

የሙስና ሥጋት ተጋላጭነት ጥናት ይፋ በተደረገበት ወቅት
ዜና ፕላንና ልማት ሚኒስቴርንና ተጠሪ ተቋማትን ለሙስና የሚያጋልጡ ክፍተቶች ይፋ ተደረ
ቀን: June 2, 2024
የሥነ ምግባርና ፀረ ሙስና ኮሚሽን በፕላንና ልማት ሚኒስቴርና በሚቆጣጠራቸው ተቋማት ውስጥ፣ ለሙስና ተጋላጭ የሚያደርጉ የአሠራር ክፍተቶችና ከሕግ ውጪ የሚደረጉ በርካታ የሕግ ጥሰቶችን ይፋ አደረገ፡፡
ኮሚሽኑ የፕላንና ልማት ሚኒስቴርና በውስጡ ያሉ የዘርፍ ተቋማትን በተመለከተ ያካሄደው የሙስና ሥጋት ተጋላጭነት ጥናት ውጤት ላይ፣ ግንቦት 21 ቀን 2016 ዓ.ም. የሁሉም ተቋማት ኃላፊዎች በተገኙበት ውይይት አካሂዷል፡፡
የተጋላጭነት ጥናት ሪፖርቱ በፕላንና ልማት ሚኒስቴርና በሚቆጣጠራቸው የኢትዮጵያ ስታትስቲክስ አገልግሎት፣ የፖሊሲ ጥናት ኢንስቲትዩትና የአካባቢ ጥበቃ ባለሥልጣን ላይ የተካሄደ መሆኑን ጥናቱን ያቀረቡት የኮሚሽኑ የአስቸኳይ ሙስና መከላከል መሪ ሥራ አስፈጻሚ አቶ ገዛኸኝ ጋሻው ተናግረዋል፡፡
በጥናቱ ከተለዩት ግኝቶች መካከል በሚኒስቴሩ ተቋማት ሥር ባሉት የሥነ ምግባር ክፍሎች ከሌሎች የተቋም አደረጃጀቶች በተለይ ከሕግ፣ ከተቋማዊ ለውጥና ከኦዲት ጋር በቅንጅት የሚሠራበት መደበኛ አሠራር አለመኖር፣ እንዲሁም በሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ የሕግ ክፍል ውሎችን መገምገም የሚችል ባለሙያ አለመደራጀቱን አቶ ገዛኸኝ ያቀረቡት ሰነድ ያመላክታል፡፡
በዘርፉ የሚወጡ አዋጆች፣ ደንቦችና መመርያዎች በሚፈለገው መጠን ተግባራዊ በማድረግ የተጠያቂነት ሥርዓትን አለማስፈን፣ የፕላስቲክ ፈቃድ አሰጣጥና ቁጥጥር፣ እንዲሁም የደረቅ ቆሻሻ አያያዝ፣ አጓጓዝ፣ አወጋገድና የቁጥጥር ሥርዓት ውጤታማነት በተመለከተ ዘርፉ ከሚመለከታቸው መሥሪያ ቤቶች፣ ከክልሎችና ከከተማ አስተዳደሮች ጋር ቅንጅታዊ አሠራር ሥርዓት ዘርግቶ ተግባራዊ ያላደረገ መሆኑ በሪፖርቱ ተገልጿል፡፡ ለአብነትም ረጲ የኤሌክትሪክ ኃይል ማመንጫ ሥራውን ካቆመ ከሦስት ወራት በላይ ቢሆነውም በዘርፉ የሚደረግ ክትትልና ድጋፍ አለመኖሩን፣ ፕሮጀክቱ ሲቋቋም በሰዓት 50 ሜጋ ዋት ለማምረት የተጠና ቢሆንም ሲያመርት የነበረው ግን ከ13 ሜጋ ዋት ያነሰ እንደነበር የገለጹት አቶ ገዛኸኝ፣ በጥናቱ ጊዜ ፕሮጀክቱ ኃይል ማመንጨት ማቆሙንና በዘርፉ የሚደረግ ክትትልና ድጋፍ አለመኖሩ፣ በማሳያነት አቅርበዋል፡፡
በአካባቢ ጥበቃ ዘርፍ ከሁሉም ሠራተኞች ጋር ዓመታዊ ዕቅድና በጀት ዙሪያ ውይይት እንደማይደረግ፣ የሚወሰኑ ውሳኔዎች በቃለ ጉባዔ ተደግፈው ተደራሽ አለመሆናቸው፣ የሚሰጡ ውሳኔዎች አሳታፊና ተጠያቂነት ባለው መንገድ አለማከናወን የሚሉት ክፍተቶች በጥናት የተረጋገጡ የአሠራር ክፍተቶች ናቸው ብለዋል፡፡
የሚወጡ ሕጎች ተግባራዊ መሆናቸውን በመከታተል ግልጽነትና ተጠያቂነት እንደማይረጋገጥ፣ የልማት ፕሮጀክቶት ባለቤት ወደ ትግበራ ከመግባቱ በፊት የአካባቢና ማኅበረሰብ ተፅዕኖ ግምገማ በማካሄድ ከሚመለከተው የአካባቢ ጥበቃ መሥሪያ ቤት ፈቃድ ማግኘቱን፣ እንዲሁም የአካባቢና የማኅበረሰብ ተፅዕኖ ግምገማ የይሁንታ ፈቃዶች በሕጉ መሠረት እየተገበሩ መሆናቸውን እንደማይረጋገጥም ተመላክቷል፡፡
በዘርፉ የግዥ አፈጻጸም ሪፖርት ግምገማ መሠረት ያለ ፕሮፎርማና ያለ ዕቅድ በተደጋጋሚ የሚፈጸሙ ግዥዎች መኖራቸው፣ የግዥ ዕቅድና አፈጻጸም ለብቻው ትኩረት ተሰጥቶት ዓመታዊ ግምገማ የማይካሄድበት መሆኑ፣ ከአንድ አቅራቢ በተደጋጋሚ ግዥ ስለመፈጸሙና ምክንያቱን የሚገልጽ መረጃ አለመቅረቡንም አቶ ገዛኸኝ አስረድተዋል፡፡
በሚኒስቴሩ ሥር የሚገኙ ተቋማት ሐሰተኛ የትምህርትና የሥራ ልምድ የማጣራት ሥራ እንደማያከናውኑ፣ የሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ የፕሮጀክት ሠራተኞች ያለ ውድድር የሚመደቡ መሆናቸው፣ ግዥዎቹ ለምን በግልጽ ጨረታ እንዳልተከናወኑ፣ ሳይታቀዱ እንደተገዙና ከአንድ አቅራቢ እንደተገዙ ምክንያቱን የሚገልጽ መረጃ አለመቅረቡ፣ ፕሮጀክቶች ከተያዘላቸው ጊዜና በጀትና በላይ የሚወስዱ መሆናቸው፣ የተቋማት አመራሮች በኦዲት ግኝት ላይ ተመሥርተው የእርምት ዕርምጃ በአግባቡ አለመውሰዳቸው፣ እንዲሁም አራት አመራሮች ሀብታቸውን አሳውቀው አለማስመዝገባቸው በሪፖርቱ ተመላክቷል፡፡
በመድረኩ የተገኙት የሥነ ምግባርና የፀረ-ሙስና ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነር አቶ እሸቴ አስፋው፣ ያለ ፕሮፎርማና ያለ ዕቅድ የሚከናወኑ ግዥዎች፣ ፕሮጀክቶች ከታቀደላቸው ጊዜና ሀብት በላይ መጠየቃቸውና መራዘማቸው መቆም አለበት ብለዋል፡፡
በጥናቱ ለተብራሩት ክፍትቶች ምላሽ የሰጡት የፕላንና ልማት ሚኒስትር ፍፁም አሰፋ (ዶ/ር) ተጋላጭ የሚያደርጉ አሠራሮችን እንደሚፈተሹ፣ ከአዋጅና ከግዥ ጋር የተገናኙ ከፍተቶች እንደሚስተካከሉ፣ የጎደለ የሰው ኃይል መንግሥት በጊዜያዊነት ቅጥር እንዲቆም ከመወሰኑ ጋር የተገናኘ መሆኑን፣ ነገር ግን የሚለቁ ሠራተኞችን የመተካት ሥራ እንደሚከናወን አስረድተዋል፡፡
በኮሚሽኑ ባለፉት ጥቂት ዓመታት ብቻ በሀብት ምርመራ ሒደት 5.5 ቢሊዮን ብር፣ 905 ተሽከርካሪዎች፣ 234 ቤቶችና 133,916 ካሬ ሜትር ቦታ እንዲታገዱ መደረጋቸውንና የመያዣ ትዕዛዝ ከወጣባቸው ንብረቶች መካከል ተጠቅሰዋል፡፡