

ዜና አገራዊ የምክክር ውይይቶች በብልፅግና ካድሬዎች የተሞሉ ሆነዋል ሲል ኢዜማ ከሰሰ
ቀን: April 3, 2024
- በጉዳዩ ዙሪያ ለጠቅላይ ሚኒስትሩ ጥያቄ ማቅረቡን አስታውቋል
- ‹‹የአገር አቀፍ የምክክር ውይይቱ ላይ እየተሳተፉ ያሉት የገዥው ፓርቲ አባላት ብቻ ናቸው የሚለው ክስ አልገባኝም››
ጠቅላይ ሚኒስትሩ
የኢትዮጵያ ዜጎች ለማኅበራዊ ፍትሕ (ኢዜማ) ፓርቲ፣ የኢትዮጵያን ውስብስብና ሥር የሰደዱ ችግሮች ይፈታል ተብሎ ተስፋ የተጣለበትን የአገራዊ ምክክር የውይይት መድረኮች ብልፅግና እየዋጠው እንደሆነ አስታወቀ፡፡ ፓርቲው ማክሰኞ መጋቢት 24 ቀን 2016 ዓ.ም. ከጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ አህመድ (ዶ/ር) ጋር የተፎካከሪ ፓርቲዎች ውይይት ሲያደርጉ ለጠቅላይ ሚኒስትሩ ያቀረባቸውን ጥያቄዎች በጽሑፍ ይፋ አድርጓል፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ አህመድ (ዶ/ር) ግን በሰጡት ምላሽ ‹‹የአገር አቀፍ የምክክር ውይይቱ ላይ እየተሳተፉ ያሉት የገዥው ፓርቲ አባላት ብቻ ናቸው የሚለው ክስ አልገባኝም›› ብለዋል፡፡
ለጠቅላይ ሚኒስትሩ ካቀረባቸው ጥያቄዎች አንዱ አገራዊ ምክክር ኮሚሽንን የተመለከተ ጥያቄም እንደሚገኝበት ይፋ አድርጓል፡፡
አገራዊ ምክክሩ እንዲሳካ መንግሥት የአንበሳውን ድርሻ እንደሚጫወት የጠቀሰው የኢዜማ፣ ጥያቄ ይሁን እንጂ የብልፅግና ካድሬዎች የውይይት መድረኮቹን እየሞሉት መሆኑን የሚያብራራ መሆኑን ጠቁሟል፡፡
በተለይ በታችኛው መዋቅር የሚገኙ ሹማምንት በየደረጃው የሚደረገውን ውይይት በብልፅግና ፓርቲ ተወካዮች አብላጫ ተሳትፎ እንዲካሄድ፣ በተለያዩ የኅብረተሰብ ክፍሎች ተሳትፎ ስም የፓርቲ አባላትን እያስገቡ ይገኛል በማለትም ፓርቲው ጥያቄውን ያቀርባል፡፡
ኢዜማ ጥያቄውን ሲቀጥል ይህ ዓይነቱ አሠራር በቀደመው የኢሕአዴግ መንግሥት ወቅት ሲሞከር የቆየና ለማንም የማይጠቅም መሆኑን ያስቀምጣል፡፡ ይህ አካሄድ የምክክር መድረኮቹን በብልፅግና ፓርቲ ተፅዕኖ ሥር እንዲወድቁ ለማድረግ የሚደረግ ጥረት ስለመሆኑም ይገልጻል፡፡
መንግሥት በሚጠራቸው ሠልፎች፣ ስብሰባዎች፣ ውይይቶችና ማንኛውም ከመንግሥት ጋር የሚደረጉ ሕዝባዊ መስተጋብሮች ላይ በተጋባዥነት የሚጠሩት የፓርቲ አደረጃጀት አባላት መሆናቸው የተለመደ ሆኗል ሲል የሚኮንነው ኢዜማ፣ ይህ ደግሞ መንግሥትን ከሕዝብ የሚነጥል ብቻ ሳይሆን በመንግሥትና በገዥው ፓርቲ መካከል የጠራ ድንበር እንዳይኖር ያደረገ ነው ይላል፡፡
አገራዊ ምክክሩ ለአገሪቱ ካለው ተስፋና ፋይዳ አንፃር መንግሥት ይህን ችግር እንዲያርም ኢዜማ ጠይቋል፡፡ ከዚሁ ጋር በማያያዝም አገሪቱ ትገኝበታለች ስላለው የመፍረስ አደጋ፣ ስለሰላምና ደኅንነት ጥያቄዎችን ለጠቅላይ ሚኒስትሩ ማንሳቱን አስታውቋል፡፡
‹‹የአገር አቀፍ የምክክር ውይይቱ ላይ እየተሳተፉ ያሉት የገዥው ፓርቲ አባላት ብቻ ናቸው የሚለው ክስ አልገባኝም ምክንያቱም ውይይቱ ገና አልተጀመረም።›› ሲሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዓብይ አህመድ (ዶ/ር) ለቀረበላቸው ጥያቄ ምላሽ ሰጥተዋል፡፡ የውይይት ሐሳብ እያቀረበ ያለው ብልፅግና ፓርቲ ብቻ ነው ለማለት ከሆነ እናንተም ማቅረብ ትችላላችሁ። ብልፅግና ፓርቲ አገር አቀፍ ምክክሩን በተቻለ መጠን ለማሳካት ሙሉ ቁርጠኝነት ይዞ የገባበት ሥራ እንደሆነ ግን ላረጋግጥላችሁ እችላለሁ። የተቃውሞ ፖለቲካ ሲባል ስንገናኝ መወቃቀስ ከሆነ ወይም በሐሳብ የማንደጋገፍ ከሆነ ትርጉም እንደሌለው ተናግረዋል።
ፕሮፈሰር ብርሃኑ ነጋ ለእኛ ፓርቲ የሚመቹ አይደሉም። እርሳቸው እንዴት ትምህርት ሚኒስቴርን ይመራሉ የሚል ክስ በብልፅግና ፓርቲ አባላት ይቀርብባቸዋል። እውነት ለመናገር በጣም ጥቂት ሚኒስትሮች ናቸው በእሳቸው ልክ ሀብት አሰባስበው ችግር ለመፍታት የሚሞክሩት። በዚህ ሥራቸው እናከብራቸዋለን፣ ለሥራቸው ባላቸው ታማኝነት እናከብራቸዋለን። ስለሚጨቀጭቁን ደግሞ አይመቹንም። ይህንን ሚዛን ጠብቀን ነው እኛ የምንሄደው፣ በማለትም አስረድተዋል፡፡