“ ኑሮ ውድነቱን ሠራተኛው ሊቋቋመው አልቻለም ” – አቶ ካሳሁን ፎሎ
ዛሬ የሜይዴይ በዓል እየተከበረ ነው።
በዓሉ አስመልክቶ ትላንት የሥራና ክህሎት ሚኒስቴር መግለጫ ሰጥቶ የነበረ ሲሆን በመግለጫው ላይ የኢትዮጵያ ሠራተኞች ማህበራት ኮንፌዴሬሽን ተገኝቶ ነበር።
ኮንፌዴሬሽኑ ፤ በባለፈው ዓመት በተከለከለው ሰልፍ ሳቢያ ከመንግሥት ጋር የገጠማችሁ አለመግባባት ተፈታ ? የሠራተኞች ጥያቄ ምላሽ እንዲያገኝ አሁንስ ምን እየተሰራ ነው ? የሚል ጥያቄ ቀርቦለታል።
የኢሰማኮ ፕሬዚዳንት አቶ ካሳሁን ፎሎ፣ “ ከአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ነው ክልከላው ደርሶን የነበረው። በመነጋገር መፍታት አልቻልንም በወቅቱ ” ብለዋል።
“ ከዚያ በኋላ ግን ለምን እንደተከለከልን ከመንግሥት አካላት ጋር በየደረጃው ተወያይተናል። ክልከላው ሆን ተብሎ ሠራተኛው ያለውን ጥያቄ እንዳያቀርብ የተደረገ እንዳልነበር ተግባብተናል ” ሲሉ ገልጸዋል።
“ ከዚያም ጥያቄያችንን አደራጅተን ለጠ / ሚኒስትሩ አቅርበን ግብር እንዲቀነስ፣ ዝቅተኛ የደመወዝ ወለል ስኬል እንዲወሰን መጠየቃችን ይታወቃል። ጠ/ሚኒስትሩ በጥናት ላይ ተመስርቶ ምላሽ እንደሚሰጥ አቅጣጫ አስቀምጠዋል ያኔ ” ሲሉ አስታውሰዋል።
“ አቅጣጫ የተሰጠባቸውን ጉዳዮች እየተከታተልን ነው ” ያሉት አቶ ካሳሁን ፣ “ ነገር ግን አቅጣጫ የተሰጠባቸው የኑሮ ውድነቱን የተመለከቱ ጥያቄዎች ምላሽ አሁንም ዘግይቷል። ኑሮ ውድነቱን ሠራተኛውም ሊቋቋመው አልቻለም ” ብለዋል።
አሁን ምን አዲስ ነገር አለ ? ለሚለው ፦
ከሠራተኛው በነጻ መደራጀት ጋር በተያያዘ ለሁሉት ዓመታት ተቋርጦ የነበረው መንግስትና ሠራተኛ ቁጭ ብለው የሚወያዩበት የአሰሪና ሠራተኛ አማካሪ ቦርድ ዘንድሮ ሥራ ጀምሯል፡
በሥራና ክህሎት ሚኒስቴር ሰብሳቢነት የሁሉም ክልሎች ሠራተኛ እና ማኀበራዊ ጉዳይ ቢሮ ኃላፊዎች በሚገኙበት ስብሰባ ግምገማ ማካሄድ ተጀምሯል ጥያቄዎች በዚሁ አካሄድ ይፈታሉ ሲሉ አስረድተዋል።