ማኅበራዊ ኮሌራና ኩፍኝን ጨምሮ በወባ የሚሞቱ ሰዎች ቁጥር መጨመሩ አስጊ ሆኗል ተባለ

አሸናፊ እንዳለ

ቀን: March 27, 2024

በወባ፣ በኮሌራና ኩፍኝ ወረርሽኞች የሚሞቱ ሰዎች ቁጥር ከፍ ማለቱና የወረርሽኞቹ መስፋፋት አስጊ ደረጃ ላይ መድረሱ ተገለጸ፡፡

በየካቲት ወር ብቻ 705 ሺሕ ሰዎች በወባ ተይዘው 764 ሰዎች መሞታቸውን በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት (ተመድ) የሰብዓዊ ጉዳዮች ማስተባበሪያ ጽሕፈት ቤት ያወጣው ሪፖርት ያመለክታል፡፡ በአጠቃላይ በወባ የተያዙ ሰዎች ቁጥር 5.2 ሚሊዮን መድረሱና ባለፈው አንድ ወር ብቻ 705,000 ሰዎች መያዛቸውን ሪፖርቱ አትቷል፡፡ የወባ ወረርሽኝ በብዛት የተስፋፋው በኦሮሚያ፣ በአማራ፣ በደቡብ ምዕብራ፣ በጋምቤላና በቤኒሻንጉል ክልሎች መሆኑ ተጠቁሟል፡፡

በኩፍኝ በሽታ የሞቱ ሰዎች ቁጥር ደግሞ በየካቲት ወር ብቻ 30 በመቶ በመጨመር 315 መድረሱን ሪፖርቱ ያመለክታል፡፡ ኩፍኝ በ71 ወረዳዎች የተስፋፋ ሲሆን፣ ከፍተኛ ቁጥር የታየባቸው ኦሮሚያ፣ ደቡብ ምዕራብ፣ ሶማሌና አማራ ክልሎች ናቸው፡፡ በኩፍኝ ከተያዙት 42,000 ሰዎች ግማሾቹ ሕፃናት ናቸው፡፡

ሌላው ከፍተኛ መስፋፋት እያሳየ ያለው ወረርሽኝ ኮሌራ ሲሆን እስካለፈው ወር ድረስ 36,900 ሰዎች ተይዘዋል፡፡ ወረርሽኙ በአፋር፣ በድሬዳዋ፣ በሐረር፣ በኦሮሚያና በሶማሌ እየተስፋፋ መሆኑ ተነግሯል፡፡

የበሽታዎቹ መስፋፋት ባለፉት ስድስት ወራት በከፍተኛ ፍጥነት እየተስፋፋ ሲሆን፣ በዋነኛነት በክትባትና በመድኃኒት እጥረት ምክንያት እንደሆነ ሪፖርቶች ያሳያሉ፡፡ የንፁህ ውኃ እጥረት፣ በቂ ያልሆነ የጤና ዘርፍ በጀትና ያልተለመደና ከጎረቤት አገር የገባ የትንኝና የቆላ ዝንብ ዓይነት ተጠቃሽ ናቸው፡፡ በተለይ በኦሞ ወንዝ አቅራቢያ የሚከሰቱ ወረርሽኞች ለረዥም ዓመታት በመቆየታቸው፣ ክትባት ሊያስወግዳቸው እንዳልቻለ የአካባቢው የጤና ባለሙያዎች ተናግረዋል፡፡

በተለይ የኮሌራ ክትባት መድኃኒት እጥረት በዓለም አቀፍ ደረጃ መከሰቱን በጥቂት ሳምንታት በፊት የወጣው የዓለም ጤና ድርጅት እንዲሁም የኢትዮጵያ የኅብረተሰብ ጤና ኢንስቲትዩት ሪፖርቶች ያሳያሉ፡፡

ኢንስቲትዩቱ ከሦስት ሳምንታት በፊት ያወጣው ሪፖርት እንደሚያሳየው፣ የኮሌራ ወረርሽኝ በ54 ወረዳዎች ውስጥ የተከሰተ ሲሆን፣ ይህም በኦሮሚያ (14 ወረዳዎች)፣ በሶማሌ (28 ወረዳዎች)፣ በድሬዳዋ (ሰባት ወረዳዎች) እና በሐረር ሁለት ወረዳዎች ውስጥ ነው፡፡

የኢንስቲትዩቱ ሪፖርት እንደሚያሳየው፣ በኦሮሚያና በአማራ ባለው የፀጥታ አለመረጋጋት ምክንያት በተለይ ወደ ጉጂ ዞን፣ ቦረናና ቤኒሻንጉል አካባቢ መድኃኒቶችን ማድረስ እንዳልተቻለ ተጠቅሷል፡፡

የበጀትና ፈንድ እጥረት፣ የመረጃ መዘግየት፣ የሎጂስቲክስ ተሽከርካሪዎች እጥረት፣ የዝናብ ወቅቱን አለመጠበቅና የመኖሪያ ቤቶች በጊዜ መድኃኒት አለመርጨት በምክንያትነት በሪፖርቱ ላይ ተዘርዝረዋል፡፡