በ128ኛው የዓድዋ ድል በዓል”የተከለከለ ልብስ ለብሳችኋል” በሚል በርካቶች ወጣቶች እየታሠሩ ነው – አዲስ ማለዳ

128ኛው የዓድዋ ድል በዓል የአደረንጓዴ ቢጫና ቀይ፣ የምኒሊክ እና የእቴጌ ጣይቱ ምስል ያለበት ልብስ ለብሳችኋል በሚል በርካቶች ወጣቶች ታስረዋል።
እንዲሁም ከነዚህ ልብሶች በተጨማሪም “የፋኖ ልብስ ነው” የለበሳችሁት በሚል የታሰሩ መኖራቸውን ለአዲስ ማለዳ ከአንድ ፖሊስ ጣቢያ የታሰሩ ሰዎች ሰምታለች።
ለ128ኛው የዓድዋ ድል በዓል ለማክበር የተሰበሰቡ ወጣቶች ወደ ምንሊክ አደባባይ ሲጓዙ “ትፈለጋላቹ” በሚል በፖሊስ ተይዘው በአዲሱ ገበያ ወረዳ ስምንት ፖሊስ ጣቢያ ተወስደዋል።
በአንድ ቦታ ላይ “ሀምሳ አካባቢ እንሆናለን። ዝም ብለው አስቀምጠውናል። አንድ በአንድ አስገብተው እየመረመሩ ነው” ሲል አንድ ወጣት ለአዲስ ማለዳ ገልጿል። ሌሎችንም እያመጡ እየጨመሩ ነውም ተብሏል።
ከአዲሱ ገበያ በተጨማሪ ጊዮርጊስ እና ሌሎች አካባቢዎች በሚገኙ ፖሊስ ጣቢያዎችም የታሰሩ መኖራቸውና እንዲሁም ይህ ዘገባ እስከወጣበት ሰዓት ድረስ እስር እንደቀጠለ ምንጮች ገልጸዋል።

ወደ ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን እንጂ ወደ ምንሊክ ሃውልት ማለፍ እንደማይቻል እና ወደ አደባባዩ የሚወስዱ መንገዶች ላይ የፀጥታ ኃይሎች ጥብቅ ፍተሻ እያደረጉ እንደነበር አዲስ ማለዳ በስፍራው ተገኝታ ተመልክታለች።
የድል በዓሉ ከዚህ ቀደም ይከበርበት ከነበር የምኒሊክ ሃውልት ጋር ሳይከበር በመቅረቱ በርካቶች ቅሬታቸውን ሲያንፀባርቁም አዲስ ማለዳ ታዝባለች።ለዚህም ከተለያየ አካባቢ በዓሉን ለመታደም በቡድን በመሆን ተመሳሳይ ልብስ በማሰራት በስፍራው ይገኙ የነበሩ ታዳሚዎች ቁጥር ከዚህ ቀደሙ መቀነሱ አይነተኛ ማሳያ ነው።
መከላከያ ሚንስቴር ያዘጋጀው የአድዋ ድል በዓል በአድዋ ድል መታሰቢያ ሙዝየም የተከረ ሲሆን፤ በርካታ ታዳሚዎች ‘አድዋ’ የሚል ጽሁፍ በጥቁር ቀለም ከጦርና ጋሻ ምስል ጋር ያለበት ቲሸርት ለብሰው እንደነበር አዲስ ማለዳ ተመልክታለች።