ተመስገን ተጋፋው

April 21, 2024

ከ2007 ዓ.ም. ጀምሮ በጋምቤላ ክልል በእርሻ ልማት የተሰማሩ ከአሥር በላይ የሆኑ ኢንቨስተሮች ከልማት ባንክ የተበደሩትን ብድር መመለስ ባለመቻላቸው ባንኩ ንብረታቸውን በሐራጅ ሊሸጥባቸው መሆኑ ተሰማ፡፡

የጋምቤላ ክልላዊ መንግሥት ኢንቨስትመንት ኮሚሽን ኮሚሽነር ሎው አቡፕ (ዶ/ር) ለሪፖርተር እንደገለጹት ከ2014 እስከ 2015 ዓ.ም. ድረስ ክልሉ ላይ በነበረው የፀጥታ ችግር በርካታ ኢንቨስተሮች በታጣቂዎች ንብረታቸው ተወስዷል፡፡

በአሁኑ ወቅት ልማት ባንክ ንብረታቸውን በሐራጅ ሊሸጥባቸው ጨረታ ያወጣባቸው ኢንቨስተሮች ለኮሚሽኑ ቅሬታ ማቅረባቸውን የገለጹት ኮሚሽነሩ፣ ኮሚሽኑም በጉዳዩ ዙሪያ ከልማት ባንክ ጋር ውይይት ካደረገ በኋላ ባንኩ ንብረታቸውን ለመሸጥ ውሳኔ እንዳሳለፈ መረዳታቸውን ገልጸዋል፡፡

ልማት ባንክ ለየትኛውም ኢንቨስተር ብድር ሲሰጥ የራሱ የሆነ መመሪያ እንዳለውና በመመሪያው መሠረትም ውሳኔ ላይ መድረሱን የጠቀሱት ኮሚሽነሩ፣ ባንኩ ለእነዚህ ኢንቨስተሮች የብድር ማራዘሚያ እንዲሰጥ ኮሚሽኑ በውይይት ወቅት መጠየቁን አክለው ገልጸዋል፡፡

ከዚህ በፊት በጋምቤላ ክልል በርካታ ኢንቨስተሮች በደቡብ ሱዳን ታጣቂዎች ንብረታቸው ያለአግባብ ይወሰድ እንደነበር ያስታወሱት ኮሚሽነሩ ታጣቂዎችም የእርሻ ምርት የሚደርስበትን ወቅት በመጠበቅ ድርጊቱን እንደሚፈጽሙ ተናግረዋል፡፡

ልማት ባንክ ንብረታቸው በሐራጅ እንዲሸጥ የወሰነባቸውን ኢንቨስተሮች ስም ዝርዝርና ያለባቸውን የዕዳ መጠን ኮሚሽኑ እንደማያውቅ ጠቅሰው፣ በአሁኑ ወቅት በተለያዩ ሥራዎች ላይ የተሰማሩ ከ600 በላይ ኢንቨስተሮች በክልሉ ውስጥ እንደሚገኙ ጠቁመዋል፡፡

ልማት ባንክ የእርሻ ትራክተሮች፣ የሰብል ምርቶችና ተሽከርካሪዎች በሐራጅ ለመሸጥ ጨረታ ያወጣ ሲሆን የክልሉ መንግሥትም ባለሀብቶች ወደ ክልሉ መጥተው እንዲሠሩ ጥረት እያደረገ መሆኑን ገልጸዋል፡፡

በጋምቤላ ክልል በእርሻ ልማት የተሰማሩ ከአሥር በላይ ኢንቨስተሮች በሐራጅ ለመሸጥ ውሳኔ ላይ የደረሰበትን ምክንያትና እስካሁንስ ያልተመለሱ ብድሮችን መጠን ከኢትዮጵያ ልማት ባንክ ለማረጋገጥ ጥረት ቢደረግም ሳይሳካ ቀርቷል፡፡