ዜና
በሰባት ክልሎች 1.7 ሚሊዮን ዜጎች ለጎርፍ አደጋ ተጋላጭ እንደሚሆኑ ተነገረ

ፅዮን ታደሰ

ቀን: May 1, 2024

የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የሰብዓዊ ዕርዳታ ማስተባበሪያ ጽሕፈት ቤት (ኦቻ) ባወጣው ሪፖርት እንዳስታወቀው በአፋር፣ ኦሮሚያ፣ አማራ፣ ሶማሌ፣ ደቡብና ትግራይ ክልሎች ከ1.7 ሚሊዮን በላይ ዜጎች ለከፍተኛ የጎርፍ አደጋ ተጋላጭ እንደሚሆኑ አስታውቋል፡፡

የሰብዓዊ ድጋፍ ሰጪ አካላት በአደጋ ሥጋት ሥራ አመራር ኮሚሽን መሪነት፣ በተዘረዘሩት ክልሎች የጎርፍ አደጋ ቅድመ ዝግጅት ዕቅዶችን አስቀድመው ቢያወጡም የገንዘብ ድጋፍ እጥረት መኖሩ በሪፖርቱ ተጠቁሟል፡፡

በሰባት ክልሎች 1.7 ሚሊዮን ዜጎች ለጎርፍ አደጋ ተጋላጭ እንደሚሆኑ ተነገረ | Ethiopian Reporter | ሪፖርተር

ሪፖርቱ እንደሚያሳየው በሶማሌ ክልል 1.2 ሚሊዮን ሰዎች ለጎርፍ አደጋ ተጋላጭ እንደሚሆኑ የተገመተ ሲሆን፣ ከ700 ሺሕ በላይ የሚሆኑና በአፍደር፣ ሊባኖን፣ ኮራህ፣ ኤረር፣ ዳዋ፣ ጃራር፣ ኖጎብና ሸበሌ ዞኖች የሚኖሩ ዜጎችን ከቀያው ሊያፈናቅላቸው እንደሚችል ተሠግቷል፡፡ በደቡብ ክልል ከ140 ሺሕ በላይ የሚሆኑ ዜጎች በአደጋው ሊጠቁ እንደሚችሉና በመጋቢት ወር መጀመሪያ ላይ በሀላባ፣ ስልጤ እንዲሁም ሲዳማ 64 ሺሕ የሚሆኑ ዜጎች ከቀያቸው መፈናቀላቸው በሪፖርቱ ተገልጿል፡፡ 

በኦሮሚያ ክልል በተጠቀሱት ወራት ይከሰታል ተብሎ በሚጠበቀው የጎርፍ አደጋ ከ420 ሺሕ በላይ ሰዎች እንደሚጠቁና ከቦረና፣ ጉጂ፣ ምዕራብ ጉጂ፣ ባሌ፣ ምሥራቅ ባሌ፣ አርሲ፣ ምዕራብ አርሲ፣ ምሥራቅ ሸዋ፣ ምዕራብ ሐረርጌና ምሥራቅ ሐረርጌ ዞኖች ከ100 ሺሕ በላይ ነዋሪዎች ሊፈናቀሉ እንደሚችሉ ሪፖርቱ አስቀምጧል፡፡

በአፋር ከልል 83 ሺሕ ያህል ሰዎች ለጉዳት ሊጋለጡ እንደሚችሉና በበርካታ ዞኖች 62 ሺሕ ሰዎች ሊያፈናቅሉ እንደሚችሉ ተገልጿል። ክልሉን የጎበኙ አጋሮችና ለጋሽ ድርጅቶች ከአፋጣኝ የሰብዓዊ ዕርዳታ በተጨማሪ ውጤታማ የሆኑ የቅድመ ማስጠንቀቂያ ሥርዓቶችን መተግበር የእርሻ ሥርዓቱንም ሆነ የአርብቶ አደሩን ሕይወት እንደሚጠብቅ ጠቁመዋል።

በተመሳሳይ በአማራ ከልል 45 ሺሕ የሚጠጉ ሰዎች ጉዳት ይደርስባቸዋል ተብሎ የሚጠበቅ ሲሆን፣ በስሜን ወሎ፣ በደቡብ ወሎና በኦሮሚያ ልዩ ዞን ሦስት ሺሕ ሰዎች በጎርፍ አደጋው ምክንያት ይፈናቀላሉ። ሪፖርቱ የተመለከተው ሌላኛው ቦታ የትግራይ ክልል ሲሆን፣ 4000 ገደማ ሰዎች ጉዳት ይደርስባቸዋል በሚል አስቀምጦ፣ በደቡብና ደቡብ ምሥራቅ 1000 ሰዎች የመፈናቀል ዓውድ ውስጥ ይገባሉ ብሏል።

በኦቻ ሪፖርት ላይ እንደተገለጸው፣ አንዳንድ አካባቢዎች ከባድ ዝናብና የጎርፍ መጥለቅለቅ የሚያስከትለውን ጉዳት እየዘገቡ ሲሆን፣ በሰሜን ሸዋ ዞን ሸዋ ሮቢት ቀበሌ ባለፈው ወር መጨረሻ ሳምንት አካባቢ በተከሰተው ከባድ ዝናብና የጎርፍ መጥለቅለቅ 446 ቤተሰቦች ንብረታቸውና የእርሻ መሬታቸው ወድሞባቸዋል።

በተመሳሳይ ኦሮሚያ ክልል አርሲ ዞን በሚያዚያ ወር የአዋሽ ወንዝ በመሙላቱ በመርቲ ቀበሌ በርካታ ቤተሰቦች ላይ ከፍተኛ ጉዳት መድረሱንም ዘገባዎች አመላክተዋል። ከዚህም ባሻገር በዚሁ ዞን የሚገኘው የጀጁ ቀበሌ በጎርፍና በአውሎ ንፋስ ጉዳት የደረሰበት ሲሆን ቁጥራቸው በውል የማይታወቅ ሰዎች መፈናቀላቸውም ሪፖርት ተደርጓል፟ ብሏል።

ምንም እንኳን የገንዘብ እጥረት ቢያጋጥምም የሰብዓዊ ድጋፍ ሰጪ ተቋማት ከአደጋ ሥጋት ሥራ አመራር ኮሚሽን ጋር በጋራ በመሆን ጉዳቱን ለመቀነስ እየሠሩ መሆናቸው የተገለጸ ሲሆን ዕርዳታ ለሚያስፈልጋቸው ዜጎች ለመድረስና ለአደጋው ፈጣን ምላሽ ለመሰጠት የገንዘብ ድጋፍ ማግኘት አስፈላጊ መሆኑ በሪፖርቱ ተጠቁሟል።

ከዚሁ ጋር በተገናኘ በአዲስ አበባ ከተማ ሚያዚያ 21 ቀን 2016 ዓ.ም. ንጋት ላይ የጣለውን ዝናብ ተከትሎ በተከሰተ የጎርፍ አደጋ የአራት ሰዎች ሕይወት ማለፉን የአዲስ አበባ የእሳትና አደጋ ሥጋት ሥራ አመራር ኮሚሽን ማስታወቁ አይዘነጋም።