመኛ የሰነድ ዕውቅና እንዲሰጥላቸው ጥያቄ ማቅረባቸውንና ወጪ ማውጣታቸውን መስክረዋል፡፡

ሁለተኛው ምስክርም አሜሪካ አገር እንደሚኖሩና አቶ አብነት በሚልኩላቸው ገንዘብ ለሼክ መሐመድ የክብር እንግዶች እንደሚከፍሉ፣ ሦስተኛና አራተኛውም ምስክሮቹ ተመሳሳይነት ያለው ምስክርነት መስጠታቸውን ፍረዱ ያብራራል፡፡  

ፍርድ ቤቱ አጠቃላይ የተያዙ ጭብጦችን በዝርዝር ከመረመረ በኋላ፣ አቶ አብነት በ2006 ዓ.ም. ከሼክ መሐመድ የተሰጣቸውን ውክልና የሥልጣን ገደብ እንዳለውና በሰነዶች ማረጋገጫና ምዝገባ ሰኔ 17 ቀን 2013 ዓ.ም. ያደረጉት ማሻሻያ ተቀባይነት እንደሌለው፣ የገንዘብ ዕዳ አከፋፈል መተማመኛ ውል እንደማይባል ፍርድ ሰጥቷል፡፡

አቶ አብነት ውሉን የፈጸሙት ከራሳቸው ወንድም ጋር በመሆኑ (ውክልና የሰጡት) በፍትሐ ብሔር ሥነ ሥርዓት ሕግ ቁጥር 2287፣ 2288 እና 2233 መሠረት ውሉ ፈራሽ መሆኑን ፍርዱ ያብራራል፡፡

ፍርድ ቤቱ ዘርዘር ያለ ፍርድ የሰጠ ሲሆን፣ በአጠቃላይ አቶ አብነት ለሼክ መሐመድ የክብር እንግዶች በአሜሪካ አገር 153,660,000 ብር እንደከፈሉና በሰነዶች ምዝገባ ማረጋገጫ በኩል የመተማመኛ ሰነድ መፈራረማቸውን ቢገልጹም፣ ፍርድ ቤቱ በሰውም ሆነ በሰነድ የተፈራረሙበት ሰነድ ወይም ምስክርነት በሰጡት ሰዎች ማረጋገጥ አለመቻሉን በመግለጽ፣ የአቶ አብነትን ክስ በሙሉ ድምፅ ውድቅ ማድረጉን በፍርዱ አስታውቋል፡፡