አቶ ጣሂር ሙሐመድ
የምስሉ መግለጫ,አቶ ጣሂር ሙሐመድ

ከ 4 ሰአት በፊት

ላለፈው ሁለት ዓመት ከስምንት ወር ገደማ የአማራ ክልል ባህልና ቱሪዝም ቢሮ ኃላፊ ሆነው ሲሰሩ የነበሩት የአማራ ብሔራዊ ንቅናቄ አብን (አባሉ) አቶ ጣሂር ሙሐመድ “በግል ምክንያት” ከኃላፊነት መልቀቃቸውን ለቢቢሲ ተናገሩ።

በአቶ ጣሂር ቦታ ሌላኛው የአብን አባል አቶ መልካሙ ፀጋዬ በክልሉ ርዕሰ መስተዳድር መሾማቸውን የአማራ ክልል ኮሚዩኒኬሽን አስታውቋል።

ስድስተኛው አገር አቀፍ ምርጫን ያሸነፈው ገዢው ብልፅግና ፓርቲ መንግስት ሲመሰረት በተከተለው የተቃዋሚ ፓርቲ አባላትን በመንግስት ኃላፊነት ላይ የማካተት ውሳኔ መሰረት ወደ ኃላፊነት የመጡት አቶ ጣሂር፤ የተሾሙት መስከረም 2014 ዓ.ም. ነበር።

በወቅቱ የክልሉ ፕሬዝዳንት የነበሩት ዶ/ር ይልቃል ከፋለ ለኃላፊነት ያቀረቧቸው ሌላኛው የተቃዋሚ ፓርቲ አባል የአማራ ዴሞክራሲያዊ ኃይል ንቅናቄ (አዴኃን) ሊቀመንበር አቶ ተስፋሁን አለምነህ ነበሩ። አቶ ተስፋሁን የተሾሙት የክልሉ የአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን ኃላፊ ሆነው ነበር።

ከሹመቱ በኋላ ሶስት ዓመት ለሚጠጋ ጊዜ በቢሮ ኃላፊነት የቆዩት አቶ ጣሂር፤ ከኃላፊነት ለመልቀቅ ጥያቄ ያቀረቡት ከስድስት ወር በፊት እንደነበር ለቢቢሲ ገልፀዋል። ይሁንና “በክልሉ ያለውን ወቅታዊ ሁኔታ ተከትሎ አመራሩ በተለያዩ ሁኔታዎች በመያዙ (busy በመሆኑ)” ጥያቄያቸው መልስ ሳያገኝ መቆየቱን አስረድተዋል።

በአቶ ጣሂር ምትክ የተሾሙት አቶ መልካሙ ፀጋዬ
የምስሉ መግለጫ,በአቶ ጣሂር ምትክ የተሾሙት አቶ መልካሙ ፀጋዬ

ባለፉት “ሶስት፣ አራት ወራት” ወዲህ አንስቶ ከኃላፊነት የመልቀቅ ጉዳይ ላይ ከክልሉ አመራሮች ጋር “በዝርዝር” ንግግር ማድረጋቸውን ያስታወሱት አቶ ጣሂር፤ የክልሉ መንግሥት ጥያቄውን እንደተቀበለው ተናግረዋል። የቀድሞው የአማራ ክልል ባህልና ቱሪዝም ቢሮ ኃላፊ፤ “ትንሽ የቤተሰብ ጉዳይ ስለነበረብኝ በቤተሰብ እና በራሴ ጉዳይ ነው የለቀቅሁት” ሲሉ ከኃላፊነት የለቀቁበትን ምክንያት አስረድተዋል።

አቶ ጣሂር፤ “[ከክልሉ አመራሮች ጋር[ በመነጋገር ከፓርቲያችን ሰው ተክተን ነው የወጣሁት” ሲሉም ከኃላፊነት ሲለቅቁ በእሳቸው ቦታ የሚሾም ሌላ የፓርቲው አባል እንዲተካ መደረጉን ለቢቢሲ ገልጸዋል።

የአማራ ክልል ኮሚዩኒኬሽን ቢሮ ዛሬ ማክሰኞ ሚያዝያ 22፤ 2016 ዓ.ም. በፌስቡክ ገጹ ባወጣው መረጃ የክልሉ ርዕሰ መስተዳድር አቶ አረጋ ከበደ አቶ መልካሙ ፀጋዬን ባህል እና ቱሪዝም ቢሮ ኃላፊ አድርገው መሾማቸውን አስታውቋል።

አዲሱ ተሿሚ አቶ መልካሙ፤ የአብን ስራ አስፈጻሚ አባል ሲሆኑ የፓርቲው የፅህፈት ቤት ኃላፊም ሆነው ሲሰሩ ነበር።

አቶ መልካሙን ለቢሮ ኃላፊነት እንዲሾሙ በፓርቲው የተመረጡት ያላቸውን “የተሻለ የአመራር ሂደት” እና “የመንግስት ቢሮክራሲ ልምድ” ከግምት ውስጥ በማስገባት እንደሆነ አቶ ጣሂር ገልጸዋል።

አቶ ጣሂር በቀጣይ መዳረሻቸው የት ሊሆን እንደሚችል ከቢቢሲ ለቀረበላቸው ጥያቄ “እሱን አሁን መናገር አልችልም” የሚል ምላሽ ሰጥተዋል።

የቀድሞው የክልሉ ባህል እና ቱሪዝም ቢሮ ኃላፊ አቶ ጣሂር፤ በትግራይ ተቀስቅሶ ወደ አማራ እና አፋር ክልሎች ተስፋፍቶ የነበረውን ጦርነት ያስቆመው የፕሪቶሪያ ግጭትን በዘላቂነት የማስቆም ስምምነት ከተፈረመ በኋላ በጥር 2015 ዓ.ም. የተከበረው የጥምቀት በዓል በጎንደር ከተማ በድምቀት ለመካሄዱ የነበራቸው ሚና ስማቸው ይነሳል።

አሁን በክልሉ ባለው ግጭት ምክንያት ግን “በባህልና ቱሪዝም ዘርፍ በታቀደው እና በሚፈለገው ልክ ተግባራትን መፈፀም እንዳልተቻለ” ቢሮው ማስታወቁን የአማራ ሚዲያ ኮርፖሬሽን ባለፈው ሳምንት ዘግቦ ነበር።