EthiopianReporter.com


ዜና
የፌዴራል ቤቶች ኮርፖሬሽን ተተኪ ቦታ ሳይሰጠው 980 ቤቶች እንደፈረሱበት ተገለጸ

ሰላማዊት መንገሻ

ቀን: March 20, 2024

የፌዴራል ቤቶች ኮርፖሬሽን የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ተተኪ መሬት ሳይሰጠው 980 የሚጠጉ ቤቶች እንዳፈረሱበት ተገለጸ፡፡

የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት 18ኛ መደበኛ ስብሰባውን ማክሰኞ መጋቢት 9 ቀን 2016 ሲያደርግ አቶ ፈይድ ሸራብ የተባሉ የምክር ቤት አባል እንደገለጹት፣ የኮርፖሬሽኑ ንብረት የነበሩትን ቤቶች የከተማ አስተዳደሩ ካፈረሰ በኋላ፣ ተጨማሪ ለመገንባት የሚያስችል ተተኪ መሬት አለመሰጠቱን ገልጸዋል፡፡

ለፈረሱት ቤቶች የተከፈለው የካሳ ክፍያም ቢሆን በጣም አነስተኛ መሆኑን አቶ ፈይድ ጠቁመው፣ ኮርፖሬሽኑ ለደንበኞቹ ከ300 ብር እስከ አንድ ሺሕ ብር ድረስ በማከራየት ገቢ የሚያገኝባቸው ቤቶች እንደነበሩ አስረድተዋል፡፡

የኢንቨስትመንት ሆልዲንግ እያስተዳደራቸው ከሚገኙ የልማት ድርጅቶች መካከል አንዱ ኮርፖሬሽኑ ስለሆነ፣ እንዲህ ዓይነት ተቋማት እንዴት መስተናገድ እንዳለባቸው ግልጽ መደረግ አለበት ሲሉ አሳስበዋል፡፡

ለሕዝብ ጥቅም ሲባል የመሬት ይዞታ የሚለቀቅበት፣ ካሳ የሚከፈልበትና ተነሺዎች መልሰው የሚቋቋሙበትን ሁኔታ ለመወሰን የወጣውን አዋጅ ቁጥር 1161/2011 ለማሻሻል የወጣውን ረቂቅ አዋጅ ማብራሪያ እንዲመለከቱ የተላከላቸው የከተማ መሠረተ ልማትና ትራንስፖርት ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ፣ እንዲሁም የሕግና ፍትሕ ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ እንዲህ ዓይነት ተቋማት የሚስተናገዱበትን አሠራር እንዲመለከቱም ጠይቀዋል፡፡

የረቂቅ አዋጁን አስፈላጊነት በተመለከተ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የመንግሥት ዋና ተጠሪ ሚኒስትር አቶ ተስፋዬ በልጅጌ፣ ለምክር ቤት አባላት ማብራሪያ ሲሰጡ፣ ለልማት ተነሺዎች ተገቢ የሆነ የካሳ ክፍያ ለማከናወን እንዲሁም የልማት መጓተት ችግርን ለመፍታት ረቂቁ ይጠቅማል ብለዋል፡፡

ረቂቅ አዋጁ ለሕዝብ ጥቅም ሲባል የመሬት ይዞታ የሚለቀቅበት፣ ካሳ የሚከፈልበትና ተነሺዎች መልሰው የሚቋቋሙበትን አሠራር የሚያቀላጥፍ ስለመሆኑም አብራርተዋል።

የመሠረተ ልማት ሥራዎች ሲከናወኑ የንብረት መገመት፣ የመክፈልና የማስነሳት ሥራ ለክልሎችና ለከተማ አስተዳደሮች የሚሰጥ መሆኑንም ጠቅሰዋል።

የምክር ቤት አባላትም የአዋጁ ማሻሻያ ከመተግበሩ አስቀድሞ ለሕዝቡ የግንዛቤ መፍጠር ሥራ ትኩረት እንዲደረግበት ጠይቀዋል።

በአሠራር ሒደቱ ክልሎችና የከተማ አስተዳደሮች የመክፈል አቅም ውስንነት እንዳያጋጥማቸው፣ ከፌዴራል መንግሥት ጋር በትብብር ቢከናወን ሲሉም አስተያየት ሰጥተዋል።

በተጨማሪም አዋጁ ከመውጣቱ በፊት መስተናገድ የሚገባቸው ተነሺዎች ጉዳይና ሲቀርቡ የነበሩ የካሳ ክፍያ ቅሬታዎች እንዴት እንደሚስተናገዱ ቋሚ ኮሚቴው እንዲመለከተው አባላቱ አሳስበዋል፡፡

ለሕዝብ ጥቅም ሲባል የመሬት ይዞታ የሚለቀቅበት፣ ካሳ የሚከፈልበትና ተነሺዎች የሚቋቋሙበት ለመወሰን የማሻሻያ ረቂቅ አዋጅ 1161/2011 ከአምስት ዓመት በፊት መውጣቱ ይታወሳል፡፡