October 13, 2024 

የሚኖርበት ቤት ለልማት በሚል የፈረሰበት እና ስራ እንዳይሰራ የተከለከለ ወጣት ራሱን አጠፋ

(መሠረት ሚድያ)- ነዋሪነቱ አዲስ አበባ ኡራኤል አካባቢ የሆነ አዲሱ ካሳሁን የተባለ ወጣት ከኡራኤል ቤተክርስቲያን ወደ አትላስ ሆቴል በሚወስደው መንገድ አካባቢ በሚገኘው ‘በፀጋህ ሆስፒታል’ ፊት ለፊት ነዋሪ ሲሆን ከትናንት በስቲያ ራሱን አጥፍቷል።

አዲሱ ነጠላ ከሚሸጥበት ኡራኤል ቤተከርስቲያን አካባቢ ስራ እንዳይሰራ ሁለት ግዜ በደንብ አስከባሪዎች ተባሮ እና ንብረቱም ተወስዶበት እንደነበር የአካባቢው ነዋሪዎች እና የቅርብ ሰው ለመሠረት ሚድያ ተናግረዋል።

ከዚህም በተጨማሪ ከትናንት በስቲያ ምሽት ማታ ወደ ቤቱ ሲገባ የሚኖርበት ቤት በነጋታው ጠዋት እንደሚፈርስ ሲነገረው ተስፋ በመቁረጥ ስሜት እዛው ቤቱ ውስጥ ራሱን እንዳጠፋ ለመሠረት ሚድያ ከአካባቢው ነዋሪዎች የደረሰው ጥቆማ ያሳያል።

የልጅ አባት የሆነው እና በቅርቡ የወለደች ባለቤት ያለው ወጣቱ ይህን ድርጊት ከፈፀመ በኋላ ትናንት ስድስት ሰአት ላይ በኡራኤል ቤተክርስቲያን ቀብሩ እንደተፈፀመ ሰምተናል።