የአዲስ አበባ ከተማ የፐብሊክ ሰርቪስና የሰው ሀብት ልማት ቢሮ ኃላፊ ጣሰው ገብሬ (ዶ/ር)

ዜና የከተማ አስተዳደሩን የመንግሥት ተቋማት የሥራ ሰዓት ለማራዘም የተጀመረው ጥናት መቆሙ ተሰማ

ተመስገን ተጋፋው

ቀን: April 17, 2024

በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ሥር የሚገኙ የመንግሥት ተቋማት አገልግሎት የሚሰጡበትን ሰዓት ከስምንት ወደ 16 ሰዓት ለማራዘም የተጀመረው ጥናት መቆሙን፣ የከተማው የፐብሊክ ሰርቪስና የሰው ሀብት ልማት ቢሮ አስታወቀ፡፡

ጥናቱ የተጀመረው በከተማ አስተዳደሩ ሥር በሚገኙ የመንግሥት ተቋማት የሚሠሩ ሠራተኞች የግል ገቢ እንዲኖራቸው፣ እንዲሁም የከተማዋን የኢኮኖሚ እንቅስቃሴ ለማነቃቃት ታስቦ መሆኑን ቢሮው ማስታወቁ ይታወሳል፡፡

የከተማው የፐብሊክ ሰርቪስና የሰው ሀብት ልማት ቢሮ ኃላፊ ጣሰው ገብሬ (ዶ/ር) ለሪፖርተር እንደገለጹት፣ ከዚህ በፊት የመንግሥት መሥሪያ ቤቶች የሥራ ሰዓት ለማራዘም የተጀመረው ጥናት ሙሉ ለሙሉ ቆሟል፡፡

የመንግሥት መሥሪያ ቤቶችን የሥራ ሰዓት ለማራዘም መነሻ ጥናት ተደርጎ እንደነበር፣ ይሁን እንጂ በአሁኑ ወቅት ምንም ዓይነት እንቅስቃሴ እንደሌለ አክለው ገልጸዋል፡፡

ኃላፊው በጉዳዩ ላይ  ተጨማሪ ማብራሪያ እንደማይሰጡ ገልጸው፣ ወደፊት የታሰበው አሠራር ተግባራዊ ይደረጋል አይደረግም የሚለውን እንደማያውቁ ተናግረዋል፡፡

ጥናቱ የተጀመረው በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ሥር የሚገኙ መሥሪያ ቤቶችን የሥራ ሰዓት ከጠዋቱ 2፡30 አስቀድሞ ለማስጀመርና ከ11፡30 በኋላ እስከ ምሽት ለማስቀጠል ታቅዶ ነበር፡፡

ዕቅዱ ይፋ የተደረገው የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የፐብሊክ ሰርቪስና የሰው ሀብት ልማት ቢሮ የከተማዋ መሥሪያ ቤቶች አገልግሎት አሰጣጥን አስመልክቶ መሆኑን፣ ቢሮው ግንቦት 3 ቀን 2015 ዓ.ም. ከባለድርሻ አካላት ጋር ባደረገው ውይይት  መግለጹ ይታወሳል፡፡