ሒሩት ገብረ ሥላሴ ምክትል ዋና ኮሚሽር

ዜና በአገራዊ ምክክር ወቅት ተሳታፊዎች በሚያነሷቸው ሐሳቦች በወንጀል እንዳይጠየቁ ዋስትና ሊሰጥ ነው

ፅዮን ታደሰ

ቀን: May 29, 2024

አገራዊ የምክክር ኮሚሽን በሚያካሂዳቸው የምክክር ምዕራፍ ሒደቶች የሚሳተፉ የየትኛውም የማኅበረሰብ ክፍል ተወካዮች፣ በሚያነሷቸው ሐሳቦች በወንጀል ተጠያቂ እንዳይሆኑ ዋስትና እንደሚሰጥ ገለጸ፡፡ 

ኮሚሽኑ ከትናንት በስቲያ ሰኞ ግንቦት 19 ቀን 2016 ዓ.ም. በሰጠው መግለጫ እንዳስታወቀው፣ ክልላዊ የምክክር ምዕራፍ ረቡዕ ግንቦት 21 ቀን 2016 ዓ.ም. ይጀምራል፡፡ ተሳታፊዎች በሚሰጡት አስተያየት ወይም በምክክር ሒደቱ ወቅት በሚሰነዝሩት ሐሳብ፣ በወንጀል ተጠያቂ እንዳይሆኑ ኮሚሽኑ ከለላ ወይም ዋስትና እሰጣለሁ ብሏል፡፡ 

የአገራዊ ምክክር ኮሚሽን የተቋቋመው ከፖለቲካ ፓርቲዎችና ከሲቪል ማኅበራት በቀረበ ጥያቄ መሠረት መንግሥት አምኖበት መሆኑን የገለጹት ምክትል ዋና ኮሚሽር ሒሩት ገብረ ሥላሴ፣ በአዋጅ እንዲቋቋም ሲደረግም በሒደቱ የሚሳተፉ ባለድርሻ አካላት ለሚያደርጉት ተሳትፎ ዋስትና እንደሚሰጣቸው፣ ከመንግሥት ጋር በመነጋገር መግባባትና መተማመን የተደረሰበት መሆኑን ጠቁመዋል፡፡ 

‹‹በምክክር ሒደቱ ላይ በሚሰጥ አስተያየት ወይም ሐሳብ ምክንያት ምንም ዓይነት ተጠያቂነት እንደማይኖር ኮሚሽኑ ያረጋግጣል፣ በዚህ ሥጋት ሊኖር አይገባም፤›› ብለዋል፡፡ 

በጉዳዩ ላይ ተጨማሪ ማብራሪያ የሰጡት ኮሚሽነር አቶ ጌታቸው ሽፈራው በበኩላቸው፣ ‹‹በምክክሩ ወቅት ሐሳባቸውን የሚያቀርቡ ተሳታፊዎች በወንጀል ተጠያቂ እንዳይሆኑ ኮሚሽኑ ዋስትና ይሰጣል ሲባል፣ በአገሪቱ ሕግ የተከለከሉና የአገሪቱን ሰላምና ደኅንነት የሚያናጉ ተግባራትን የሚፈጽሙ ግለሰቦች በሕግ አይጠየቁም ማለት አይደለም፤›› ብለዋል።

‹‹በተሳታፊዎች መካከል ሁከትንና ብጥብጥን የሚያስነሳ ተግባር የፈጸመ ግለሰብ በአገሪቱ ሕግ መሠረት ሊጠየቅ ይችላል፤›› ያሉት አቶ ጌታቸው፣ በሒደቱ ላይ የሕግ የበላይነትን ማስከበርም የኮሚሽኑ ኃላፊነት መሆኑ መዘንጋት የለበትም ሲሉ አስረድተዋል፡፡ 

አገራዊ የምክክር ኮሚሽን በአዲስ አበባ ከተማ በሚያካሂደው የምክክር ምዕራፍ ከተለያዩ የማኅበረሰብ ክፍሎች የተውጣጡ ከ2‚500 በላይ ተሳታፊዎች እንደሚኖሩ የተገለጸ ሲሆን፣ በሒደቱም ተሳታፊዎች የአጀንዳ ግብዓቶቻቸውን እንደሚያዘጋጁና በአገራዊ ጉባዔው የሚወክሏቸውን ተሳታፊዎች እንደሚመርጡ ተጠቁሟል፡፡ 

በሒደቱ ላይ በዋናነት ሦስት ዋና ዋና ተግባራት እንደሚከናወኑ፣ የመጀመሪያው ሒደት ተሳታፊዎች የአጀንዳ ሐሳቦችን የሚመርጡበት መሆኑ፣ ሁለተኛው ሒደትም አጀንዳዎቻቸውን የጋራ በማድረግ ማሰባሰብ፣ ማደራጀትና የመፍትሔ ሐሳብ ማንሸራሸር፣ በመጨረሻም ለአገራዊ ምክከር ጉባዔ ተሳታፊ የሚሆኑ ተወካዮችን መምረጥ መሆኑ ተመላክቷል፡፡ 

በአዲስ አበባ ከተማ የሚደረገው የምክክር ምዕራፍ እንደተጠናቀቀ ቢያንስ በሦስት ክልሎች የምክክር ምዕራፉ እንደሚከናወን፣ የሎጂስቲክ ሥራዎችን በማጠናቀቅ በሌሎች ክልሎችም ተግባራዊ እንደሚደረግ ተገልጿል፡፡ 

በኮሚሽኑ ላይ በተደጋጋሚ የሚነሳው የአካታችነት ጥያቄን አስመልክቶ በመግለጫው ላይ ማብራሪያ የተሰጠበት ሲሆን፣ ለዚህ ጥያቄ ምላሽ ለመስጠት ዕድሮችን፣ ተፈናቃዮችን፣ የሃይማኖት ተወካዮችን፣ የፖለቲካ ፓርቲዎችን፣ እንዲሁም የተገለሉ የማኅበረሰብ ክፍሎችን ለማሳተፍ ከፍተኛ ጥረት መደረጉ ተመላክቷል፡፡