EthiopianReporter.com 

ማኅበራዊ በኢትዮጵያ 52 በመቶ የሚሆኑ ዜጎች ሕይወት የሚያልፈው ተላላፊ ባልሆኑ በሽታዎች መሆኑ ተገለጸ

በጋዜጣዉ ሪፓርተር

ቀን: March 20, 2024

በየማነ ብርሃኑ

በኢትዮጵያ ከ52 በመቶ በላይ የሚሆኑ ዜጎች ተላላፊ ባልሆኑ በሽታዎች ሕይወታቸውን በማጣት ላይ እንደሚገኙ የቅርብ ጥናቶች ማረጋገጣቸው ተነገረ፡፡

የኢትዮጵያ ጤና አጠባበቅ ማኅበር ከመጋቢት 8 እስከ 10 ቀን 2016 ዓ.ም. ‹‹ሁሉን አቀፍ የጤና ተደራሽነት›› በሚል መሪ ሐሳብ የማኅበሩን 35ኛ ጉባዔ ባካሄደበት ወቅት፣ የጤና ሚኒስትር ደኤታው ደረጀ ድጉማ (ዶ/ር) እንደተናገሩት፣ ተላላፊ ያልሆኑ በሽታዎች በተለይ ስኳር፣ የደም ግፊት፣ ካንሰር፣ የአዕምሮ መታወክ፣ የልብና የኩላሊት በሽታዎች ከየትኛውም ጊዜ በበለጠ ቁጥራቸው እያሻቀበ መሆኑንና በርካታ ዜጎችም እየሞቱ መሆኑን ገልጸዋል፡፡

በአዲስ አበባ የሚገኙ ትልልቅ ሆስፒታሎች፣ ከ80 በመቶ በላይ የሚሆኑት አልጋዎች የሚያዙት ተላላፊ ባልሆኑ በሽታዎች በሚታመሙ ሕሙማን መሆኑንም ሚኒስትር ደኤታው አክለዋል፡፡

እንደ ሚኒስትር ደኤታው ገለጻ፣ ባለፉት ዓመታት ተላላፊ የሆኑ በሽታዎችን በመከላከልና በመቆጣጠር ረገድ ከፍተኛ ስኬት ሊመዘገብ ቢችልም፣ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ግን እንደ  ወባ፣ ቲቪ፣ ኮሌራና ኤችአይቪ ያሉ በሽታዎች በወረርሽኝ መልክ በተለያዩ የአገሪቱ አካባቢዎች በመከሰት ላይ ይገኛሉ፡፡   

ኢትዮጵያ በአሁኑ ወቅት በተለያዩ ችግሮች ውስጥ እያለፈች እንደምትገኝና እነዚህም ችግሮች በጤና ዘርፉ ላይ ጫና እያሳደሩ መሆኑን፣ በሰሜኑ የአገሪቱ ክፍሎች የነበረው ግጭት በርካታ የጤና ተቋማት እንዲወድሙና በተለያዩ የጤና ዘርፎች የተመዘገቡ ውጤቶች ወደኋላ እንዲመለሱ ማድረጉን፣ የጤና ኤክስቴንሽን ፕሮግራሙም በእነዚህ ቦታዎች ከፍተኛ ችግር እንደገጠመው ሚኒስትር ደኤታው ጠቁመው፣ የወደሙና የተጎዱ የጤና መሠረተ ልማቶችን መልሶ በማቋቋምና በማደራጀት በኩል ሥራዎች እየተሠሩ መሆኑን አስረድተዋል፡፡

የገንዘብ አቅም የሌላቸውንና ከፍለው መታከም የማይችሉ የኅብረተሰብ ክፍሎችን የጤና አገልግሎት እንዲያገኙ ለማድረግና ሁሉን አቀፍ የጤና ተደራሽነትን ለማስፋት፣  ማኅረበሰብ አቀፍ የጤና መድኅን ተቋቁሞ በሥራ ላይ እንደሚገኝ የተናገሩት ደረጄ (ዶ/ር)፣ ከ56 ሚሊዮን በላይ የሚሆኑ ዜጎች የማኅረበሰብ አቀፍ የጤና መድኅን አገልግሎት ተጠቃሚ ለመሆን ችለዋል ብለዋል፡፡

እንደ ሚኒስትሩ ገለጻ፣ በተለያዩ የአገሪቱ ክፍሎች የድርቅና የጎርፍ አደጋዎች እንዲሁም ወረርሽኞች ሕፃናትን ለከፍተኛ የምግብ እጥረት እያጋለጡ ይገኛሉ፡፡  ከተለያዩ አካባቢዎች የተፈናቀሉና በልዩ ልዩ የመጠለያ ጣቢያዎች የሚገኙ ወገኖች አስፈላጊውን የጤና አገልግሎት እያገኙ እንዳልሆነ የገለጹት ሚኒስትሩ፣ መሥሪያ ቤታቸው ከተለያዩ አጋር ድርጅቶች ጋር በመሆን በዚህ ዙሪያ ትኩረት ሰጥቶ በመሥራት ላይ እንደሚገኝ ተናግረዋል፡፡