October 31, 2024

ጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ ዛሬ ሐሙስ ጥቅምት 21፤ 2017 በፓርላማ በነበራቸው ቆይታ፤ ሰፋ ያለ ጊዜ ወስደው ካብሯሯቸው ጉዳዮች ሰላም እና ጸጥታን የተመለከቱት ይገኙበታል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ በዚሁ ማብራሪያቸው፤ “ሰላምን የማይመርጡ” ስላሏቸው ሰዎች አንስተዋል።
“መቶ ፐርሰንት ሰው አመዛዛኝ ስለሆነ፤ ሰላም ይፈልጋል ማለት አይደለም” ያሉት አብይ፤ በዚህም ሳቢያ በአለም ላይ ያሉ መንግስታት፤ ለዜጎቻቸው መኖሪያ ቤት እንደሚገነቡ ሁሉ ማረሚያ ቤት እንደሚገነቡ ጠቅሰዋል። ሆኖም መኖሪያ ቤት መገንባት ብቻውን “ሰላምን አያረጋግጥም” ሲሉ አጽንኦት ሰጥተዋል።

የኢትዮጵያ መንግስት ለደሃ ዜጎች የሚሆኑ 248 ሺህ ቤቶች መገንባቱን የገለጹት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ በዚያው ልክ ማረሚያ ቤት አለመገንባቱን ተናግረዋል። “ቁጥሩ ቢያንስም” ማረሚያ ቤት መገንባት እንደሚያስፈልግም ማብራሪያቸውን ለተከታተሉት የፓርላማ አባላት አስገንዝበዋል።
“አብዛኛው መኖሪያ ቤት፣ አብዛኛው የንግድ ቦታ፣ አብዛኛው ለውጥ የሚያመጣ [ቢገነባም]፤ ትንሽም ቢሆን ግን ማረሚያ ቤት ደግሞ ያስፈልጋል። ይሄንን balance መጠበቅ አስፈላጊ ነው። ምክንያቱም ‘ሰው ሁሉ ሰላም ይፈልጋል፤ ሰው ሁሉ ለሰላም ይሰራል’ ብሎ በጥቅሉ ማየት ያስቸግራል። ባለፉት አመታት ያየነው ልምድም የሚያሳየው እንደዚያ አይደለም” ሲሉም ጠቅላይ ሚኒስትሩ ተደምጠዋል። (ኢትዮጵያ ኢንሳይደር)