ተሟገት የኢትዮጵያ የፖለቲካ ትግል በሕግ አምላክ ይላል

አንባቢ

ቀን: April 21, 2024

በገነት ዓለሙ

የአገራችንን ሰላም፣ የመላውን ዓለም ሰላም ጭምር የሚፈታተነውና አደጋ ላይ የጣለው ልዩ ልዩነታችን በጭራሽ አይደለም፡፡ ሕመማችን፣ ጠንቀኛው በሽታችን ራሱ ልዩ ልዩነታችን ቢሆን ኖሮማ የዓለም አቀፋዊ የሰብዓዊ መብታችንና ነፃነታችን ሕጎች በልዩ ልዩነታችን ልክ በነፃ እንድንደራጅ፣ በዚያው ልክ የተለያዩ አመለካከቶችን በነፃነት እንድንገልጽ ባልፈቀዱ፣ ባልደነገጉ፣ ለዚህም ተፈጻሚነት ባልተጉና ባልተዋደቁ ነበር፡፡ የሰላማችን ዋነኛ ደመኛና ጠንቀኛ ጠላት ልዩ ልዩነታችን፣ መለያየታችን ሳይሆን ይህን ልዩ ልዩነት እንወክላለን፣ እንገልጻለን የሚሉ የፖለቲካ ኃይሎች፣ ቡድኖች ትግልና ግብግብም ጭምር ከሕጋዊ፣ ሰላማዊና ዴሞክራሲያዊ መድረክ ግቢ ውጭ መሆኑ ነው፡፡ ጠላታችን ልዩነታችን አይደለም፡፡ ልዩነታችን ላጥፋ ማለትም ጤነኛ መፍትሔ አይደለም፡፡ እንዲያውም የጤናማነት ማረጋገጫችን ልዩነታችን ነው፡፡ በልዩነታችን ላይ የተመሠረተው ትግል ወይም ግብግብ ወይም ‹‹ጦርነት›› ከሰላማዊና ሕጋዊ እንዲያውም ዴሞክራሲያዊ ማዕቀፍ ውጭ ሲሆን ግን አገርንና ሕዝብን ጤና ይነሳል፣ ብሎም የዓለም የራሱ የፀጥታ ጉዳይ ይሆናል፡፡

ተደጋግሞ እንደተነገረውና ከዚህም በላይ ተደጋግሞ መነገር ያለበት ሰላም የሚያሳጣንና ሰላምም የነሳን እንኳንስ ልዩነታችን ራሱ አብሮ ለመሥራት አያስችለንም፣ ልዩነታችን አያኗኑረንም ማለት ቀርቶ ልዩነታችንን ከሰላማዊና ከሕጋዊ ግቢ ውጪ ለመፍታት መሞከር ነው፡፡

በተለይም ደግሞ ለዴሞክራሲ እታገላለሁ፣ ዴሞክራቶች ነን፣ እያሉ በስሙም እየተጠሩና እየማሉ፣ በመረጃና በዕውቅ መከራከርን፣ አለመግባባትን በውይይት ለመፍታት አለመለማመድን ባህልና ወግ አድርጎ ዘራፍ ባይነት ሥልጣኔ ሀክ እንትፍ አድርጎ የጣለው የአረመኔያዊነት ዳር ዳርታው ነው፡፡ የትም ቦታና በየትኛውም መልክ፣ በይፋና በፖለቲካ መድረኮችም ሆነ ከፖለቲካ መለስ ባሉ ጉዳዮችም ከራሳችን የተለየ ሐሳብን ለመስማት ቻይ ሳንሆን፣ የተለየና ከእኛ የሚለይ፣ የሚቃረን ሐሳብን ስለሌላው ወገን መብትና ነፃነት ብሎ ብቻ ሳይሆን፣ የገዛ ራሴም ጥቅም ነው ብሎ ማድመጥና ማቅረብ ባህል ሳይኖር፣ ዴሞክራሲ ቢሉ ዴሞክራሲ ይስቅብናል፡፡ ትግል ከሁሉም በላይ ሕግ ማክበር አለበት፡፡ አዎ ሕጋዊነት ትግል ብለን በየዝነው የድርጊት/የዕርምጃ ዓይነትና ትግሉ በሚካሄድበት አገር ውስጥ በሚገኘው ሕግ ይዘት ልክ የሚወሰን ነው፡፡

በየትኛውም ሁኔታ ቢሆን ግን፣ በተለይም ከመንግሥት ጋር የሚደረገው ትግል ወይም ግብግብ በሕገ መንግሥቱ የተረጋገጡ መብቶች አይረጋገጡ፣ መንግሥታዊ ሕገወጥነት፣ አጥፊነትና ሕግ ረጋጭነት ተጠያቂ ይሁን ከማለት ይጀምራል፡፡ የብዙዎች መከራከሪያ ስለሕጋዊ ትግል የሚወራው መንግሥት ራሱ ሕግ በማያከብርበት አገር ነው ይላል፡፡ የትግሉ መነሻ ከዚህ ይጀምራል፡፡ መንግሥትን ራሱን ሕግህን አክብር፣ ሕገወጥነትን አቁም ብሎ መታገል የጥበብም የትግልም መጀመርያ ነው የሚባለውም ለዚያ ነው፡፡

ከዚህ ውጪ ግን በሚቻለው ስልት ሁሉ፣ በጉልበት፣ በደመ ነውጠኝነት፣ በሸርና በሸፍጥ መንገድ ሁሉ ሰብዓዊ መብቶችን እየጣሱና ንብረት እያወደሙ መታገል ትግል አይደለም፡፡ የትኛውንም ዓይነት ሕገወጥነትና የመብት ረገጣን ያለ አድልኦ (የእኛ፣ የእነሱ ሕገወጥነትና የመብት ረገጣ ሳይል) የሚቃወም የፖለቲካ ዕይታ የሌለው ትግል ደግሞ ትግል አይደለም፡፡

ከሁሉም በላይ ‹‹በሕግ አምላክ›› በማለት የሚታወቅ፣ ‹‹በሕግ አምላክ›› ማለትን ያውቃል፣ እምነቱ አድርጓል በሚባል አገርና ሕዝብ ውስጥ ሕግ አለማክበር፣ ይልቁንም ሕግ መጣስ፣ ከዚያም አልፎና ብሶ ወንጀልን ከቶውንም የትግል ስልት፣ የትግል መንገድ፣ የትግል መሣሪያ ሲያደርጉ ማየትን የመሰለ ሕመምና በሽታ የለም፡፡ ሰላማችንን የነሳን፣ ለሰላማችን ጠንቅ የሆነውም ይኸው ነው፡፡ በተለይም የፖለቲካ ኃይሎች  ግብግብ ከሕጋዊ ግቢውም መሆኑ ነው፡፡

ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ኢትዮጵያ ፖለቲካ ውስጥ የገባ፣ ማንም የሚያውቀው፣ የፕሪቶሪያው ስምምነት ተብሎ የሚጠራ፣ ከሞላ ጎደል ሁሉም የሰላም መሠረት፣ አድርጎ የሚጠቅሰው (ስለስምምነቱ አፈጻጸም፣ አፈጻሙ ላይ ስለደረሰውና ስለሚደርሰው ከመጎሳቆል ጀምሮ አሻጥር፣ ሸር፣ ወዘተ ብዙ ልንነጋገር እንችላለን) ስምምነት ቢያንስ ቢያንስ ግጭትን አስቁሟል፣ በዚያው አካባቢ ጦርነትን አስቀርቷል፡፡ ከእነ ስሙም በሌላ መጠሪያው ‹‹cessation of Hostilities Agreement (CoHA)›› የሚባለው ለዚሁ ነው፡፡ የዚህ ስምምነት ዋናው መሠረት የስምምነቱ አልፋና ኦሜጋ ስምምነቱን የሁሉም ድል፣ የተደራዳሪ ሁለት ወገኖች ሁሉ ድል ብቻ ሳይሆን፣ የሌሎችም የፖለቲካ ኃይሎች ትምሀርትና የጥበብ መጀመርያ  መሆን ያለበት ጉዳይ ስምምነቱ ውስጥ አብሪ ኮከብ ሆኖ የተቀረፀውና ደምቆ ያተስተጋባው አንድ ወሳኝ ጉዳይ፣ የፌዴራላዊ ዴሞክራሲያዊ ኢትዮጵያ ‹‹የመከላከያ ሠራዊት አንድ ብቻ ነው›› ተባብለው የተማማሉበትና የተፈራረሙበት ነገር ነው፡፡ የአገር የፀጥታ ኃይሎች ብቸኛ ሕጋዊ ታጣቂነት፣ በኃይልና በጉልበት ላይ ያለው የመንግሥት የሞኖፖል መብት/ሥልጣን ባይልልኝ እንጂ ከዚያ ሁሉ ዕልቂት በኋላ ከፕሪቶሪያ የሚገኝ ትምህርት ባልሆነ ነበር፡፡

የፕሪቶሪያን ስምምነት የመሰለ ትምህርት ከተገኘ በሰላም ዛሬም ሰላማችንን የሚሳን የፖለቲካ ቡድኖች ግብግብ ከሰላማዊው ግቢ ውጪ መሆኑ ብቻ ሳይሆን፣ የባለጠመንጃ ቡድኖች እዚህም እዚያም እንደ አረም ብቅ ማለት ብቻ ሳይሆን፣ እንዲያውም ከመንግሥት ጋርም ሆነ ከሌላው የፖለቲካ ተፎካካሪ ጋር የሚደረገው የትግል መንግድ ይህንን እከተላለሁ ማለት ነው፡፡ አሳዛኙን ምናልባትም አሳፋሪው ጉዳይ የአንድ አገር መንግሥት የፀጥታ ኃይሎች ብቸኛ ሕጋዊ ታጣቂነት የፖለቲካ መርህ ሕገ መንግሥታዊ ድንጋጌ መሸርሸሩና መጣሱ ብቻ ሳይሆን ተራው ፖለቲከኛም፣ ሕዝቡ ውስጥም ባለጠመንጃ ቡድኖችን የመደገፍ አባዜውን ነውር አለማድረጉ ነው፡፡

ይህ ምናልባት ‹‹ፖለቲካዊ›› ነገር ነው፣ ፖለቲካ ነው፣ ለተራው ሰው የማይገባ ጉዳይ ነው የሚል ሰበብና ማመካኛ ሊሰጠው ይችላል፡፡ መጋቢት 6 እና 7 ቀን 2016 ዓ.ም. (ዓርብ መንፈቀ ሌሉትና ቅዳሜ አጥቢያ ላይ) በኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ላይ የደረሰው ጥቃት ወንጀል ነው፡፡ ባንኩ ከ800 ሚሊዮን ብር በላይ ያላግባብና ያለ ሕግ ያጣበት፣ ከዚህ ውስጥ 662.9 ሚሊዮን ብር ያህሉ መልሶ እጁ ያስገባበት በመላው ዓለም እንደ ጉድ የተዘገበው ይህ ድርጊት ያለ ጥርጥር የኢትዮጵያ የወንጀል ሕግ ዛሬ ሳይሆን፣ በተለይም ከ1949 ዓ.ም. ጀምሮ በንብረት መብቶች ላይ የሚፈጸሙ ወንጀሎች ብሎ  በሚወስናቸው የተከለከሉ ተግባሮች ውስጥ የሚፈረጅ ድርጊት ነው፡፡ ለምንነጋገርበት ጉዳይ ምንም አላስፈላጊ ቢሆንም ይህን ተግባር ሕግ ምን ብሎ እንደሚጠራው እናውሳ፡፡ ሕገወጥ በሆነ መንገድ ወይም ያላግባብ መበልፀግ ይለዋል፡፡ ‹‹ወንጀል አድራጊው ለራሱ ወይም ለሌላ ሦስተኛ ሰው ሕገወጥ የሆነ ጥቅም ለማስገኘት አስቦ የፈጸመው ድርጊት ወንጀል መሆኑ በሕግ የተደነገገ ሲሆን፣ ድርጊቱ ተገቢ ያልሆነ ጥቅም ለማግኘት የተፈጸመ ነው ተብሎ ይገመታል፡፡

‹‹እንደዚህ ባለ ሁኔታ የታሰበው ብልፅግና ባይገኝም እንኳን፣ ያላግባብ የመበልፀግ ፍላጎቱና ተግባሩ ተጣምረው መገኘታቸው ከተረጋገጠ ፍፃሜ ያገኘ ወንጀል እንደተደረገ ይቆጠራል፡፡

‹‹በዚህ ሁኔታ የተወሰደውን ሀብት የመመለስ ወይም ለደረሰው ጉዳት ካሳ አስቀድሞ የመክፈሉ ጉዳይ በአድራጊው ፈቃደኝነት የተፈጸመ ቢሆንም፣ ወንጀሉን አያስቀረውም፡፡ ነገር ግን ስለቅጣቱ አወሳሰን ፍርድ ቤቱ ይህንን ከግምት ማስገባት ይቻላል፤›› ይላል ሕጉ፡፡

‹‹በሕግ ከተወሰደች በቅሎዬ ያለ ሕግ የሄደችው ዶሮዬ ጉዳይ ይቆጨኛል፤›› ያለው ሰው አባባል ምሳሌ ብቻ ሳይሆን የአገር የፍትሕ ህዋስ፣ የማይነቃነቅ መለኪያ ሆኖ በሚኮራበትና በሚፎከርበት አገር ውስጥ ከቀልደኛው ከበዕውቀቱ ሥዩም በስተቀር፣ አገሪቱን እንደ ጉድ ከወረራት እዚህ ሁሉ ወፈ ሰማይ ዩቲዩበር ውስጥ አንድም ሰው ድርጊቱን  በስሙ ሲጠራው፣ የአገር አጀንዳ ሲያደርገው አላየንም፡፡

የኢትዮጵያ ባንኮች ማኅበር ወዲያውኑ ያወጣው መግለጫም በምንነጋገርበት በዚሁ አገርን ቀስፎ በያዘው  ነውር ምክንያት በየሚዲያው በተገቢው ልክ አልተስተጋባም እንጂ ድርጊቱን ያወገዘ መግለጫ ነበር፡፡

የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች፣ የኢትዮጵያ ፖለቲካ፣ ዴሞክራሲ፣ የሰብዓዊ መብት አያያዝ ያሳስበናል የሚሉ ዜጎች ስለመብት ስለነፃነት ሲንሰፈሰፉና ሲንገበገቡ እንሰማለን፡፡ በሰው ነፃነት ላይ የሚፈጸም ወንጀል (ሰው ማገት፣ ሰው በፖለቲካ ምክንያት መጥለፍ፣ የተጠለፈውን ሰው ዘመድ የተጠየቀውን ገንዘብ አላመጣም ብሎ ገድሎ ሰው በየአደባባዩ ማሳጣት) ግን አላስደነግጥ ሲል፣ ይልቁንም  ውግዘት ሲያጣ በአገራችን ላይ የደረሰው ሕመም ይበልጥ አሳሳቢና አደገኛ ሆኖ ይመጣል፡፡ በተለይ ወንጀልን፣ የወንጀል ድርጊትን የትግል ስልት አድርጎ መያዝ፣ በሌላው የኑሮ ዘርፍም ሕጋዊና ቀጥተኛ መንገዶች ዋጋ እንዲያጡ ዘወርዋራና መሰሪ፣ እንዲሁም ሕገወጥ መንገዶች እንዲንሰራፉ ሕይወት በተገኘው ማንኛቸውም አቋረጦችና አጋጣሚዎች ሁሉ የመጠቀም ታላቅ ቁማር እንዲሆን፣ መንግሥት ራሱ ይበልጥ እንዲደኸይ፣ ኅብረተሰቡ እንዲጎዳ፣ በህሊና በሙያና በኃላፊነት ማመንዘርና በሥልጣን መቆመር በአጠቃላይ የምናውቀውና ‹‹በሕግ አምላክ›› እያልን የምንኮራበት ሲወርድ ሲዋረድ የመጣው የኅብረተሰቡ የሕግ ሥርዓትና የሥነ ምግባር ውቅራቶች ፍልስልሳቸው እንዲወጣ ያደርጋል፡፡

ይህ የምንነጋገርበት ጉዳይ ከመንግሥት ጋር የሚታገሉትን የፖለቲካ ቡድኖችን ወይም የእነሱን ደጋፊዎች ወይም በዝምታ ሴራ ጭምር፣ ይህን የሚያበረታታውን ተመልካቹንና ቲፎዞውን ‹‹ሕዝብ›› ብቻ የሚመለከት አይደለም፡፡ የመንግሥትንም ሕግ አክባሪነት ይጠይቃል፡፡ የመንግሥት የሕግ አስከባሪነት በሕዝብ መታገዝና መደገፍ ያለበትን ያህል፣ ሕግ የማስከበር የመንግሥት የትኛውም እንቅስቃሴና ዕርምጃ በተለይም መንግሥት ሕገጥነትን ለመግታት የሚወስደው ዕርምጃ የራሱንም የሕግ አክባሪነት የውኃ ልክ አለማስገመቱን፣ ጥያቄ ውስጥ  አለማስገባቱን ሲበዛ ማረጋገጥ አለበት፡፡ ከዚህም በላይ መንግሥት ሕግ ማክበርን ይበልጥ ማስተማርና ማስለመድ አለበት፡፡ መንግሥት ይህን የሚያስተምረው፣ የሚያለማምደውና የሚያበረታታው ደግሞ ከሕገወጡ ይበልጥ ሕጋዊውን መንገድ የላቀ ተመራጭ፣ የሚያዋጣና የሚክስ የሚያደርግ የፖለቲካ የባህልና የአሠራር ሁኔታ በማልማት ነው፡፡

የምንነጋገረው እጅግ በጣም አንገብጋቢ ስለሆነው ስለሥርዓት ነውና ይህ ጉዳይ ይበልጥ እንዲገባንና እንዲያሳስበን እንዲያንገበግበን ጭምር፣ ከዚህ ቀደም በታሪካችን ውስጥ ሥርዓት ማለት ምን እንደሆነ አሳምሮ ማስገንዘብ ይቻላል ብዬ የመረጥኩትን በዳግማዊ አፄ ቴዎድሮስ  ዘመን ስለመሆኑና ስለመፈጸሙ የነገረለትን አንድ ታሪክና ትምህርት ላጋራችሁ፡፡ በነገራችን ላይ የዚህ ታሪክና ትምህርት ደራሲ ዕውቁ አፈወርቅ ገብረ እየሱስ ናቸው፡፡

‹‹አንድ ሌባ በጨለማ ተዋጨት ተስቦ ገብቶ ላም ሲሰርቅ ባለቤቱ ነቃና ትልቅ ጦሩን እየሰበቀ ለመግደል ያባርረው ጀመር፡፡ አባራሪና ተባራሪ ሁነው ሲሯሯጡ በሩጫ ሌባው አባተ፡፡ እንዳመለጠው ባየ ጊዜ አባራሪው በቴዎድሮስ ሞት ቁም! በሞቱ አትላወስ አለና ያን ሌባ ተማፀነ፡፡ ይሄን ቃል በሰማ ጊዜ ጭራሹን እንደማምለጥ ሁሉ ያው ሌባ እሺ ብሎ ቆመለት፡፡ በዚህ ጊዜ አባራሪው ቀርቦ አመቻቸና የታባህ ብሎ በያዘው ጦር ሰነበቀው፡፡ ደም አፈታበትና ያ ሌባ ግልድው ብሎ በወደቀ ጊዜ አባራሪው ገድየዋለሁ መስሎት የወጋበትን ጦር ደም ጠራጥርጎ ወደ ከብቶቹ ተመለሰ፡፡ ያም የተወጋ ሌባ ደም አስክሮት ነብሱን አጥቶ ከዚያው እንደወደቀ አመዳይ ተጋግሮበት አደረ፡፡ በማግሥቱ አንድ እጸድቅ ባይ ጎዳነኛ ጭርስ አለመሞቱን ባየ ጊዜ ተሸክሞ ወስዶ ታንድ ደጀ ሰላም አስጠጋውና ሄደ፡፡ ከዚአም በኋላ ተዛኒጋባ የሚኖሩ መበለቶች ቁስሉን በዶሮ ላባ እያጠቡና ዲን እየነሰነሱ በቶሎ አስታመው አዳኑት፡፡  

‹‹ያው ሌባ ግን ወዲያው ተቁስሉ እንደዳነ ሄዶ ላጤ ቴዎድሮስ እንዲህ ብሎ ጮኸ፡፡ ጃንሆይ እግዚአብሔር ያሳይዎ ክርስቶስ ያመልክትዎ ልዦቸም ምሽቴም እኔም አራብ ቢአጠቃነ እንኳን እህል — አሎጫ በጋ ሁኖ ቢአጥነና ልንሞት ብንሆን እራብ ብዙ ያስመኛል፣ ጥንቱን ሆዳም ለጋሱን ስስታም ነባዩን አባይ ያደርጋልና ተምሞት ብዬ አድርጌው የማላውቀውን ነገር ልሰርቅ በጨለማ ሄድሁ፡፡ ነገር ግን ገና ተበረቱ እንደገባሁ ባለቤቱ ነቃና የጠቀርሻ ጦሩን ነጥቆ ተከተለኘ፡፡ እኔም ስሮጥ እሱም እየፎከረ እየተደባደቀ ሲከተለኘ ምንም በጠገበ ጉልበቱ ቢወዘገዘግ እንደተቻለኘ ተፈናጥሬ አመለጥሁት፡፡ እንዳመለጥሁት ማምለጥ ሲቻለኝ እሺ ብዬ በስምዎ ተዳኘቼ ቆምሁለት፡፡ እሱ ግን ሌላ ምንም አላለ እንዲያው ባውራ ጣቱ ሲአበራድደው የነበረውን ጦር በሽንጤ ላይ ወደወደብኘ፡፡ ከዚህ በኋላ በደም አባላ ተነክሬ አእምሮዬን ስቼ ወድቄ ባየኘ ጊዜ ጨርሸዋለሁ መስሎት ጥሎኝ ተመለሰ፡፡ እኔም ተዚአው እንደወደቅሁ አድሬ በበነጋው ስለክርስቶስ ያለ መንገደኛ ተወደቅሁበት አንስቶ ወደ ቤተክርስቲያን እድሞ አስጠግቶኘ መበለቶች አስታመውኝ አዳኑኝ፡፡ አሁን ግን ነገሩን እንዲሰሙት ብዬ ወጊየን ከስሼ ይሄው አመጣሁት፣ እግዚአብሔር ያሳይዎ ጃንሆይ አለ፡፡

‹‹አጤ ቴዎድሮ ግን እሄን ሁሉ ነገር ዝም ብለው አድምጠው በመጨረሻ በጨለማ ተሰው በረት ገብቶ ከብት የሚወስድ ሰው ጅብ ነው እንጂ ሰው አይባልም፣ አሁን ጅብ ቢወጋ ለምን ወጋ ብለህ ነው መክሰስህ አበጀ ወጋህ! አሉና ተቆጡት፡፡ ወዲአውም ወደዚያ ወደወጊው ዘወር አሉና ነገሩን የወደዱለት አስመስለው አንተሳ ከሳሽህ የተናገረው ሁሉ የውነት ነውን ብለው እየሳቁ ጠየቁት፡፡ ተከሳሹ በዚህ አድራጎቱ የተወደደለት መስሎት አወን እርግጥ ነው ብሎ መለሰ፡፡

‹‹አጤ ቴዎድሮስ አወንን በሰሙ ጊዜ በዚህ ሁሉ ሰው መሀል ካሳ የመይሳ ልዥ ብለው ፈከሩና አያችሁ በኔ ስም አራዊቱ ጅቡ ሳይቀር ሲገዛና ሲዳኝ የሌት ሌባ ጅብና አውሬ ነው ይሄው አውሬ በቴዎድሮስ አምላክ ቢባል ቀጥ ብሎ ቆመ! ብለው ለመኳንንቱ ሁሉ አሰሙት፡፡ ቀጥለው ግን ተከሳሹን ተበረትህ ምን ያህል ቁም አለህ አሉና ጠየቁት እሱም ተጥጃውም ተምኑም ብየ አንድ አምስት መቶ ያህል ቁም አለኘ አለ፡፡ አስንት ልጆች አሉህሳ አሉት፡፡ ምሽቴ መካን ናትና ምንም ልጅ የለኝ ብሎ መለሰ፡፡ እንዲሀስ ተሆነ መልካም አንተ በቴዎድሮስ አምላክ ቁም ብትለው ታመለጠህ ወዲአ ተዳኝቶ እሱ ሌባው ቢቆምልህ አንተ ሳትዳኝ ወግተህ ጣልከው፡፡ እንዲህ ተሆነ እኔን የኔን ስም ነው እንጂ የወጋህ እሱን አይደለም! ስለዚህ ከሳሸህ እኔ ነኘና መኳንንቱ ይፍረዱነ ፍርድ ቢሰጥህ ዳን ፍርድ ቢነሳህ ተቀጣ ብለው ንጉሡ ከሰሱት፡፡

‹‹መኳንንቱም ሊቃውንቱም አንድ ሁነው እንዲህ ብለው ፈረዱበት፣ በሩጫ ተፈታትነው በጉልበት ተሞካክረው አባራሪው በተባራሪው ለመድረስ ሰንፎ ባይሆንለት ባምላኩ ብሎ ያመለጠውን ከሰሰ፡፡ አሄም ተከሰሰኘ ለስራት እንጂ ለመውጋት አላሰበኘም ብሎ ተዳኘቶ ቆመለት፡፡ እሱ ከሳሹ ግን ስራቱን ትቶ ወደ ጉልበቱ ተመልሶ ወጋና ጣለው፡፡ እሄን ታደረገ ቀኘና ግራ ተከሳሶ ቆሞ ተዳኛ ፊት ተሙግት መሀል አንዱን አንዱ እንደመግደል ያለ ነውና አደባባይ ወጥቶ ተዛፍ ላይ ይሰቀል በቃ ብለው ፈረዱበት፡፡

‹‹አጤ ቴዎድሮስ ግን ብቅል ይመስል እሱን ተመስቀል ይልቀን በሱ ንብረት ያ የተወጋው ይግባበት፣ ወጊውም ተስር ቤት ገብቶ በጅቦ ይታሰርና እድሜዬ ይፍታው፡፡ ምሽቱ ግን በሱ አበሳ አትወረስምና ጣማ ገንዘቧን ተወራሹ ጋር ተካፍላ ትሂድ ብለው ፈረዱ . . .››፡፡

ይህንን እንዳለ ከእነ ቋንቋው ያቀረብኩላችሁን የአፈወርቅ ገብረ እየሱስን ‹‹የሕግና ፍትሕ›› ታሪክ ወይም ተረክ አብራራለሁ ብዬ አልሞክርም፡፡ አንዳንድ ጉዳዮች ላይ አስተያየት ለመስጠት ግን አንባቢያንን፣ በዚያው በወቅቱና አሁንም ጨርሶ ባልቀረው ቋንቋ ‹‹እግዚአብሔር ያሳይዎ ክርስቶስ ያመልክትዎ!›› ብዬ የማመለክታቸውና የማሳስባቸው አንዳንድ ጉዳዮች አሉኝ፡፡ ኢትዮጵያ አገራችንና ሕዝቧ ልማት ሊሳካልን ቀርቶ፣ ራሱ ከረሃብ የማምለጥ ጥያቄ ዋናው እስከመሆን ገዝፎ በዓለም ውስጥ አሉታዊ ምሳሌ አድርጎን፣ ‹አንዳንድ› ቋንቋዎች ውስጥም ኢትዮጵያ ማለት ረሃብ፣ ጠኔ፣ ችጋር ማለት እስኪሆን ድረስ በጣም በክፉ ታውቀን ነበር፡፡ እንዲህ ያለ ታሪክና ተሞክሮ ባለው/በነበረው አገርና ሕዝብ ውስጥም ማጣት ክፉ ቢሆንም ጨርሶ ስርቆትን፣ ወሮበላነትን፣ ዝርፊያን በአጠቃላይ ሕጉ በንብረት/በሀብት ላይ የሚሠራ ወንጀል የሚለውን ድርጊት ተገቢ አያደርግም፡፡ ይህንን ሀቅ ከራሱ ከ‹‹ሌባ››ው  አቤቱታና ታሪክ እንረዳለን፡፡ ነገሬን ለማስረገጥ እደግመዋለሁ፡፡ ማጣት ክፉ ነገር ነው፣ ነገር ግን ስርቆትን ተገቢ አያደርግም፣ የዚህ ጥፋት/ወንጀል መከራከሪያም መከላከያም አይደለም፡፡ ስርቆት ማለትም በሌላ ሰው ሀብት ላይ የሚሠራ ወንጀል ከ38 ምዕት ዓመት በፊት በወጣው የሀሙራቢ ሕግ ጭምር ወንጀል ሆኖ ኖሯል፡፡ በመጽሐፍ ቅዱስ ከአሥርቱ ትዕዛዛት መካከል አንዱና ስምንተኛው ኦሪት ዘጸአት 20፡15 አትስረቅ ይላል፡፡ ቅዱስ ቁርዓንም አቻ ድንጋጌዎች አሉት፡፡ በዚህ ምክንያት ስርቆት ነውርም፣ ወንጀልም፣ ሐጢያትም ነው፡፡ ደግሞ በሕግ ዓይነት ዓይነት አለው፡፡ ተራ ስርቆት ከባድ ስርቆት፣ ውንብድና፣ ከባድ ውንብድና፣ ዘረፋ፣ እንዲሁም የባህር ውንብድና እየተባሉ ይዘረዘራሉ፡፡ በጦርነት ጊዜ የውንብድና (ማለትም በኃይል ተግባር የታገዘ  የስርቆት ወንጀል መፈጸም) የጦርነት ወንጀል ውስጥ መካተት ድረስ የሚከፋ ከባድ የወንጀል ዓይነት ነው፡፡ በተለምዶ ሌባ፣ ቀማኛ፣ ‹‹ጨለማን ተገን አድርጎ›› መስረቅ የምንለውን ዓይነት በልክና በመልኩ መዘርዘሩ ነው፡፡

ብዙዎቻችን የኔ ቢጤዎችና የዕድሜ አቻዎች ያለፍንበት የትምህርት ሥርዓት ፈልጎም ይሁን ሳይፈልግ እንዳደረገን ሀሙራቢ የሚባለውን ንጉሥና ሕጎቹን የምናውቀው በሕጎቹ ‹‹ጨካኝነት››/‹‹በጨቋኝ ሕጎቹ ነው፡፡ ማለትም በቅጣቶቹ ነው፡፡ ዛሬም የሚጠናው የሀሙራቢ ሕግ መርሆዎች ግን በጣም የሚገርሙና ዛሬም ዋጋ ያላቸው፣ ከሁሉም በላይ ደግሞ አሁንም ቢሆን ገና ዘልቀው ያልገቡን ናቸው፡፡ ሁለት ነገሮች ብቻ ባጭሩ ልጥቀስ፡፡ የኢትዮጵያ ሕገ መንግሥቶች  በተለያዩ ዘመናት (1948ቱ በአንቀፅ 53 የ1980ው በአንቀጽ 45፣ የ1987ቱ በአንቀጽ 20/3) የደነገጓቸው የተከሳሽ ከፍርድ በፊት እንደ ጥፋተኛ ያለመቆጠር መብት ሥረ መሠረት 3800 ዓመት ዕድሜ ያለው የሀሙራቢ ሕግ ነው፡፡ የወንጀል  ፍትሕ ሥርዓታችንን ዛሬም ድረስ ብዙ ዘልቆ ያልገባውና ጨምድዶ ያልያዘው አንድ ነገር ቢኖር (ከሌሎች መካከል) የወንጀል ድርጊት ሰለባዎች መብት (ቪክቲምስ ራይትስ) የሚባለው ነው፡፡ የሀሙራቢ ሕግ በዚህ ጉዳይ ላይ ከ38 መቶ ዓመት በፊት ያስቀመጠው መርህ ምን ይላል መሰላችሁ? አንድ ሰው ላይ ለምሳሌ የግድያ ወንጀል ቢፈጸምበት መንግሥት ሰውዬው ከመሞት ባለማዳኑ፣ የግድያ ወንጀሉን መከላከል ሳይችል በመቅረቱ አንድ ጊዜ ወደቀ፡፡ የዚህን ሰውዬ ገዳይ ለይቶ፣ ለፍርድ አቅርቦ፣ ጥፋተኛውን ማረጋገጥ ሳይችል ሲቀር ደግሞ ሁለተኛ ፈተና ወደቀ ይላል፡፡

ጉዳያችን አድርገን በተከታተልነው የአፄ ቴዎድሮስ ዘመን የሀብት ባለመብትና የ‹‹ሌባ››ው ጉዳይ ውስጥ መጨረሻ ላይ ከ‹‹አባራሪው›› ይልቅ የ‹‹ተባራሪው››፣ ከባለሀብቱ ወይም ከባለመብቱ ይልቅ የ‹‹ሌባ››ው ወይም የስርቆት ድርጊት ለመፈጸም የሞከረው ሰው መብት በልጦና ደምቆ ሲወጣ አይተናል፡፡ የዚህ ምክንያት በሀብት ላይ ያለ መብትን ፋይዳ አሽቀንጥሮ መጣል ወይም የስርቆት ወንጀልን  ማራከስ አይደለም፡፡ የከሳሹ/የ‹‹ሌባው›› አቤቱታ ራሱ አንጀት እየበላ፣ ልብ እየነካ እንደሚያስረዳው (‹‹እንዳመለጥኩ ማምለጥ ሲቻለኝ እሺ ብዬ በስምዎ ተዳኝቼ ቆምኩለት››) የሥርዓት ጉዳይ ነው፡፡ ‹‹በሩጫ ተፈታትነው፣ በጉልበት ተሞካክረው፣ አባራሪው በተባራሪው ለመድረስ ሰንፎ ባይሆንለት በአምላኩ ብሎ ያመለጠውን ከሰሰ፡፡ ይኼም ተከሰሰኝ ለስራት እንጂ ለመውጋት አላሰበኝም ብሎ ተዳኝቶ ቆመለት፡፡ እሱ ከሳሹ ግን ስራቱን ትቶ ወደ ጉልበቱ ተመልሶ ወጋና ጣለው፡፡ ይኼን ታደረገ ቀኝና ግራ ተካስሶ ቆሞ ተዳኛ  ፊት ተሙግት መሀል አንዱን አንዱ እንደ  መግደል ያለ ነውና…›› ብለው ፈረዱበት፡፡

መኗኗሪያ ማድረግ ሳይሆን፣ ማድነቅ ሳይሆን ማወቅ መረዳት ያቃተን የዚህን የ‹‹…ሥርዓት››/‹‹የስራት›› ትርጉም ነው፡፡ በሕግ አምላክ ብሎ ጠይቆ፣ ለጥያቄውም ምላሽ አግኝቶ አስቁሞ መግደል በተራ የልጆች ጨዋታ (‹‹ሰኞ ማክሰኞ››ም ሆነ በሌላ) በካርታ ጨዋታም ሆነ በሌላው ጦርነትን በመሰለ የቀይ መስቀል ሕግ በሚገዛው ‹‹ጨዋታ››ም ውስጥ ፐርፊዲ (Perfidy) ነው፡፡ ክህደት ነው፡፡ ወራዳነት ነው፡፡ ሞላጫነት ነው፡፡

ዛሬ መላው ዓለም፣ በተለይም የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የሰብዓዊ መብቶች ሥርዓት ዓለም አቀፋዊ የሰብዓዊ መብቶች ሕግጋት የሚሏቸው ሕጎች የኢትዮጵያ ሕግ አካል ናቸው፡፡ እነዚህ ሥልጣኔ ቃል ለሰማይ ለምድር ብሎ የተቀበላቸውና አከብራቸዋለሁ ያላቸው ሕጎች የኢትዮጵያ ሕግ አካል በመሆናቸው ብቻ ሳይወሰን፣ በሕገ መንግሥቱ አንቀጽ 13(2) መሠረት ደግሞ የመሠረታዊ መብቶችና ነፃነቶች ድንጋጌዎች የውኃ ልክና የደረጃ መለኪያ ናቸው፡፡ ከሁሉም በላይ ደግሞ የአገር የወንጀል ሕግ በእነዚህ መሠረታዊ ልብዓዊ መብቶች ላይ የሚፈጽሙ ድርጊቶችን ወንጀል አድርጎ ይቀጣል፡፡ ‹‹በሰው ነፃነት ላይ የሚፈጸሙ ወንጀሎች›› ብሎ ከአንቀጽ 580 ጀምሮ በተዘረዘሩ (580-600) አንድ ርዕስ (የመጽሐፍ ክፍል) በተሰጣቸው ድንጋጌዎች ተካተዋል፡፡ እዚህ ውስጥ ከሚገኙት ወንጀሎች መካከል ሰው መጥለፍ/ማፈን/ማገት ይገኝበታል፡፡ እጅግ በጣም የሚገርመው ይህን የመሰለው ወንጀል/በሰብዓዊ መብት ላይ የሚፈጸም ወንጀል ወይም መብት ረገጣ ራሱ፣ በኢትዮጵያ ውስጥ የሚገኙ የፖለቲካ ፓርቲዎች የትግል መሣሪያ ሆኖ መለመዱ፣ መገንተሩና ከሁሉም በላይ ደግሞ ሀይ ባይ ያጣ ይልቁንም የተመረቀ የትግል ስልት መሆኑ ነው፡፡ የሕዝብ አጠቃላይ ንቃትና ግንዛቤ ይህን የትግል ስልት አክ እንትፍ ብሎ አላወገዘውማ፡፡ በዚህ ምክንያት ነው የኢትዮጵያ ፖለቲካ ትግልም የኢትዮጵያ የፖለቲካ ሰላምም በሕግ አምላክ የሥርዓት ያለህ ይላል የምንለው፡፡

ሕገወጥነትን፣ ሕግ መጣስን፣ ወንጀልን ሰላማዊ ያልሆኑ ስልትን ደመ ነውጠኝነትን፣ ግር ብሎ መነሳትን፣ ጋጋታን፣ ውድመትን ዘዴው ያደረገ ትግል የትጥቅ ትግል ጭምር በዛሬው ዓለም ኢትዮጵያም ሆነ ሌላ  ዓለም ውስጥ ትክክለኛው ፖለቲካ መሆኑ ቀርቷል፡፡ ያንኑ ያህልም ባለጠመንጃ ቡድኖችን ከመደገፍ አባዜና መርገምት ያልወጣ የሕዝብ ድጋፍ የዴሞክራሲ አማጭ እንደማይሆን መረዳት ያለበት ይመስለኛል፡፡