

የግብርና ሚኒስትሩ ግርማ አመንቴ (ዶ/ር)
ማኅበራዊ እንደ አገር ምን ያህል የዘር ብዛትና የሰብል ዓይነት እንደሚያስፈልግ እንደማይታወቅ ግብርና ሚኒስቴር…
ቀን: March 31, 2024
በርካታ የክልል አመራሮች ዘር ትዝ የሚላቸው የዘር ወቅት ሲደርስ በመሆኑ፣ እንደ አገር ምን ያህል የዘር ብዛት በየትኛው የሰብል ዓይነት እንደሚፈለግ እንደማይታወቅ፣ የግብርና ሚኒስትሩ ግርማ አመንቴ (ዶ/ር) አስታወቁ፡፡
በምርጥ ዘር ብዜት አቅርቦትና ሥርጭትን አስመልክቶ በሳምንቱ መጨረሻ አካባቢ ከባለድርሻ አላላት ጋር ውይይት ባደረጉበት ወቅት ሚኒስቴሩ እንደተናገሩት፣ ከ2016 እስከ 2018 ዓ.ም. ባለው ጊዜ ውስጥ ከመካከለኛው ዘመን ከመንግሥት ዕቅድ ጋር ሊጣጣም በሚችል ሁኔታ፣ አሁን ካለው የዘር አቅርቦት በዕጥፍ ለማሳደግ እየተሠራ ነው ብለዋል፡፡
በኢትዮጵያ በሚቀጥሉ ሦስት ዓመታት የስንዴ፣ የበቆሎ፣ የገብስ፣ የጤፍና የማሽላ የሰብል ዓይነቶች ምርጥ ዘር ለማባዛት እየተሠራ መሆኑን አክለዋል፡፡
እነዚህ የሰብል ምርቶች የኢትዮጵያን 87 በመቶ የምግብ ፍላጎት የሚሸፍኑ መሆኑን ጠቅሰው፣ ሚኒስቴሩም በየዓመቱ ሁለት ሚሊዮን ኩንታል ምርጥ ዘር ለመሰብሰብ ዕቅድ ይዞ እየተንቀሳቀሰ እንደሚገኝ አስረድተዋል፡፡
‹‹በተለይ እንደ አገር ምን ያህል የዘር ብዛት፣ የትኛው የሰብል ዓይነት እንደሚፈለግ አይታወቅም፤›› ያሉት ሚኒስትሩ፣ ይህም በዘር ሥርጭት ላይ ክፍተት መፍጠሩን ተናግረዋል፡፡
በዚህ መሠረት ግብርና ሚኒስቴር ይህንን ችግር ለመፍታት ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲና ከሌሎች ባለድርሻ አካላት ጋር በመሆን፣ በአገር አቀፍ ደረጃ ተግባራዊ የሚደረግ የዘር ቋት መረጃን ለመሰብሰብ የተለያዩ አሠራሮችን ዘርግቶ እየሠራ እንደሆነ አብራርተዋል፡፡
ከዚህ በተጨማሪም በምርጥ ዘር ብዜት ላይ ተሠማርተው የሚንቀሳቀሱ ተቋማት መነሻ ዘር ሲፈልጉ ቅድሚያ ምን ማሟላት እንዳለባቸው የሚያሳይ ቅድመ ሁኔታ መዘጋጀቱን ገልጸው፣ ይህንንም ያላሟሉ ድርጅቶች የማይስተናገዱ መሆኑን ተናግረዋል፡፡
በቅርብ ጊዜ የመንግሥትም ሆነ የግል ዘር አባዦችን በሙሉ በመጥራት ዕቅዳቸውን እንዲያቀርቡ መደረጉን ያስታወሱት ሚኒስትሩ፣ አብዛኛዎቹም ይህንን ዕቅድ ማቅረብ መቻላቸውን ጠቁመዋል፡፡
የዘር አባዦቹ ዕቅዳቸውን ሲያቀርቡ እንደ ችግር ያነሱት ክልሎች ለዘር ማባዣ የሚሆን መሬት እያቀረቡልን አይደለም የሚል እንደነበር አስታውቀዋል፡፡
ክልሎች በክልላቸው ውስጥ ያሉትን የዘር አባዦች ዕቅድ መጠየቅ እንዳለባቸውና ይህንንም ለመተግበር ግብርና ሚኒስቴር ሰፊ እንቅስቃሴ የሚያደርግ መሆኑን አስረድተዋል፡፡
የፌዴራል መንግሥትና የክልል መንግሥታት የአገሪቱን የምግብ ዋስትና በዘላቂነት ለማረጋገጥ የአሥር ዓመት ስትራቴጂክ ቀርፀው ወደ ሥራ መግባታቸውን፣ የኢትዮጵያ ግብርና ምርምር ኢንስቲትዩት የቴክ ብዜትና ዘር ምርመር ዳይሬክተር ካርታ ካስኬ (ዶ/ር) ተናግረዋል፡፡
ከዚህ አንፃር በአሥር ዓመቱ መጨረሻ 624 ኩንታል የምግብ እህል ለማምረት ዕቅድ የተያዘ ሲሆን፣ ይህንን ተፈጻሚ ለማድረግ ጥራት ያለው ምርጥ ዘርና ማዳበሪያ ለአርሶ አደሩ ማቅረብ እንደሚያስፈልግ አብራርተዋል፡፡
የዘንድሮ ዓመትን ጨምሮ በቀጣይ ሦስት ዓመታት ውስጥ ስድስት ሚሊዮን ኩንታል ምርጥ ዘር ለማቅረብ መታሰቡንና ከዚህ ውስጥም አምስት ሰብሎችን ለይቶ በመውሰድ ትኩረት ሰጥቶ እየተሠራ መሆኑን አክለው ገልጸዋል፡፡
የኢትዮጵያ የዘር ሥርዓት ውስጥ እንደ ችግር ከሚታዩ ጉዳዮች መካከል አንዱ ዘርፉን በተቀናጀ መንገድ አለመምራት እንደሆነና የዘር ሥርዓቱም ብዙ ባለቤት ስላለው ችግሩ ሊፈጠር መቻሉን አስታውሰዋል፡፡
የዘር ሥርዓቱንም በትክክለኛ መንገድ ለመምራት በፌዴራል ደረጃም ሆነ በክልል ኮሚቴ መዋቀሩን ገልጸው፣ ብዙ ጊዜ በርካታ ዘር አባዦችም እንደ ችግር የሚያነሱት ቅድሚያ መሥራች ዘር እያገኘን አይደለም የሚል ነው ብለዋል፡፡
በአገር አቀፍ ደረጃ በየዓመቱ በአማካይ ከ350 ሺሕ ኩንታል ለዘር ተጠቃሚው የሚያቀርቡ መሆኑን፣ በኢትዮጵያ ግብርና ሥራዎች ኮርፖሬሽን የኢትዮጵያ ምርጥ ዘርና ደን ውጤት አቅርቦት ዘርፍ ሥራ አስፈጻሚ አቶ ዘነበ ወልደ ሥላሴ ተናግረዋል፡፡
ስንዴ፣ በቆሎ፣ ጤፍ፣ ማሽላና ገብስ በጣም ተፈላጊ መሆናቸውን ያስታወሱት ሥራ አስፈጻሚው፣ በኢትዮጵያ ግጭት ያለባቸው ቦታዎች ላይ ዘር ለማቅረብ የተወሰነ መቸገራቸውን አስረድተዋል፡፡
የኢትዮጵያ ግብርና ምርምር ኢንስቲትዩት ከዚህ በፊት በተሰጠው መሬት ልክ እየሠራ ቢሆንም፣ አሁን ያለው የዘር ፍላጎትን ብዙም ማሟላት አለመቻሉን ተናግረዋል፡፡
በሌላ በኩል ክልሎችና ዘር አቅራቢዎች ተናበው መሥራት ላይ ክፍተት እንዳለባቸው ገልጸው፣ አንዳንድ ዘር አባዦችም ድንገት የዘር እጥረት ይገጥመኛል በሚል ፍራቻ የሚያከማቹ መኖራቸውን ጠቁመዋል፡፡