
ከ 9 ሰአት በፊት
በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ውስጥ በሚገኘው ጫሞ ሐይቅ ላይ ሲጓዝ የነበረ ጀልባ ተገልብጦ ከአስር በላይ ሰዎች የደረሱበት አለመታወቁ ተገለጸ።
ሐሙስ ጥቅምት 7/2017 ዓ.ም. ከቀኑ 10 ሰዓት አካባቢ ከአርባ ምንጭ በጫሞ ሐይቅ ላይ ሙዝ እና 16 ሰዎችን አሳፍሮ ሲጓዝ የነበረው ጀልባ ተገልብጦ 13 ሰዎች የደረሱበት አለመታወቁን የጋሞ ዞን ፖሊስ ለቢቢሲ ገለጸ።
ሰዎች እና ምርት ጭኖ ሲጓዝ የነበረው ጀልባ የተነሳው ከኮሬ ዞን አቡሎ አርፋጮ ከሚባል አካባቢ ሲሆን መድረሻውም አርባ ምንጭ ከተማ እንደነበር ጋሞ ዞን ፖሊስ መመሪያ የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊ ኮማንደር ረታ ተክሉ ለቢቢሲ ተናግረዋል።
በጀልባው ላይ ሹፌሩን ጨምሮ 16 ሰዎች ሙዝ ጭነው ወደ አርባምንጭ ከተማ እየመጡ ነበር ያለው ፖሊስ፤ አደጋው ሲደርስ ሁለቱ ሰዎች ጀሪካን ይዘው በመንሳፈፍ ሕይወታቸውን ማትረፍ መቻላቸውን ይናገራሉ።
ተጨማሪ አንድ ሰው ወደ ሐይቁ ዳርቻ እየዋኘ ተሻግሮ በፍለጋው ወቅት በሕይወት መገኘቱን አክለው ገልጸዋል።
ኮማንደር ረታ ተክሉ ጀልባው የተገለበጠው ሐሙስ ዕለት ቢሆንም ስለአደጋው ለፖሊስ ጥቆማ የተሰጠው ግን ዛሬ አርብ ማለዳ ላይ መሆኑን ተናግረዋል።
- ሐማስ መሪው ያህያ ሲንዋር መገደሉን አረጋግጦ ትግሉን እንደሚቀጥል አስታወቀ18 ጥቅምት 2024
- በሰሜን ጎጃም ዞን ድሮንን ጨምሮ በተፈጸሙ ጥቃቶች በርካታ ሰዎች መገደላቸውን የዓይን እማኞች ተናገሩ18 ጥቅምት 2024
- በሁለት ሳምንት ውስጥ በአማራ ክልል 11 ዳኞች መታሰራቸው ተነገረ18 ጥቅምት 2024
አደጋውን ተከትሎ በሐይቁ ላይ ጄሪካን ይዘው በሕይወት መትረፍ የቻሉት ሁለት ሰዎችም ሆኑ ዋኝቶ መውጣት የቻለው አንድ ግለሰብ በመልካም ጤንነት ላይ እንደሚገኙ ፖሊስ አስታውቋል።
የአደጋው መንስኤ ከጀልባው አቅም በላይ መጫን ሳይሆን እንዳልቀረ የተነገረ ሲሆን፣ በጀልባው ላይ የነበሩት ተሳፋሪዎች የቀን ሠራተኞች መሆናቸውን ኮማንደር ረታ ለቢቢሲ ገልጸዋል።
የጋሞ ዞን መንግሥት ኮሚዩኒኬሽን በበኩሉ 15ቱ የቀን ሠራተኞች ሙዝ ለመጫን ወደ ስፍራው የሄዱት ከአርባ ምንጭ ዙሪያ መሆኑን የጠቀሰ ሲሆን፣ ኮማንደር ረታ በበኩላቸው ማንነታቸውን የመለየት ሥራ እንደሚሠራ ተናግረዋል።
በጫሞ ሐይቅ ላይ አደጋው መድረሱን ለፖሊስ ከተገለጸ በኋላ ፍለጋ እየተደረገ ቢሆንም፣ እስካሁን ድረስ በሕይወት የተረፉም ሆነ የሞቱ ሰዎችን ማግኘት አለመቻሉን ፖሊስ አመልክቷል።
በጀልባ አደጋው ሐይቁ ውስጥ የሰመጡትን 13 ሰዎች የደረሱበትን ለይቶ ለማግኘት ጥረት እየተደረገ ሲሆን፣ የአርባ ምንጭ ፖሊስ እና የከተማው ማኅበረሰብ በፍለጋው ላይ ተሰማርተው ጥረት እያደረጉ መሆናቸውን ኮማንደር ረታ ገልጸዋል።