የሲአይኤቲ ተመራማሪ አቶ ስንታየሁ ዓለማየሁ

ማኅበራዊ ድርቅ ከመከሰቱ በፊት ቅድመ ትንበያ የሚሰጥ ድረ ገጽ ይፋ ተደረገ

ሰላማዊት መንገሻ

ቀን: February 7, 2024

በድርቅ ምክንያት እየተጎዱ ያሉትን አርብቶ አደሮች ችግር ለመቅረፍ የሚረዳ ድርቅ ከመከሰቱ በፊት ቅድመ ትንበያ የሚሰጥ ድረ ገጽ ይፋ ሆነ፡፡

የ‹‹እንስሳት ቅድመ ማስጠንቀቂያ መረጃ ሥርዓት›› ድረ ገጽ ከአንድ ዓመት በፊት በቢልና ሜሊንዳ ጌትስ ፋውንዴሽን የገንዘብ ድጋፍ አማካይነት የተጀመረ ፕሮጀክት ሲሆን፣ ጥር 27 ቀን 2016 ዓ.ም. በሃያት ሪጀንሲ ሆቴል የፕሮጀክቱ ማስጀመሪያ ፕሮግራም ተካሂዷል፡፡

በዕለቱ ከመንግሥት ተቋማት፣ ከልማት አጋሮች፣ ከቦረና ዞን የማኅበረሰብ አቀፍ አመራሮች፣ ከምርምር ተቋማት፣ ከአካዴሚክና ከግሉ ዘርፍ የተውጣጡ ተወካዮች በተገኙበት የድረ ገጹ ጠቀሜታና አጠቃቀም ላይ ሰፊ ማብራሪያ ተሰጥቷል፡፡

በአሊያንስ ኦፍ ባዮቨርሲቲ ኢንተርናሽናልና ሲአይኤቲ የሚመራው ከግብርና ሚኒስቴርና ከኢትዮጵያ ግብርና ምርምር ኢንስቲትዩት ጋር በመተባበር፣ ከአንድ ዓመት በፊት በተጀመረ ፕሮጀክት ሥር የተሠራ ድረ ገጽ መሆኑን፣ የሲአይኤቲ ተመራማሪ አቶ ስንታየሁ ዓለማየሁ ተናግረዋል፡፡

የ‹‹እንስሳት ቅድመ ማስጠንቀቂያ መረጃ ሥርዓት›› በኢንተርኔት፣ በጽሑፍ መልዕክትና በቴሌቪዥን መረጃው የሚሠራጭበት መንገድ ነው ብለዋል፡፡

ፕሮጀክቱ የርቀት ዳሰሳና የአየር ሁኔታ መረጃን በመጠቀም የእንስሳትን ውኃ አቅርቦት የሚከታተል፣ በአካባቢው ድርቅ የመከሰት አደጋ ከመድረሱ በፊት ትንበያ የሚሰጥ በድረ ገጽ ላይ የተመሠረተ የውሳኔ ሰጪ መሣሪያ መሆኑን አቶ ስንታየሁ ተናግረዋል።

የፕሮጀክቱ ዋና ዓላማ አርብቶ አደሩ ሲጠቀምበት የነበረውን ባህላዊ የትንበያ ዘዴን በማሻሻል፣ የውኃ ሀብትና አቅርቦት መረጃን ለመሰብሰብና ለማሠራጨት የሚረዳ ነው ብለዋል፡፡

የድረ ገጽ አተገባበሩን ወደ መሬት በማውረድ የግብርና ሚኒስቴር ከፍተኛ ሚና የሚጫወት በመሆኑ፣ በቅድሚያ ተግባራዊ የሚደረገው ቦረና ውስጥ ሲሆን፣ በቀጣይ ወደ ሶማሌና አፋር አካባቢዎች የማስፋፋት ዕቅድ መያዙን አቶ ስንታየሁ ተናግረዋል፡፡

ኢትዮጵያ በአፍሪካ ትልቁ የእንስሳት ሀብት ያላት አገር በመሆኗ፣ የእንስሳቱን ደኅንነት በመጠበቅ ለአርብቶ አደሩ የገቢ ምንጭ ሊሆኑ እንደሚገባ አቶ ስንታየሁ አስረድተዋል፡፡

በርካታ እንስሳት ባሉባቸው አካባቢዎች የሚገኙ አርብቶ አደሮች፣ ወቅታዊ መረጃን በተለይም በየወረዳዎቻቸው በሚገኙ የውኃ ጉድጓድ የውኃ መጠን ማግኘት ባለመቻላቸው ችግሩን ለመቅረፍ የተሠራ ፕሮጀክት ነው ብለዋል፡፡

አርብቶ አደሩ ወቅታዊ መረጃ ባለማግኘቱ በተደጋጋሚ ድርቅን ለመቋቋም ያለውን አቅም እንዲቀንስ እያደረገ እንደሚገኝ አቶ ስንታየሁ ተናግረዋል፡፡

በሚሊዮን የሚቆጠሩ አርብቶ አደሮች ሙሉ በሙሉ መተዳደሪያቸው በእንስሳት ላይ ጥገኛ በመሆኑ፣ ያልታሰበ ድርቅ በሚከሰትበት ወቅት በምግብ ዕጦትና በረሃብ ምክንያት ኑሯቸው ሥጋት ላይ እንዳይወድቅ ያለመ ፕሮጀክት መሆኑን ገልጸዋል፡፡