March 29, 2024

በሕገ ወጥ መንገድ ዜጎችን ማሰር እና ማንገላታት የገዢውን ፓርቲ እንባገነናዊ ፈላጭቆራጭነት ያመለክታል- ኢሕአፓ

(አዲስ ማለዳ) የኢትዮጵያ ሕዝባዊ አብዮታዊ ፓርቲ (ኢሕአፓ) ”በሕገወጥ መንገድ ዜጎችን ማሰር እና ማንገላታት የሚያመለክተው የገዢውን ፓርቲ እየሄደበት ያለውን አንባገነናዊ ፈላጭ ቆራጭነት ባህሪ ነው ሲል አወገዘ።

የኢሕአፓ ሊቀ መንበር ረዳት ፕሮፌሰር ዝናቡ አበራ ከትላንት ወዲያ በፓርቲው ጽህፈት ቤት በስራ ላይ እንዳሉ “በህገ ወጥ” መንገድ በጸጥታ ሀይሎች በቁጥጥር ስር መዋላቸውን ገልጿል።

የኢትዮጵያ ሕዝብ አብዮታዊ ፓርቲ (ኢሕአፓ) ትላንት መጋቢት 19 ቀን 2016 ካወጣው መግለጫ አዲስ ማለዳ እንደተመለከተችው በተመሳሳይ ቀደም ሲል የድርጅቱ ተቀዳሚ ምክትል ሊቀ መንበር “ጦርነት ይቁም ሰላም ይስፈን” የሚል ሰላማዊ ሰልፍ ለማዘጋጀት በመሞከራቸው ለወራት እስር ተዳርገው በቅርቡ መለቀቃቸውን አስታውሷል።

ፓርቲው የኢትዮጵያ መሰረታዊ ችግሮች እንዲፈቱ የሚደረገውን ትግል ለማሰናከል እና “መሪዎቻችን ይፈቱ” በሚል ጥያቄ ዙሪያ እንድንጠመድ አንደኛው አመራር በተፈቱ ሳምንት ባልሞላ ጊዜ ውስጥ ሊቀ መንበሩ መታሰራቸውን ገልጿል።

በመሆኑም በስልጣን ላይ ያለው የብልጽግና ፓርቲ በምክክር እና በውይይት ከአቻ የፖለቲካ ድርጅቶች ጋር የሚሰራ ሳይሆን ከፓርላማ አባላት እስከ ፖለቲካ ድርጅት መሪዎች እንዲሁም የተለያዩ የማህበረሰብ ክፍል አባላትን ማፈንና ማሰር ኢ-ፍትሀዊ በመሆኑ ድርጅቱን እንደሚኮንን ኢሕአፓ አስታዉቋል።