የካናዳ ዜግነትን ያገኙ የውጭ ዜጎች
የምስሉ መግለጫ,ባለፉት ዓመታት ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው የውጭ ዜጎች ወደ ካናዳ ከመግባታቸው በተጨማሪ በርካቶች የካናዳ ዜግነትን አግኝተዋል

ከ 6 ሰአት በፊት

ካናዳ ለበርካታ አስርት ዓመታት ራሷን ለአዲስ መጤዎች ክፍት የሆነች አገር አድርጋ ቆይታለች:: የስደተኞች ፖሊሲዎቿም የሕዝቧን ብዛት ለማሳደግ፣ የሠራተኛ ክፍተቶችን ለመሙላት እና ከዓለም ዙሪያ ግጭቶችን የሚሸሹ ስደተኞችን ለመቀበል ታስበው የተዘጋጁ ናቸው።

ነገር ግን ከቅርብ ወራት ወዲህ ጠቅላይ ሚኒስትር ጀስቲን ትሩዶ የማኅበራዊ አገልግሎቶች አቅርቦት ተደራሽ ያለመሆን፣ ከፍተኛ የኑሮ ውድነት እና እጅግ ውድ የሆነ መኖሪያ ቤት አቅርቦትን በተመለከተ በሕዝቡ ዘንድ እየጨመረ የመጣውን ስጋት ተከትሎ ካናዳ ወደ ግዛቷ እንዲገቡ የምትፈቅደው የስደተኞች ቁጥርን በከፍተኛ ሁኔታ ለመቀነስ እንዳሰቡ አሳውቀዋል።

ጠቅላይ ሚኒስትሩ በአውሮፓውያኑ 2015 ለሥልጣን በተወዳደሩበት ጊዜ ለአገሪቱ እና ለራሳቸው ዋነኛ የፖሊሲ አቅጣጫ ለውጥ በማድረግ ብዝኅ ባሕልን ማስፋፋት የካናዳ ቁልፍ የማንነት መገለጫ እንዲሆን አጀንዳ ይዘው ነበር።

የትሩዶ መንግሥትም የአገሪቱን የምጣኔ ሀብት ዕድገትን ለማፋጠን ከፍተኛ ተስፋ በጣሉበት የኢሚግሬሽን ግቦች ላይ መሠረት አድርገው ነበር።

በዚህ ፖሊሲያቸው ትችት የበዛባቸው እና ፖለቲካዊ ተቀባይነታቸው እያሽቆለቆለባቸው ያለው ጠቅላይ ሚኒስትሩ አሁንመንግሥታቸው የተሳሳተ ስሌት እየተከተለ እንደነበረ እና የካናዳ መሠረተ ልማቶች ከሕዝቡ ብዛት ጋር የተታጣሙ ሆነው እንዲቀጥሉ ለማድረግ የሕዝብ ብዛቱን “ማረጋጋት” አስፈላጊ መሆኑን አምነዋል።

ባለፈው ሐሙስ ጠቅላይ ሚኒስትር ትሩዶ እና የኢሚግሬሽንሚኒስትር ማርክ ሚለር ከዚህ በፊት ከነበሩት በበለጠ በጣም ጥብቅ የሆነ የኢሚግሬሽን ቁጥርን የሚቀንስ ዕቅድ አቅርበዋል። በዚህም በቀጣዩ የአውሮፓውያን ዓመት በቋሚ ነዋሪነት ወደ ካናዳ ይገባሉ ተብሎ ከተያዘው ቁጥር በ21 በመቶው ይቀንሳል።

የአገሪቱ ከፍተኛ ባለሥልጣናት ይህንን በቋሚነት ወደ ካናዳ የሚገቡ ስደተኞች ቁጥርን የሚቀንሰውን ዕቅዳቸውን ካሳወቁ በኋላ ጊዜያዊ የውጭ አገር ሠራተኞች እና የዓለም አቀፍ ተማሪዎችን ጨምሮ በጊዚያዊ የመኖሪያ ፈቃድ የሚገቡት ሰዎች ቁጥርም ይቀንሳል።

ጠቅላይ ሚኒስትር ትሩዶ የአዲሱን ፖሊሲያቸውን ለውጥ ሲያብራሩ ካናዳውያን ስደተኞችን ተቀባይ በሆነው ሥርዓታቸው “ምክንያታዊ በሚባል ደረጃ ኩራት ይሰማቸዋል” ብለዋል።

ይህ ፖሊሲያቸውም “ምጣኔ ሀብታችንን ዓለም የሚቀናበት አድርጎታል” በማለት “በዚህም ጠንካራ እና ብዝሃነት ያለው ማኅበረሰብ እንዴት እንደሚገናባ አሳይቷል።”

ነገር ግን ትሩዶ ከኮቪድ-19 ወረርሽኝ በኋላ የሠራተኛ እጥረትን ለማቃለል በርካታ ጊዜያዊ ነዋሪዎችን አገሪቱ ስትቀበል መንግሥታቸው “ሚዛኑን በትክክል አልጠበቀም ነበር” ሲሉ አምነዋል። ስለዚህም አሁን የካናዳ የኢሚግሬሽን ሥርዓትን“ማረጋጋት” ያስፈልጋል ብለዋል።

የጠቅላይ ሚኒስትሩ አዲስ ዕቅድ ይፋ የሆነው ትሩዶ የተከተሉት የኢሚግሬሽን ፖሊሲ በካናዳ የሕዝብ ዘንድ ያለው ድጋፍ እየቀነሰ በመምጣቱ ምክንያት ነው።

ከአውሮፓውያኑ 1977 ጀምሮ የካናዳውያን ከኢሚግሬሽን አንጻር ያላቸውን አመለካከት የተከታተለው የኢንቫይሮኒክስ ኢንስቲትዩት በመስከረም ወር ላይ ባሰባሰበው የሕዝብ አስተያየት፣ ከሩብ ምዕተ-ዓመት ወዲህ ለመጀመሪያ ጊዜ አብዛኞቹ የአገሪቱ ዜጎች ስደተኞች በጣም በዝተዋል ይላሉ።

ተቋሙ እንደሚለው የዚህ አመለካከት ለውጥ በዋናነት የሚመነጨው የመኖሪያ ቤት እጥረት በፈጠረው ስጋት ነው። ነገር ግን ኢኮኖሚው፣ የሕዝብ መብዛት እና የኢሚግሬሽን ሥርዓቱ የተያዘበት መንገድ በተጨማሪ በትልቅ ምክንያትነት ተጠቅሰዋል።

የካናዳ ዓርማ

በጥቅምት ወር በወጣው የአባከስ ዳታ የሕዝብ መለኪያ ላይ አስተያየቱን የሰጠው ዴቪድ ኮሌቶ “በስደት ዙሪያ በሕዝቡ ዘንድ ያለው መግባባት እየተከፋፈለ ነው” የሚለው ሃሳብ ቅሬታውን ቀለል አድርጎ የሚያሳይ ነው በማለት ተችቷል።

“እኔ እንደማስበው ያ የነበረው መግባባት አሁን የለም የሚያስብል ሲሆን በሚቀጥለው ዓመት በፌዴራል እና በግዛቶች ፖለቲካ ውስጥ በጣም ወሳኝ ከሆኑ ጉዳዮች ውስጥ አንዱ እንደሚሆን እጠብቃለሁ” ብሏል።

ካናዳ ከዓለም ዙሪያ ስደተኞችን በስፋት ስትቀበል ቆይታለች። መረጃዎች እንደሚያሳዩት ስደተኞችን በመቀበል እና መልሶ በማቋቋም ረገድ በዓለም መሪ ከመሆኗ በተጨማሪ አገሪቱ ባለፉት 50 ዓመታት ውስጥ አዲስ ስደተኞችን ተገቢውን ቦታ የምትሰጥ የመባል ዝናን አግኝታለች።

በአውሮፓውያኑ 1988 የወጣው የካናዳ የብዝሃ ባሕል አገርነት ሕግ ብዝሃነትን የካናዳ ማንነት ዋነኛ ማንነት አካል አድርጎ ይቀበላል።እንዲሁም የአገሪቱ ሕገ መንግሥት የብዝሃ ባሕል ማንነትን እውቅና ሰጥቶ ጥበቃ ያደርጋል።

በቶሮንቶ ዩኒቨርስቲ የፖለቲካ ሳይንስ ፕሮፌሰር የሆኑት ማይክል ዶኔሊ ለቢቢሲ እንደተናገሩት “ከ1990ዎቹ መጨረሻ አንስቶ በካናዳውያን ዘንድ ያለው አመለካከት ስደተኞችን በአዎንታዊ የሚመለከት ሆኖ ቆይቷል” ብለዋል።

በ2019 የተደረገው የፒው ምርምር ሪፖርት ከጠቀሳቸው 10 የስደተኞች መዳረሻ አገራት መካከል ካናዳ ለስደተኞች ከሁሉም አገራት በበለጠ አዎንታዊ አመለካከት አላት ብሏል።

ፕሮፌሰር ዶኔሊ እንደሚሉት ስደተኞች በካናዳ ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው መራጮች በመሆናቸው፣ ዋነኛ ፖለቲካ ፓርቲዎች ፀረ ስደተኛ የሆነ አቋም እንዳይዙ አድርጓቸዋል።

ካናዳ እንዲሁ ከቁጥጥር ውጭ በሆነ ፍልሰት ሌላ ቦታ ያጋጠማት ችግር – የጂኦግራፊዋ ጥቅም ፣ በሶስት ውቅያኖሶች እና በአሜሪካ ወደ ደቡብ መከበቧ – እና የኢሚግሬሽን ስርአቷ በሕዝብ ዘንድ ክፍት እና በደንብ የተስተካከለ ተደርጎ ይታይ ነበር።

ካናዳ በሌሎች አገራት የሚያጋጥመው ዓይነት ከቁጥጥር ውጪ የሆነ ፍልሰት እምብዛም አልፈተናትም፤ ለዚህም መልክዓ ምድራዊ አቀማመጧ ጠቅሟታል። በሦስት ውቅያኖሶች እና በደቡብ በኩል በአሜሪካ መከበቧ እንዲሁም የኢሚግሬሽን ሥርዓቷ ክፍት እና በአግባቡ የተያዘ ነው ተብሎ በሕዝቡ ይታመን ስለነበረ ነው።

ነገር ግን ይህ አዎንታዊ አመለካከት ባለፉት ጥቂት ዓመታት ተቀይሯል ይላሉ ፕሮፌሰር ዶኔሊ።

ለዚህ አንዱ ምክንያት ደግሞ ታይቶ በማይታወቅ ሁኔታ ያሻቀበው በጊዜያዊነት ወደ ካናዳ የሚመጡት ሰዎች ቁጥር መጨመር ነው።

ከ2022 እስከ 2023 ባለው ጊዜ የዓለም አቀፍ ተማሪዎች ቁጥር በ30በመቶ ገደማ ማደጉን የካናዳ ዓለም አቀፍ ትምህርት ቢሮ አስታውቋል። ይህ በእንዲህ እንዳለ፣ ባለፉት አምስት ዓመታት በካናዳ የሚገኙ ጊዜያዊ የውጭ ሠራተኞች ቁጥር በእጥፍ መጨመሩን የመንግሥት መረጃዎች ያሳያሉ።

ሌላው ምክንያት ደግሞ በከፊል የካናዳ መንግሥት በፈጸመው የስሌት ስህተት ምክንያት የካናዳ የኢሚግሬሽን ሥርዓት ተአማኒነቱን እያጣ ነው የሚለው ስሜት እያደገ መምጣቱ ነው ይላሉ ፕሮፌሰር ዶኔሊ።

በአውሮፓውያኑ 2016 ካናዳ ከሜክሲኮ ለሚመጡ ቱሪስቶች የቪዛመስፈርቶችን ካስወገደች በኋላ የጥገኝነት ጠያቂዎች ቁጥር አሻቅቧል:: በዚህም ምክንያት ካናዳ ካለፈው ጥር ወዲህ የቪዛ ገደቦችን መልሳ ተግባራዊ ለማድረግ ተገዳለች።

የካናዳ መገናኛ ብዙኃን አንዳንድ ዓለም አቀፍ ተማሪዎች ጊዜያዊ ቪዛቸውን ተጠቅመው በአገሪቱ ውስጥ ቋሚ ጥገኝነት እንደሚጠይቁ ዘግበዋል፤ ይህንን አዝማሚያም የኢሚግሬሽን ሚኒስትሩ ሚለር “አሳሳቢ” ብለውታል።

ፕሮፌሰር ዶኔሊ እነዚህ ክስተቶች እና ሌሎችም “ሰዎች መንግሥት የስደተኞችን ፍልሰት መቆጣጠር እንደቻለ እንዲያስቡ አድርጓቸዋል” ይላሉ።

እነዚህ ሁሉ ስጋቶች በመላ አገሪቱ ካናዳውያንን በነካው የመኖሪያ ቤት ችግር ዙሪያ ያጠነጥናል:: ቤቶች እጥረት የኪራይ እና የቤትዋጋ ለብዙዎች እንዲጨምር አድርጓል።

“ሰዎች ብዙ ቁጥር ያላቸው ስደተኞች ወደ አገሪቱ ሲገቡ እና የመኖሪያ ቤት እጥረት ሲያዩ፣ ይህ በቀጥታ የተያያዘ ነው ብለው ያምናሉ” ብለዋል።

ፕሮፌሰር ዶኔሊ ካናዳ በኢሚግሬሽን ዙሪያ አንዳንድ የዘረኝነት ንግግሮችን ስትመለከት፣ የካናዳውያን የአመለካከት ለውጥ በዋናነት በአውሮፓ አገሮች ወይም በአጎራባች ዩናይትድ ስቴትስ ውስጥ በሚታዩ ስሜቶች የሚመራ እንዳልሆነ ጠቁመዋል።

ይልቁንም፣ ሰዎች ካናዳ የኢሚግሬሽን ሥርዓቷን መልሳ እንድትቆጣጠር ካላቸው ፍላጎት የተነሳ ነው።

አሁን ይፋ በተደረገው ዕቅድ አማካኝነትም “የትሩዶ መንግሥት በግልጽ ‘ችግሩን በቁጥጥር ስር አድርገነዋል’ የሚል መልዕክት ለማስተላለፍ እየሞከረ ነው” ብለዋል ፕሮፌሰር ዶኔሊ።