የአሜሪካ ብሔራዊ ደህንነት ምክር ቤት ቃለ አቀባይ ጆን ኪርቢ

ከ 7 ሰአት በፊት

አሜሪካዊው ወታደር በሩሲያ በስርቆት ተወንጅሎ በቁጥጥር ስር መዋሉን የአሜሪካ ጦር አስታወቀ።

ወታደሩ መቀመጫው በደቡብ ኮሪያ እንደሆነም ተነግሯል።

ጎርደን ብላክ የተሰኘው ወታደር ከአንዲት ሴት ላይ በመስረቅ ወንጀል እንደተከከሰሰ የቢቢሲ አጋር ሲቢኤስ ዘግቧል።

ወታደሩ ከቀናት በፊት በምስራቅ ሩሲያ በምትገኘው ቭላዲቮስቶክ ከተማ በቁጥጥር ስር የዋለ ሲሆን በአገሪቱም የነበረው ጉብኝት የስራ አይደለም ተብሏል።

የአሜሪካ ብሔራዊ ደህንነት ምክር ቤት ቃለ አቀባይ ጆን ኪርቢ ወታደሩ በቁጥጥር ስር ስለመዋሉና ሌሎች ከሩሲያ ጋር የተያያዙ ጉዳዮች እንደሚያውቁ ተናግረዋል።

ቃለ አቀባዩ ሰኞ እለት በነበረው የዋይት ሐውስ አጭር መግለጫ ላይ ተጨማሪ ዝርዝር መረጃዎች መስጠት አልችልም ብለዋል።

የአሜሪካ ጦር ባወጣው መግለጫ ወታደሩ በወንጀል ክስ ቀርቦበታል ብሏል።

“ጦሩ ለቤተሰቡ ያሳወቀ ሲሆን የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር በሩሲያ ለተከሰሰው ወታደር ተገቢውን የቆንስላ ድጋፍ እያደረገ ነው” ሲሉ ቃለ አቀባይዋ ሲንቲያ ስሚዝ ተናግረዋል።

ወታደሩ ከደቡብ ኮሪያ ወደ አሜሪካ ቴክሳስ፣ ፎርት ካዘቮስ ለመዘዋወር በሂደት ላይ የነበረ መሆኑን ሲቢኤስ ዘግቧል።