EthiopianReporter.com 

ማኅበራዊ የሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶች ባለሥልጣን የ477 ድርጅቶችን ፈቃድ እንደሚሰርዝ አስታወቀ

ሰላማዊት መንገሻ

ቀን: February 11, 2024

የሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶች ባለሥልጣን የሁለት ዓመታት የኦዲት ሪፖርት ማቅረብ ያልቻሉ 477 የሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶችን ፈቃድ እንደሚሰርዝ አስታወቀ፡፡

ባለሥልጣኑ ጥር 29 ቀን 2016 ዓ.ም. ይፋ ባደረገው ደብዳቤ መሠረት፣ ህልውናቸውን ባላረጋገጡ የሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶች ላይ ማብራሪያ ሰጥቷል፡፡

የኦዲት ሪፖርት ያላቀረቡ ድርጅቶች እንዲያቀርቡ፣ ወይም በተለያዩ ምክንያቶች ሳይሠሩ ከቆዩ ያልሠሩበትን ምክንያት እንዲያሳውቁ ባለሥልጣኑ ማስጠንቀቂያ መስጠቱን ገልጿል፡፡

የሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶቹ በባለሥልጣኑ በጋዜጣ ማስታወቂያ በወጣላቸው 30 ቀናት ውስጥ፣ ህልውና ካላቸው ተወካዮቻቸው እንዲቀርቡና ሪፖርት ያልቀረበበትን ምክንያት እንዲያስረዱ በደብዳቤ ገልጾላቸው እንደነበር አስታውቋል፡፡

የአንድ ሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅት ተወካይ በተሰጠው ጊዜ ውስጥ ቀርቦ ድርጅቱ ሪፖርት ያላደረገበትን በቂ ምክንያት ካላቀረበ፣ የባለሥልጣኑ ዋና ዳይሬክተር ጉዳዩን ለቦርዱ አቅርቦ ድርጅቱ እንዲፈርስና ፈቃዱ እንዲሰረዝ ውሳኔ እንደሚተላለፍ በደብዳቤው ተብራርቷል።

በዚህም መሠረት ባለሥልጣን መሥሪያ ቤቱ ሁለት ጊዜ ጥሪ አቅርቦ ከ805 ህልውናቸውን ካላረጋገጡ ድርጅቶች 328 ድርጅቶች ቀርበው ምክንያታቸውን ያስረዱ መሆናቸውን፣ ቀሪዎቹ 477 ድርጅቶች ምክንያታቸውን ማቅረብ ባለመቻላቸው ፈቃዳቸው እንደሚሰረዝ በደብዳቤው ተገልጿል፡፡

ድርጅቶቹ በአብዛኛው ሪፖርት ያላቀረቡበት ምክንያት በአገሪቱ በተለያዩ አካባቢዎች ባለው የፀጥታ ችግርና በፈንድ እጥረት መሆኑን በመግለጻቸው፣ የሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅቶች ባለሥልጣን ምክንያታቸውን በመቀበል ሪፖርት ባላቀረቡት ድርጅቶች ላይ በሕጉ መሠረት ለቦርድ አቅርቦ እንዲፈርሱ እንደሚደረግ ተመልክቷል፡፡

ማንኛውም የሲቪል ማኅበረሰብ ድርጅት በአዋጅ 1113/2011 አንቀጽ 70 መሠረት ሪፖርት ለማቅረብ የተቀመጠው የጊዜ ገደብ ባለፈ በሦስት ወራት ውስጥ ሪፖርት ካላቀረበ፣ ባለሥልጣኑ የድርጅቱን ህልውና ለማረጋገጥ በጋዜጣ ጥሪ ያደርጋል።

በአዋጁ መሠረት ባለሥልጣኑ በ2012 እና በ2013 ዓ.ም. ሪፖርት ማቅረብ ሲገባቸው ያላቀረቡትን ድርጅቶች ሚያዝያ 4 ቀን 2015 ዓ.ም. በአዲስ ዘመን ጋዜጣ ማስታወቂያ አውጥቶ ሪፖርት ያላቀረቡበትን ምክንያት እንዲገልጹ ቢያስታውቅም፣ ቀርበው ያስረዱት በጣም ጥቂቶች መሆናቸውን ደብዳቤው ይገልጻል፡፡

ባለሥልጣኑ ታኅሳስ 18 ቀን 2016 ዓ.ም. በጻፈው የመጨረሻ የማስጠንቀቂያ ደብዳቤ በ15 ቀናት ውስጥ ድርጅቱ ሪፖርት ያላቀረቡበት ምክንያት ቀርበው እንዲያስረዱ በማስታወቅ፣ ምክንያታቸውን ያላቀረቡ ድርጅቶች እንዲፈርሱ የሚያደርግ መሆኑን መግለጹ ይታወሳል፡፡