ዜና የፓዌ ወረዳ ነዋሪዎች ከአማራ ክልል ተሻግረው በሚመጡ ታጣቂዎች ጥቃት እየደረሰብን ነው አሉ

ተመስገን ተጋፋው

ቀን: April 21, 2024

ከአማራ ክልል አዋሳኝ ድንበር አካባቢ በምትገኘው ፓዌ ወረዳ ውስጥ የሚኖሩ የቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልል ነዋሪዎች፣ ከአማራ ክልል አዊ ብሔረሰብ አስተዳደር ተሻግረው በሚመጡ ታጣቂዎች ጥቃት እየተፈጸመባቸው እንደሆነ አስታወቁ፡፡

በፓዌ ወረዳ ሥር የሚገኙ አራት ቀበሌዎች ማለትም ቀበሌ 14፣ ቀበሌ 17፣ ቀበሌ 24 እና ቀበሌ 26 ታጣቂዎች መቆጣጠራቸውን ነዋሪዎች ለሪፖርተር ገልጸው፣ በዚህ ምክንያት በአራቱ ቀበሌዎች ውስጥ የሚኖሩ ነዋሪዎች ሥጋት ውስጥ መሆናቸውንና ምንም ዓይነት የሥራ እንቅስቃሴ እያደረጉ አለመሆናቸውን አስረድተዋል፡፡

ካለፈው ሳምንት ጀምሮ ከአማራ ክልል ተሻግረው የሚመጡ ታጣቂዎች ከቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልል ውስጥ ከሚገኙ የአካባቢ ሚሊሻዎችና ከሌሎች የፀጥታ ኃይሎች ጋር የተኩስ ልውውጥ ማድረጋቸውን የተናገሩት ነዋሪዎች፣ ሦስት የመንግሥት  ተሽከርካሪዎች በታጣቂዎቹ እንደተወሰዱ አክለው ገልጸዋል፡፡

በአሁኑ ወቅት በቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልል ከተማ ውስጥ የሚገኙ የመንግሥት ኃላፊዎች ወደ አካባቢው ደፍረው እንደማይገቡ ጠቅሰው፣ ታጣቂዎቹም የመተከል ዞንን ለመያዝ ፍላጎት እንዳላቸውና ከዚህ በፊትም ተደጋጋሚ ጥቃት ሲያደርሱ እንደነበር ጠቁመዋል፡፡

በፓዌ ወረዳ የሚገኙ በርካታ ነዋሪዎች ሥጋት ውስጥ እንደሆኑና በታጣቂዎቹ ንብረታቸውም የተወሰደባቸው ሰዎች እንዳሉ የተናገሩት ነዋሪዎቹ፣ መንግሥት በአፋጣኝ ዕርምጃ በአካባቢው ያለ ከልካይ የሚንቀሳቀሱ ታጣቂዎችን ማስወጣት አለበት ብለዋል፡፡

የጉሙዝና የሸኔ ታጣቂዎች በክልሉ ነዋሪዎች ላይ ጥቃት እያደረሱ የንፁኃንን ሕይወትን እያጠፉ መሆኑን ያስታወሱት ነዋሪዎቹ፣ በክልሉ ውስጥ የሚታየው ችግር ከአቅም በላይ እንደሆነባቸው አብራርተዋል፡፡

ከአማራ ክልል ተሻግረው የሚመጡ ታጣቂዎች ገንዘብና ከብቶቻችሁን አምጡ ብለው እንደሚያስገድዷቸው፣ ታጣቂዎቹ እንዲህ ዓይነት ድርጊት ይፈጽሙ እንጂ እስካሁን አንድም ሰው እንኳን አለመግደላቸውን ነዋሪዎቹ ተናግረዋል፡፡

በአማራ ክልል አዊ ብሔረሰብ አስተዳደር ዞን ውስጥ ጃዊ የሚባል ወረዳ እንዳለና  ወረዳውን እነዚህ ታጣቂዎች መቆጣጠራቸው ገልጸው፣ በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል ዳንጉር ወረዳ ውስጥ የሚንቀሳቀሱ የጉሙዝ ታጣቂዎች እንዳሉም አብራርተዋል፡፡

የክልሉ መንግሥት ድርጊቱን ለመቆጣጠር ያደረገው ሙከራ ይህ ነው የሚባል እንዳልሆነ ጠቅሰው፣ በቅርቡ የዳንጉር ወረዳ ምክትል አስተዳደሪን የጉሙዝ ታጣቂዎች አግተው መልቀቃቸውን ተናግረዋል፡፡

የፓዌ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ይርጋ አስፋው በአማራ ክልል ሥር የሚገኘው የፓዌ ወረዳ፣ ከቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልል ፓዌ ወረዳ ጋር እንደሚዋሰን ለሪፖርተር ተናግረዋል፡፡

ከአማራ ክልል ተሻግረው በመጡ ታጣቂዎች በፓዌ ወረዳ ሥር የሚገኙ ሁለት ቀበሌዎች ተይዘው እንደነበር የገለጹት ዋና አስተዳዳሪው፣ በአሁኑ ወቅት ችግሩን በመቅረፍ ታጣቂዎች ከወረዳው እንዲወጡ ተደርጓል ብለዋል፡፡

ከአማራ ክልል ተሻግረው ከመጡ ታጣቂዎች ጋር ሰኞ ሚያዝያ 7 ቀን 2016 ዓ.ም. ጀምሮ ለተከታታይ ሦስት ቀናት የተኩስ ልውውጥ መደረጉን፣ በወቅቱም የተቀናጀ ኃይል በመኖሩ ከአካባቢው ለቀው እንዲወጡ መደረጉን ጠቁመዋል፡፡

በአሁኑ ወቅት በክልሉ ምንም ዓይነት የታጣቂዎች እንቅስቃሴ እንደሌለ ገልጸው፣ ከአማራ ክልል ተሻግረው የሚመጡ ታጣቂዎች ዋና ዓላማቸው ቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልል ውስጥ ገብተው ሰላም ማደፍረስ እንደሆነ ተናግረዋል፡፡

የአማራ ክልል ታጣቂዎች ነን በሚል ሰበብ ሰላምን ማደፍረስ ተገቢ አይደለም ያሉት ዋና አስተዳዳሪው፣ እስካሁን በክልሉ በሰውም ሆነ በንብረት ላይ ምንም ዓይነት ጉዳት አለመድረሱን አክለዋል፡፡

ይሁን እንጂ ክልሉ ከፍተኛ የሆነ ሥጋት እንዳለበት፣ ታጣቂ ኃይሎች አዋሳኝ ድንበር ላይ በመሆናቸው ችግር አይፈጥሩም ብሎ ማሰብ እንደማይቻል አስረድተዋል፡፡