

የኢሠማኮ ፕሬዚዳንት የመሩት ልዑክ ከጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ አህመድ (ዶ/ር) ጋር ባለፈው ዓመት ውይይት ባደረገበት ወቅት
ዜና ኢሠማኮ ለመንግሥት ሠራተኞች የደመወዝ ወለል ማስተካከያና የግብር ቅነሳ ጥያቄ እንደገና እንደሚያቀርብ አስታወቀ
ቀን: March 13, 2024
የኢትዮጵያ ሠራተኛ ማኅበራት ኮንፌዴሬሽን (ኢሠማኮ) የመንግሥት ሠራተኞች ዝቅተኛ የደመወዝ ወለል ማስተካከልና የግብር ቅነሳን በተመለከተ ያቀረበው ጥያቄ አዎንታዊ ምላሽ ካላገኘ፣ እንደገና ለጠቅላይ ሚኒስትሩ ደብዳቤ እንደሚያስገባ አስታወቀ፡፡
ኢሠማኮ ዝቅተኛ የደመወዝ ወለል መጠን እንዲወሰንና በሠራተኞች ላይ የተጫነው ግብር እንዲቀነስ፣ ነሐሴ 24 ቀን 2015 ዓ.ም. ለጠቅላይ ሚኒስትሩ ጥያቄ ማቅረቡ ይታወሳል፡፡
የኢሠማኮ ምክትል ፕሬዚዳንት አቶ አያሌው አህመድ ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ ጠቅላይ ሚኒስትሩ የችግሩን ክብደት ተመልክተው በአጭር ጊዜ ውስጥ ምላሽ ይሰጣሉ ተብሎ ቢጠበቅም በተለያዩ ችግሮች ምክንያት ምላሻቸው ዘግይቷል፡፡
በሠራተኞች ላይ የተጫነው ግብር እንዲቀንስ ኢሠማኮ ለገንዘብ ሚኒስቴር ደብዳቤ መላኩን ገልጸው፣ ዝቅተኛ የደመወዝ ወለል ጉዳይ የሚመለከተው የሥራና የክህሎት ሚኒስቴር ስለሆነ ከተቋሙ ጋር በየጊዜው ውይይት እየተደረገ መሆኑን አስረድተዋል፡፡
ኢሠማኮ ባለፈው ዓመት በጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት በተደረገ ውይይት ጥያቄውን ለጠቅላይ ሚኒስትሩ ሲያቀርብ፣ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ሙሉ ለሙሉ የቤት ሥራውን ለፍትሕ ሚኒስቴር መስጠታቸውን አቶ አያሌው አስታውቀዋል፡፡
በዚህ መሠረት ኢሠማኮ የፍትሕ ሚኒስቴርን ስለጉዳዩ ሲጠይቅ፣ ጉዳዩ የግብር በመሆኑ ከጠቅላይ ሚኒስትሩ ጋር በመነጋገር ለገንዘብ ሚኒስቴር እንዲተላለፍ ማድረጉን አክለዋል፡፡
የመንግሥት ሠራተኞች ዝቅተኛ የደመወዝ ወለልና የግብር ቅነሳን በተመለከተ ለቀረበው ጥያቄ አዎንታዊ ምላሽ ካልተገኘ፣ እንደገና ከጠቅላይ ሚኒስትሩ ጋር ለመነጋገር ኢሠማኮ ደብዳቤ የሚያስባ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡
የሠራተኞች ዝቅተኛ የደመወዝ ወለልና የግብር ቅነሳ ጥያቄ እንደ ቀላል ነገር የሚታይ እንዳልሆነ ጠቅሰው፣ ጥያቄው መቼ ይፈታል የሚለው ጉዳይ ግን ጊዜ የሚጠይቅ ነው ብለዋል፡፡
‹‹የሠራተኞች ዝቅተኛ የደመወዝ ወለልንና የግብር ቅነሳን ጥያቄ ለመመለስ፣ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ለሥራና ክህሎት ሚኒስቴር፣ ለፍትሕ ሚኒስቴር፣ ለገንዘብ ሚኒስቴርና ለሌሎች ተቋማት ጉዳዩን ዓይተው እንዲያቀርቡላቸው ኃላፊነት ሰጥተዋል፤›› ሲሉም አስረድተዋል፡፡
የሠራተኞች ዝቅተኛ የደመወዝ ወለልና የግብር ቅነሳ ጥናት የሚጠይቅ እንደሆነ የተናገሩት ምክትል ፕሬዚዳንቱ፣ ጉዳዩን በተመለከተ ከአማካሪ ቦርድ ጋር አንድ ጊዜ መወያየታቸውን አስረድተዋል፡፡
በአማካሪ ቦርዱ ውስጥ የተካተቱት ከአሠሪ፣ ከሠራተኛና ከመንግሥት የተውጣጡ መሆናቸውን ገልጸው ኢሠማኮ የችግሩን ጥልቀት ስለሚያውቅ አስቸኳይ ምላሽ ለማግኘት ይሠል ሲሉ አቶ አያሌው ተናግረዋል፡፡
ከዚህ በፊት በጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት በተካሄደው ውይይት ላይ የሥራና ክህሎት ሚኒስትሯ ወ/ሮ ሙፈሪያት ካሚል፣ የፍትሕ ሚኒስትሩ ጌዴዮን ጢሞቲዎስ (ዶ/ር)፣ የኢሠማኮ ፕሬዚዳንት አቶ ካሳሁን ፎሎና ሌሎች ኃላፊዎች ተገኝተው እንደነበር አይዘነጋም፡፡