ልናገር የፖለቲካ ችግር ፒራሚድ በኢትዮጵያና አዲስ የመውጫ በር

ቀን: November 6, 2024

በሁሴን  አዳል  መሐመድ (ዶ/ር)

ከኅብረተሰቡ  በሚነሱ  የመልካም  አስተዳደር  ጉድለቶች  ማኅበራዊና  ኢኮኖሚያዊ ችግሮች  ላይ የተመሠረተ ጤናማ የፖለቲካ ባህል  ግንባታ  ልምምድ  በአገራችን  ኢትዮጵያ  እስካሁን  የለም፡፡  የፖለቲካ  ችግሮች  ተደርገው  የሚቀርቡት  አጀንዳዎች  ምንጭ  ሕዝብ  ሳይሆን  በብሔረሰብ  ሕዝብ  ስም  የሚነግዱ  የተደራጁ  የጥቂት  ነቄ  የፖለቲካ  ልሂቃን  ቡድናዊ  ፍላጎቶች  ናቸው፡፡  የብሔር  ፖለቲካ  አገራችንን  ቀስ በቀስ  አዳክሞ  ለማፈራረስ  የዘመናት  ህልም  ላላቸው  የውጭ  ኃይሎች  እግር  መትከያና  እጅ  ማስገቢያ  ሆኖ  የተነደፈ  የሥውር  ተልዕኮ  ማስፈጸሚያ  ፖለቲካ  ነው፡፡  የባዕዳን  አጀንዳ  ተሸክመው  ጉዳይ  ማስፈጸም  የማይገዳቸው  ተከፋይ  ዜጎችን  በቀላሉ  ማግኘት  የመቻሉ  ጉዳይ  ለአገራችን  ታሪካዊ  ጠላቶች  የዘመናት  ፍላጎት  መሳካት  አስቻይ  ሁኔታ  ፈጥሮ  ቆይቷል፡፡  በአሁኑ  ጊዜ  አገራችን  ኢትዮጵያ  የምትገኝበት  አሳሳቢ  ሁኔታ  ለዚህ  አስረጂ  ነው፡፡  ዜጎች  እርስ በርስ  በመናበብ  አንድ  የጋራ  አገራዊ  የፖለቲካና ኢኮኖሚ  ማኅበረሰብ  መገንባት  ተስኗቸው  ከአገራችን  ታሪካዊ  ጠላቶች  በየዙሩ  በሚያገኙት  ድጋፍ  ፈርጥመው  በየመንደራቸው  ማሰብ  ከጀመሩ   ውሎ  አድሯል፡፡  የብሔር  ፖለቲካ  የፉክክርና  የመቀናናት  ደረቅ  ፖለቲካ  ነው፡፡  ከእያንዳንዱ  የብሔር  ፖለቲካ  ቡድን  ጀርባ፣  ድርጅት  ከማቋቋም  ጀምሮ  በሁለንተናዊ  ድጋፍ   አጠናክሮ  ቤተ መንግሥት  እስከ ማስገባት  ድረስ  ባለው  ሒደት  የማንኛውም  የውጭ  አገር  መንግሥት   እጅ  እንደነበረና  እንዳለ  አገራቸውን  በሚወዱ  ኢትዮጵያውያን  በኩል  የማይታወቅ  ጉዳይ  አይደለም፡፡  

የፖለቲካ ችግር ፒራሚድ በኢትዮጵያና አዲስ የመውጫ በር | Ethiopian Reporter | ሪፖርተር
የችግሩ ስፋት

በዘመናት  የትውልድ  ቅብብሎሽ  ለአሁኑ  ትውልድ  በውርስ  የተላለፈችውን  ታሪካዊ  አገር  የምሥረታ  ታሪክ  መናድ፣  ለዘመናት  የተገነባ  የጋራ  እሴትና  ባህልን  በማጣጣል  በአዲስ  የፖለቲካ  ትርክት  ለመተካት  መሞከር፣  እርስ በርስ  የተጋመደውን  የኢትዮጵያ  ብሔረሰቦችን  ሕዝብ  የዘመናት  የትስስር  ገመድ  አላልቶ  ሕዝቡን  ለመበታተን  የሚደረግ  ጥረት  በብርቱ  የሚሠራበት  ፕሮጀክት  ነው፡፡  ከአንድነት  ፖለቲካ  ይልቅ  የዚህ  ተቃራኒ  የሆነው  የብሔር  ፖለቲካ  ጉልበት   የፈረጠመበት  ምክንያት  በአገሪቱ  ታሪካዊ  ጠላቶች  የሚደገፍ  ጠንካራ  የፕሮጀክት  ድጋፍ  በመኖሩ  ምክንያት  ለመሆኑ  ምንም  ጥርጥር  የለውም፡፡  ድጋፍ  ሰጪ  አካላትና  ተልዕኮ  ፈጻሚ  ሆድ  አደር  ፖለቲከኞች  በአቋራጭ  የጥቅም  ቀለበት  ተቆራኝተው  መገኘት  የአገሪቱን  የፖለቲካ  ችግር   ውስብስብ  አድርጎታል፡፡  ይሁን  እንጂ  ለእነዚህ  ባዕዳን  አገሮችና  ዕኩያን  ዜጎች  ያልተቀደሰ  ጋብቻ  ጽኑ  መሠረትና  አቀጣጣይ  ነዳጅ  የሆኑ  ሌሎች  በርካታ  ተዛማጅ  ችግሮች  የሉም  ማለት  አይቻልም፡፡   የችግሩ  ፈጣሪዎችና  ተዋናዮች   የመንግሥት  ሥልጣን  የተቆጣጠሩ  ፖለቲከኞችን  ብቻ  ማድረግ  ለአገራችን  የፖለቲካ  ችግር  ዘላቂ  መፍትሔ  አያስገኝም፡፡   ችግሩን  ከሰፊ  ዳራ  ተነስቶ   በወርድና  በቁመት  ማየት  የግድ  ያስፈልጋል፡፡  ችግሩን  በዚህ  ሁኔታ  ማየት  ስንጀምር  የአገራችን  ኢትዮጵያ  የፖለቲካ  ችግር  በፒራሚድ  ምሥለት  የሚገለጽ፣  አስተውሎ  መሥራትን  የሚጠይቅ  ሰፊ  ባለድርሻ   ያለበት  ችግር  ሆኖ  እናገኘዋለን  (ሥዕል 1)፡፡

ሥዕል 1 የኢትዮጵያ ፖለቲካ ችግር ፒራሚድ

ቁልፍ ጉዳዮች

የኢትዮጵያ  ፖለቲካ  መርዝ  መበጥበጫ  ብልቃጥ  ስለሆነው  ስለብሔር  ፖለቲካ አስከፊ  ገጽታዎች  አጭር  ሀተታ  ከፒራሚዱ  በፊት  ማስቀደም  ስለፒራሚዱ  የሚደረገውን  ገለጻ  ቀላል  ያደርገዋል፡፡  የብሔር  ፖለቲካን  አስከፊ  ገጽታዎች  ቅዠት፣  የጦስ  ዶሮ  አስፈላጊነት፣  ሥልታዊ  ጋብቻና  ፍቺ፣  ኋላቀርነት  በሚሉ  ጥቂት  ንዑሳን  ርዕሶች  ለመዳሰስ  ተሞክሯል፡፡  የዚህ  ጽሑፍ  ተደራሲዎች  የብሔር  ፖለቲካ  ወንዝ  ወራጅ  ጎርፍ  ጠራርጎ  ወስዷቸው  የዘረኝነት  ጥልቅ  ባህር  ውስጥ  የሰመጡት  የብሔር  ፖለቲካ  ተጠቃሚዎች  ሳይሆኑ  በብሔር  ፖለቲካ  ትዕይንት  ተደናግረው  ከወንዙ  ዳር  ቆመው  ባህሩ  ውስጥ  የሰመጡትን  እየተመለከቱ  ወንዙ  ውስጥ  እንግባ  ወይስ  አንግባ  እያሉ  ከራሳቸው  ጋር  ለሚሟገቱ፣  እናት  አገራችን  ላይ  የደረሰውን  አስደንጋጭ  አደጋ  በልኩ  ላልተመለከቱ  በተለይም  ለወጣቱ  ትውልድ  ነው፡፡  የራሳቸውን  ፍላጎት  ከአገሪቱ  ታሪካዊ  ጠላቶች  ፍላጎት  ጋር  በጥብቅ   የጥቅም  ቁርኝት  ሰንሰለት  አስተሳስረው  የብሔር  ፖለቲካን  በኑሮ  መተዳደሪያነት  የሚጠቀሙ  አውቆ  አጥፊዎች  ጋር  ከሚታሰብ  ውይይትና  ምክክር  ይልቅ  ወጣቱ  ትውልድ  የብሔር  ፖለቲካን  ገመና  በግልጽ  ተረድቶ  ፖለቲካውን  እንዲጠየፍ  ማድረግ  የተሻለ  ውጤት  ያስገኛል፡፡

ቅዠት

የብሔር  ፖለቲካ  ቀዳሚው  ገጽታ  ቅዠት  ነው፡፡  በመዝገበ  ቃላት  ፍች  ‹‹ብሔር››  ማለት  ‹‹አገር››፣ ‹‹ብሔረሰብ››  ማለት  ‹‹የአገሩ  ሰው››  ማለት  ሲሆን  ፖለቲከኞቹ  ለቃላቱ  ከእውነታው  የራቀ፣  የተዛባ  የቋንቋ ና  የፖለቲካ  ኢኮኖሚ  ጽንሰ ሐሳብ  ፍቺ  ሰጥተው  በሕዝቡ  ህሊና  ውስጥ  በማስረጽ  ተደናግሮ  የማደናገር  የቀን  ቅዠት  ውስጥ  ናቸው፡፡  ቋንቋ  ተናጋሪነትን  የብሔረሰብ  ማንነትና  አባልነት  መነሻ  ወሳኝ  ሁነት  በማድረግ  በዕውቀትና  በእውነት  ላይ  ያልተመሠረተ  የዜጎች  የብሔረሰብ ማንነት  ምደባ  አድርገዋል፡፡  ፖለቲከኞቹ  መሠረት  የለሽ  በሆነ  ሰው ሠራሽ  የነገድ  ምደባ  መሥፈርት  ለሌሎች  ‹‹የብሔረሰብ  ማንነት  ምደባ››  የሚሰጡትና  ለራሳቸውም  የሚቀበሉት  ሌላውን  በማግለል  የአንድ  ፖለቲካ  ቡድን  አባል  መሆን  ሊያስገኝ  የሚችለውን  ማዕድ  ተዝናንተው  ለመቁረስ  እንዲችሉ  ነው፡፡  በሌላው  ብሔረሰብ  መንደር  የተሠራው  ማዕድ  የተሻለ  የእንጀራ  ቁራሽ  ካስገኘ  ‹‹በዴሞክራሲያዊ  ብሔርተኝነት››  ሽፋን  የዚያ  ብሔረሰብ  አባል  ሆነው  ሌላ  ማዕድ  ላይ  ሲቀመጡ  የመሪነት  ሚና  በመጫዎት  የሌላውን  ብሔረሰብ  ጉዳይ  ያለይሉኝታ  ሲፈተፍቱ  ተደጋግሞ  ታይቷል፡፡ ከማርክሲስት ሌኒኒስት  የፖለቲካ ኢኮኖሚ  ጽንሰ ሐሳብ  በመነሳት  በኢትዮጵያ  ተጨባጭ  ሕዝበጽፍ  (Demography)  መረጃ  ላይ  ያልተመሠረተ  የብሔር/ብሔረሰብ  (Nation/Nationalities)  ትርጉም  ሌላው  የማደናገሪያ  ርዕስ  ነው፡፡  ከሶሻሊስት  አገሮች  የፖለቲካ  ሥርዓት  በተጋባ  የቅዠት  በሽታ  በተለያየ  ሥልት ምርት  ወይም  የኢኮኖሚ  ዕድገት  ደረጃ  ላይ  የማይገኙ  የተጋመደ  የኢትዮጵያ  ብሔረሰቦች  ሕዝብን  በዕድገት  ደረጃ  ከፋፍሎ  የሣለ  በውሸት  ላይ  የተመሠረተ  የጨቋኝ/ተጨቋኝ  ትርክት  ሌላኛው  የማደናገሪያ  ቅዠት  ነው፡፡  በዚህ  ቅዠት  ተደናግሮ  ቅራኔ  ውስጥ  በገባ  በድህነት  የቆረቆዘ  ኅብረተሰብ  መካከል  እነሱ  የተመቻቸ  ኑሮ  ለመኖር  የሚያስችላቸውን  ኋላቀር   አገራዊ  የፖለቲካ  ፍልስፍና  የፀና  መሠረት  አስይዘዋል፡፡

ለብሔር ተኮር  ፖለቲካ  መኖር  አስቻይ  ሁኔታ  የፈጠረላቸው  በአገሪቱ  ውስጥ  ብዝኃነት  ወይም  የበርካታ  ብሔረሰቦች  ሕዝብ  መኖር  ሲሆን፣  ይህን  ብዝኃነት  የውበታችንና  ጥንካሬያችን  ምንጭ  በማድረግ  ፈንታ  በብዝኃነት  ውስጥ  ያለውን  ተፈጥሯዊ  ልዩነት  ለወዳጅ/ጠላት  ፍረጃ  በመጠቀም  ብሔረሰብን  ከብሔረሰብ  አጋጭቶ  የፖለቲካ  ትርፍ  ለማግኘት  ሌት  ተቀን  ሠርተዋል፡፡  በአገራችን  የብሔር  ፖለቲካ  አንድ  አስገራሚ  ነገር  ፖለቲካው  ፉክክር  ውስጥ  በገቡ  የጥቂት  ብሔረሰቦች  ቡድኖች  ምህዋር  ዙሪያ  መሽከርከሩ  ነው፡፡  የጥቂት  ብሔረሰቦች  ቡድኖች  በበርካታ  ብሔረሰቦች  ንዑስ  ቡድን  በማቋቋም  በእነዚህ  ተጨማሪ  ቡድኖች  ምርኩዝነት  በሚገኝ  ተጨማሪ  ጉልበት  የተነሱበትን  ዓላማ  ማስፈጸም  መቻላቸውና   የብሔር  ፖለቲካን  የሁሉም  ብሔረሰቦች  ፖለቲካ  አድርገው  በማቅረብ  ሕዝብን  ለማሳመን  መሞከራቸው  የስኬታቸው  ምንጭ  ነው፡፡  የጥቂት  ብሔረሰቦች  ቡድኖች  የሚያጦዙትን  የብሔር  ፖለቲካ  የመላው  ኢትዮጵያ  ብሔረሰቦች  ፖለቲካ  አድርጎ  መሳል  በራሱ  አንዱ  የብሔር  ፖለቲካ  የቀን  ቅዠት  ነው፡፡   ከኢትዮጵያ  አንፃር   (ሦስት በመቶ)  ብሔረሰቦች  ማለትም  ከትግሬ፣ ኦሮሞና አማራ   ሕዝብ  አብራክ  ወጣን  የሚሉ  ጥቂት  ቡድኖች  አድራጊ  ፈጣሪ  የሆኑበት  ፖለቲካ  ተፅዕኖ  ፈጣሪ  የሆነው  ቡድን  ሌሎችን  አደናብሮም  ሆነ  አሳምኖ  ሐሳቡን  በመላው  የኢትዮጵያ  ብሔረሰቦች  ሕዝብ  ላይ  ይጭናል፡፡  የፖለቲካው  መሪ  ሐሳብም  መፍትሔ  በሚሹ  የመልካም  አስተዳደር፣  ማኅበራዊና  ኢኮኖሚያዊ  አሁናዊ  ተጨባጭ  ችግሮች  ፈንታ  ፋይዳ  ቢስ  የጥንት  ዘመን  የአገረ  መንግሥት  ግንባታ  የታሪክ  ቅራኔ  ላይ   ያጠነጥናል፡፡

ሌላው  በጣም  ትልቅ  ቅዠት የማንኛው  ብሔረሰብ  አባል  ስለመሆናቸው  የተጣራ  የዘረመል  ወይም  ተፈጥሯዊ  ወሳኝ  ሁነት  መረጃ  በሌላቸው  ሰዎች  ፖለቲካው  የሚራመድና  በተመሳሳይ  የማንነት  ቀውስ  ውስጥ  የገቡ  ተመሳሳይ  ፍላጎት  ያላቸውን  ሰዎች  የሚያስተናግድ  አድሏዊ  ፖለቲካ  መሆኑ  ነው፡፡  ባለፉት  በርካታ  ሚሊኒየም  ዓመታት  የኢትዮጵ ያ ነገዶች  በኩታ  ገጠም  ሆነ  ተቀላቅሎ  በመኖር  የእርስ በርስ  መስተጋብርና  ውህደት  የፈጠሩ  በመሆናቸው  በእያንዳንዱ  ኢትዮጵያዊ  ደም  ውስጥ  የበርካታ ነገዶች   ዘረ መል  ስለተቀላቀለ  ማንም  ሰው  የእኔ  ነው  የሚለውን  ነገድ  በሚመለከት  የተረጋገጠ  አስረጂ  ማቅረብ  አይችልም፡፡  ለምሳሌ  ያህል  ‹‹ኦሮሞነት  በደም  የሚገኝ  ማንነት  ነው››  ሲል  የከረመ  አንድ  የኦሮሞ  ቀንደኛ  ፖለቲከኛ  በሌላ  ጊዜ  ‹‹ኦሮሞነት  አብሮ  ኖሮ  የኦሮሞ  ባህልን  በመላበስ  የሚገኝ  ማንነት  ነው››  ሲል  ተሰምቷል፡፡  ስለዚህ  የብሔር  ማንነት  የብሔር  ፖለቲከኞች  ለማንም  እንዳሻቸው  የሚለጥፉት  ዕቃ  ላይ እንደሚታሰር  ታግ  ያለ  መለያ  እንጂ  የታወቀ  የዜጎች  ምንነት  አይደለም፡፡

በፖለቲካው  መፍትሔ  ለመሻት  የሚሞክረው  ያልተፈታ  የሕዝብ  መሠረታዊ  የኢኮኖሚና  ማኅበራዊ  ችግር  ሳይሆን  ያልተሟላ  የግልና  የቡድን  ፍላጎትን  ነው፡፡  ‹‹ሁሉን  አማረኝን  ገበያ  አታውጧት››  እንዲሉ  የብሔር  ፖለቲካ  ተጠቃሚዎች  ይበቃናል  ብለው  ለሌላው  ወገን  የሚያስተርፉት  ምንም  ነገር  የለም፡፡  ወደ  ፖለቲካው  ይዘው  በሚገቡት  ባዶ  ሻንጣ  ቁሳዊ  ሀብቱንም፣  ገንዘቡንም፣  የትምህርት  ማስረጃውንም፣  ማዕረጉንም፣  ዕውቅና  ማግኘትንም፣  ሁሉንም  ነገር  በማጓፈፍ  እከሚቀደድ  ድረስ  ሻንጣውን  ይሞላሉ፡፡  ‹‹በሕዝቡ  ተሳትፎ  ትግሉ  የተፈለገውን  ውጤት ሲያስገኝ  እኔም  ከሕዝቡ  ጋር  ያልፍልኛል››  የሚል  አስተሳሰብ  ጭራሽ  የለም፡፡  ይህ  መስገብገብ  በአቋራጭ  መበልፀግ  የሚሉት  በሽታ  ነው፡፡

ፖለቲካው  ደሃ ተኮር  ስላይደለ  ሕዝባዊ  ቅቡልነት  የለውም፡፡ ‹‹ፍየል  ወዲህ  ቅዝምዝም  ወዲያ››  እንዲሉ   ፖለቲከኞቹ  የሚያናፍሷቸው  ጥያዌዎችና  ሕዝቡ  የሚገኝበት  የኑሮና  የአስተሳሰብ  ደረጃ  ፈጽሞ  የማይገናኝ  ነው፡፡  በብሔረሰብ  ቡድን  ተደራጅቶ  በብሔር  ፖለቲካ  መታገል  የሚፈለግበት  ምክንያት  የኢትዮጵያን  ሕዝብ  ማዕከል  በሚያደርግ  የግል  ተነሳሽነት  ሊሳካ  የማይችልን  የግልና  የቡድን  ጥቅም  ዓላማ  በጠባቡ  ገብቶ  በብሔረሰብ  ሕዝብ  ሽፋን  ማሳካት  እንደሚቻል  ስለሚታሰብ  ብቻ  ነው፡፡   አንዳንድ  ፖለቲከኞች  የወገኑትን  ብሔረሰብ   ፓርቲ  በመተው  ፖለቲካ  በቃን  የሚሉት  ወይም  በብሔረሰብ  የፖለቲካ  ፓርቲዎች  መካከል  የሚገለባበጡት  ወይም  ከፍተኛ  የሀብት  ማማ  ላይ  ሲደርሱ  ትግል  በቃን  ብለው  ዘወር  የሚሉት  በፖለቲካው  ላይ  ጽኑ  እምነት  አለመያዛቸውን  የሚያመላክት  ብቻ  ሳይሆን  የብሔር  ፖለቲካ  ግለሰባዊ  ፍላጎትን  ማርካት  ካስቻለ  አንድም  ቀን  ሊውሉበት፣ ሊያድሩበት  ቀርቶ  ከሰዓት  ዕላፊ  በኋላ  ጥቂት  ሊቆዩበት  የማያስፈልግ  ጊዜያዊ  ማረፊያ  ሳሎን  መሆኑን  ቀድመው  ስለተገነዘቡ  ነው፡፡  አማራጭ  የኑሮ  ሥልት  ቢያገኙ  የብሔር  ፖለቲካን  እርግፍ  አድርገው  እንደሚተው፣  ነገር  ግን  ‹‹ጅብ  ከሚበላቸው  ጅብ  በልቶ  መቀደስ››  እንደመረጡ  የሚናገሩ  አንዳንድ  የብሔር  ፖለቲከኞች  የሚናገሩበት  አጋጣሚ  አለ፡፡  ለዚህም  ነው  የብሔር  ፖለቲካ  የሆድ  አደሮች  ፖለቲካ  ነው  እስከሚባል  የተደረሰው፡፡

የጦስ  ዶሮ  አስፈላጊነት

የብሔር  ፖለቲካ  በጥላቻ  ላይ  የተመሠረተ  የሴራና  የእርግማን  ፖለቲካ  ነው፡፡  የብሔር  ፖለቲካ  የጥላቻ  ዓይን  የሚያርፍበትና  ጣት  የሚጠነቆልበት  የጦስ  ዶሮ  የሚሆን  አንድ  ብሔረሰብ  ከአገሪቱ  ብሔረሰቦች  መካከል  የግድ  መፈጠር  አለበት፡፡  በአገራችን  የብሔር  ፖለቲካ  የጥላቻ  ዓይን  ማረፊያ  የተደረገው  የአማራ  ብሔረሰብ  ሕዝብና  የብሔረሰቡ  ተወላጆች   የተባሉ  ዜጎች  ናቸው፡፡  የአማራ  ብሔረሰብ  ተወላጆችን  ከሌሎች  ብሔረሰቦች  ሕዝብ  ለመነጠል  በሚደረግ  ጥረት  የብሔረሰቡ  ሕዝብ  የብሔር  ፖለቲካ  ሰለባ  ተደርጎ  ለአጠቃላይ  የህልውና  ችግር  ተጋለጠ፡፡  ትሕነግ  ደደቢት  በረሃ  እያለ  በ1968 ዓ.ም . ያዘጋጀው  ‹‹የአማራ  ብሔርን  ኅብረተሰባዊ  ዕረፍት  ማሳጣት››  የሚለው  የጫካ  ማኒፌስቶ  የድርጅቱ  ቋሚ  የትግል  መመሪያ  ለአንዳንድ  ሌሎች  ብሔረሰቦች  ቡድኖች  በውርስ  ተላልፎላቸዋል  ተቀብለዋል፡፡  የአማራ  ሕዝብ  ህልውና  ፈተና  የሆነው  የጥላቻ  ፖለቲካ  በከተማ  ተፀንሶ፣  በጫካ ተወልዶና  አድጎ  በመጨረሻም  ቤተ መንግሥት  ገብቶ  ከአማራ  ሕዝብ  ትከሻ  ጭራሽ  አልወረደም፡፡  ለአማራ  ሕዝብ  ዕረፍት  ማጣት  መንስዔው  የአማራን  አንገት  ለማስደፋት  የተነሱ  አማራ ጠል  ቡድኖች  መኖር  ብቻ  ሳይሆን  አንገት  ለሚያስደፉ  ተላላኪና  ተባባሪ  ሆነው  የሚያገለግሉ  የብሔረሰቡ  ተወላጆች  መኖራቸው  ጭምር  ነው፡፡  የአማራ  ሕዝብ  በያለበት  በአገሩ  ላይ  ሠርቶ  የመኖር  መብቱን  የተነጠቀው  ከውስጥና  ከውጭ  ነው  የሚባለው  ለዚህ  ነው፡፡

‹‹የአማራ  ብሔረሰብን  ሕዝብ  ማኅበረሰባዊ  ዕረፍት  ማሳጣት››  የሚለውን  ግልጽ  የጠላትነት  ፖለቲካ  አቋም  ከሚቻለው  በላይ  ተጨማሪ  ዘመን  ማሻገር  ስላልተቻለ  የአማራ  ሕዝብ  ለብሔረሰብ  መብቱ  እንዳይታገል  የሚገታ ለዘብ  ያለ  የአማራ  ሕዝብ  ልጓም  መሥራት  ለፖለቲካው  መሐንዲሶች  ወሳኝ  አዲስ  ተግባር  ሆነ፡፡  በመሆኑም  ከግልጽ  ጠላትነት  ወደ  አስመሳይ  ወዳጅነት  መሸጋገር  ጊዜ  ለመሸመት  እንደሚረዳ  ስለታመነበት  ‹‹አማራ  ዴሞክራሲያዊ  ብሔርተኝነት››  የሚል  የአማራ  ግንዘት  የአማራ  የፖለቲካ  አቅጣጫ  መጠቆሚያ  ኮምፓስ  ተደረገ፡፡  ለዘመናት  በኢትዮጵያ  ብሔርተኝነት  ድባብ  ውስጥ  የኖረው  የአማራ  ሕዝብ  ከሌሎች  ብሔረሰቦች  ሕዝብ  ጋር  እኩል  በብሔረሰብ  ጥላ  ሥር  ለመሰባሰብ  ከራሱ  ጋር  ሲታገል  ጊዜ  እንደሚፈጅበት  ቀድሞውኑ  የታወቀ  ነበር፡፡  ሌሎች  ብሔረሰቦች  የፖለቲካ  ሥልጣን  ባለቤቶች  ሆነው  በራሳቸው  ጉዳይ  ራሳቸው  መወሰን  ሲችሉ  የአማራ  ሕዝብ  ሌሎች  እየወሰኑለት  በጭቆና  ቀንበር  ውስጥ  ማለፍ  ያለበት  ሕዝብ  መደረጉ  ቀጠለ፡፡  በትሕነግ  የተራመደው  ‹‹አማራን  ማኅበረሰባዊ  ዕረፍት   ማሳጣት››  አዋጅና  ‹‹የአማራ  ዴሞክራሲያዊ  ብሔርተኝነት ልጓም››  ከትሕነግ  የቀጥታ  ፖለቲካ  ሚና  መቀዝቀዝ  በኋላ  ‹‹ኦሮ አማራ  ጥምረት››  በሚል  ጭምብል  ታውሮ  እንዲቆይ  ሌላ  ዙር  የፖለቲካ  ሴራ  ተቀየሰ፡፡  ‹‹አማራ  ዴሞክራሲያዊ  ብሔርተኝነት›› ወደ  ኦሮ-አማራ  ጥምረት  ሲሸጋገር  ብአዴኖች  የሌላ  ዙር  ፖለቲካ  ዘመን  ተላላኪዎች  ከመሆን  በስተቀር  በእኩል  የብሔር  ፖለቲካ  ተዋጽኦ  የአማራ  ሕዝብን  እንግልትና  ስቃይ  አላስቀረም፡፡  ጥምረቱ  ኦሕዴድን  በትሕነግ  ምትክ  አነገሠ፣  ብአዴንን  ዳግም  ተላላኪ  አደረገ  እንጂ  ለአማራ  ሕዝብ  ያመጣለት  አንዳችም  ጠቃሚ  ለውጥ   የለም፡፡  የብአዴን  የስም  ለውጥም  ማንነቱን  ሊቀይርለት  ስላልቻለ  ጥረቱ  ‹‹መልከ  ጥፉን  በስም  ይደግፉ››  ሆኖ  ቀረ፡፡  ብአዴን  አዴፓ  ሆኖ  የብልፅግና  አጋር  ከሆነ  በኋላ  አማራ  ምን  ሆነ  ተብሎ  ለሚቀርብ  ጥያቄ  መልሱ  ‹‹ዝናብ  ዘነበ  ወይ  ቢሉት  ሁሉም  በየደጁ  ይየው››  አለ  የሚለው  ይሆናል፡፡

ሥልታዊ  የፖለቲካ  ጋብቻና  ፍቺ

ብሔረሰብ  ፖለቲካ  ፓርቲዎች  አፍአዊ  መቀራረብና  መራራቅ፣  ሥልታዊ  የፖለቲካ  ጋብቻና  ፍች  የብሔር  ፖለቲካ   ገጽታ  ነው፡፡  አስመሳይ  የእህትማማች  ፓርቲዎች  ግንኙነት፣  ውግዘትና  ውዳሴ  ድብቅ  የፖለቲካ  ዓላማን  ለማሳካት  የሚደረግ  የተለመደ  የብሔር  ፖለቲካ  ማጭበርበሪያ  ሥልት  ነው፡፡  ይህ  የፖለቲካ  ቁማር  በውጤቱ  አንዱን  አስገባሪ፣  ሌላውን  ገባሪ፣  አንዱን  ከፊት  ሌላውን  ከኋላ፣  አንዱን  ከላይ  ሌላውን  ከታች  በማድረግ  ይከናወናል፡፡  ትሕነግ  የአማራን  ሕዝብ  ትግል  ‹‹በአማራ  ዴሞክራሲያዊ  ብሔርተኝነት››  ልጓም  በመቀፍደድ  የህልውና  አደጋ  እንዲደርስበት  ያደረገው  የብሔረሰቡ  ሕዝብ  ተወካይ  ነን  የሚሉትን  ብአዴኖች  በመያዝ  ነበር፡፡  በሌላ  ዙር  የመጣው   ‹‹ኦሮ-አማራ  ጥምረት››  በኦሕዴድ  በኩል  የተፈጠረ  የአማራን  ሕዝብ  ትግል  ማቀዝቀዣ  መሣሪያ  እንጂ  ዕውነት  በቅንነትና  በእኩልነት  ላይ  የተመሠረተ  የትብብር  ኅብረት  አልነበረም፡፡

ከብአዴን  ጋር  የተፈጸመው  ‹‹ኦሮ-አማራ  ጥምረት››  የፖለቲካ  ጋብቻ  በሚፈጥረው  ጉልበት  በመታገዝ  በኦሕዴድና በዴኢሕዴግ  ላይ  ግልጽ  ተፅዕኖ  ሲያደርስ  የነበረውን  ትሕነግ  በኦሕዴድና በብአዴን  ጊዜያዊ  ጋብቻ  በመታገዝ  ከቤተ መንግሥት  ለማስወጣት  እንደሆነ  የብአዴን  የፖለቲካ  ቢሮ  ሰዎች  ለመረዳት  ሞተው  መቀበራቸውን  ማወቅ  ነበረባቸው፡፡  ‹‹የወንዝ  ውኃ  የሚወስደው  እያሳሳቀ  ነው››  እንዲሉ  የሙሽራ  አጃቢ  በመሆን  አጭር  ርቀት  አብረው  ከተጓዙ  በኋላ  የወከላቸው  ሕዝብ  ሳያነሳቸው  መጀመርያ  በምደባ  ለውጥ፣  ቀጥሎ  በመሰናበት  ሥልታዊ  ጋብቻና  ፍቺ፣  ከየተወከሉበት  የሕዝብ  ወንበርና  የመንግሥት  ሥልጣን  ተራ  በተራ  ዘወር  ሲደረጉ  ምን  እየተደረገ  እንደሆነ  ያወቁት  ከተደረጉ  በኋላ  ነው፡፡   አንዳንዶቹ  በእጃቸው  የገባውን  ዕድል  አሳልፈው  ሰጥተው  አሁን  እምቡር  እምቡር  የሚሉት  የተቃጠለውን  ቤታቸውን  በርቀት  እየተመለከቱ  ነው፡፡ ትሕነግን  ከጨዋታ  ሜዳ  ውጭ  ለማድረግ  ጥቅም  ላይ  የዋለው  የድርጅቶች  ጥምረት  በማግሥቱ  ከተጣማሪዎቹ  መካከል  የአዴፓ  ሰዎችን  በለውጡ  ጎዳና  ይዞ  መዝለቅ  አላስቻለም፡፡  አርቆ  ማሰብ  የተሳናቸው  የብአዴን  ሰዎች  የተቀየረውን  የድርጅታቸውን  መጠሪያ  (አዴፓ)  እያቆላመጡ  ከመጥራት  ውጭ  ጥምረቱ  የት  ድረስና  እንዴት  እንደሚወስድ  ማወቅ  አልቻሉም  ነበር፡፡  እስከ የት  ድረስ  አብረው  እንደሚዘልቁ  ባያውቁም  ለጊዜው  ትሕነግን  ክዶ  ኦሕዴድ  ጋር  የመጣበቅ  አማራጭ  እንደተከተሉ  ያሳያል፡፡

ኦሕዴድ  ከብአዴን  ሰዎች  ጋር  እውነተኛ  ፍቅር  ውስጥ  አለመግባቱን  እንዲጠራጠሩ  የሥዩም  ጥላሁን  ‹‹አንቺ  ወረተኛ››  ጥዑመ  ዜማ  ለብአዴኖች  ቀድሞ  ሊለቀቅላቸው  ይገባ  ነበር፡፡  የኦሮሞ  ፖለቲከኞች  ብአዴን  ተፅዕኖ  ፈጣሪ  አለመሆኑን  እንዳረጋገጡ  ብዙም  ሳይዘገዩ  ወረተኛ  በሆነው  የብሔር  ፖለቲካ  መንፈስ  እየተመሩ  ከትሕነግ  ፖለቲከኞች  ጋር  መልሶ  ለመቀራረብ  ወደ  መቀሌ  ተጓዙ፡፡  አንዴ  ‹‹ፌዴራሊስቶች››  በሚሉት  ሌላ  ጊዜ  በኦሕዴድ፣  ከትሕነግ  ጋር  መወዳጀት  በአማራ  ሕዝብ  ላይ  ላላቸው  የጋራ  ጉዳይ  ወሳኝ ዕርምጃ  መሆኑን  ለሚያውቁት  የኦሮሞ  ፖለቲከኞች  ‹‹አንገት  የተሠራው  ለምንድነው?››  የሚለውን  ጥያቄ  መመለስ  ግድ  አላላቸውም፡፡  በቋንቋ፣  ባህልና  ሥርዓተ  ትምህርት  መስክ  ኦሕዴድና  ትሕነግ  በትብብር  ለመሥራት  የመግባቢያ  ሰነድ  ለመፈራረም   መቀሌ  መገናኘት  ያስፈለጋቸው  ከአማራ  ይልቅ  የሚያቀራርባቸው  ቋንቋ፣  ባህልና  ሥርዓተ  ትምህርት  ስላለ  አልነበረም፡፡  በአማራ  ሕዝብ  ዙሪያ  ላላቸው  የጋራ  ጉዳይ  በትብብር  ለመሥራት  መቀራረብ  እንዳለባቸው  መተማመናቸውን  ይፋ  ለማድረግ  የዕወቁልን  ማስታወቂያ  ሊሠሩ  እንጂ  ዳሩ  ግን  ኦሮ-ትግሬ  ጋብቻ  ኦሮ-አማራ  ዓይነት  ጋብቻ  ሆኖ  የሚቋጭ  ቀቢፀ  ተስፋ  ነው  የሚሉ  ሰዎች  ድምፅ  ይሰማል፡፡ ከኦሮሞ  ፖለቲከኞችና  አንቂዎቻቸው  በኩል  አልፎ  አልፎ  የሚነገረው   ‹‹የኩሽ  መንግሥት›› ምሥረታ  ፍላጎት   የሥጋታቸው  ምንጭ  ተደርጎ  ይቀርባል፡፡ 

‹‹የኩሽ  መንግሥት›› የሚሉት  የህልም መንግሥት  የሴም  ቋንቋ  ምድብ  የሆኑትን  አማራና  ትግሬ  አግላይ  ነው፡፡  ‹‹የወደዱትን  ሲያጡ  የጠሉትን  ይቀላውጡ››  እንዲሉ  ትግሬ  ለአማራ  ቢቀርብ  እንጂ  አማራን  አልፎ  ለኦሮሞ  ቅርብ  ሊሆን  አይችልም፡፡  የብሔር  ፖለቲካ  ይሉኝታ  ስለሌለው  የጋራ  ዕጣ  ፈንታ  ያላቸው  የአማራና  የትግሬ  የፖለቲካ  ቡድኖች  በዳግም  የፖለቲካ  ጋብቻ  የኦሮሞ  ብሔር  ፖለቲከኞች  የጋራ  ጠላቶች ሆነው  ብቅ  በማለት  የሥዩም  ጥላሁንን  ‹‹አንቺ  ወረተኛ››  ክሊፕ  ለመልቀቅ  የሚፈጅባቸው  ጊዜ  ረዥም  አይደለም፡፡  የብሔር  ፖለቲካ  እስስታዊ  ባህሪ  የብሔረሰብ  ፖለቲከኞች  ግንኙነትና ትብብር  በነበረበት  ፀንቶ  እንዲቆይ  አይፈቅድም፡፡  የፖለቲካው  ትብብርም  በግራ  በቀኝ  ያለውን  ሕዝብ  አያሳትፍም፣ ሊያስገኝ  የሚችለው  ጥቅምም  ለሕዝቡ  ተሻጋሪ  አይደለም፡፡ 

‹ያልተቀደሰ  ጋብቻ››  የሚባለው የብሔር  ፖለቲከኞች  የወረት  ጋብቻ  ተጋቢዎችን  ቀስ  በቀስ  አዳክሞ  ሰይጣናዊ  በሆነ  ፍቺ ያለ ውጤት  መና  ስለሚያስቀር  ፖለቲካው  የዜሮ  ድምር  ፖለቲካ  ነው  በማለት  ራሳቸው  የብሔር  ፖለቲከኞቹ  በመድረክ  ሲናገሩ  ይሰማል፡፡

ኋላቀር ነት

ከብሔርተኝነት  የኋላቀር ነት  ማሳያ  ገጽታዎች  የሃይማኖት  ምርኩዝ  ፈላጊነትና  የተረኝነት  ዝንባሌ  ሊጠቀሱ  ይችላሉ፡፡  የብሔር  ፖለቲካ  ኋላቀርነት  አንዱ  ማሳያ  ራሱን  ችሎ  በእግሩ  የማይቆም  የሃይማኖት  ምርኩዝ  ፈላጊ  ደካማ  ፖለቲካ  መሆኑ  ነው፡፡  ኢትዮጵያ  አገራችን  የቆመችው  በብፁዓን  ፆምና  ጸሎት  ጭምር ነው፡፡  የአገራችን  ታሪክና  መልካም  እሴቶች  የኢትዮጵያ  ነባር  ሃይማኖቶች  አሻራ  አለበት  የሚል  የብዙኃን  ምዕመናን  አስተሳሰብ  የብሔር  ፖለቲካ  እንቅፋት  ሆኖ  ስለተገኘ  ሁለቱን  ነባር  ሃይማኖቶች  እርስ በርስ  ማጋጨት  በተለይም  የኢትዮጵያ  ኦርቶዶክስ  ቤተ ክርስቲያንን  የጥቃት  ዒላማ  ማድረግ  ቸል  የማይባል  የብሔር  ፖለቲካ  ተግባር  ሆኗል፡፡  በራሱ  እግር  የማይቆም  ፖለቲካ  ለመቆም  ሲንደፋደፍ  ሌላውን  ታክኮ  ይጥላል፡፡  በአካባቢ  የሚገኝ  ዕቃም  ይደፋል  የሚባለው  ለዚህ  ነው፡፡   ያደፈ  የጎደፈ፣  ኋላቀር   የብሔር  ፖለቲካ  የረዥም  ዘመን  ታሪክና  የዳበረ  ባህልና  ሃይማኖት  ላላት  ኢትዮጵያ   አይመጥንም፡፡  ለፖለቲካው  የሚመቹ  መጤ  ሃይማኖቶች  እግር  እንዲተክሉ  የነባር  ሃይማኖቶችን  እግር  መንቀል  ኋላቀርነት  ነው፡፡  ፖለቲካና  ሃይማኖት  መለያየት  ስላለባቸው  በሕገ መንግሥቱ  ላይ  በተጠቀሰው  መሠረት  አንዱ  በሌላው  ጣልቃ  አይገባም፡፡

የተረኝነት  ዝንባሌ  የሚገለጸው  የታሪክ  ተጠቃሚ  ነበረ  የሚባል  ብሔረሰብ  መኖርን  በመጥቀስ  እኛ  የታሪክ  ተጎጂ  ብሔረሰብ  ትውልድ  አባላት  ዛሬ  በተራችን  መጠቀም  አለብን  የሚል  አስተሳሰብ  ሲንፀባረቅ  ነው፡፡  ‹‹የታሪክ  ተጠቃሚና  የታሪክ  ተጎጂ  ትውልድ›› ትርክት  ‹‹ላም  ባልዋለበት  ኩበት  ለቀማ››  ዓይነት  ትርክት  ሲሆን፣  የእነዚያ  የታሪክ  ተጎጂ  ትውልድ  ወራሾች  ነን  የሚል  ድርቅና  የፖለቲካው  ኋላቀር ነት  ማሳያ  ነው፡፡  አሁን  ያለው  ትውልድ  የተወለደበትን  ዘር  መርጦ  እንዳልተወለደ  ሁሉ  ያለፈ  ታሪክን  እየመረጡ  መጥፎው  ታሪክ  ለእነሱ፣  መልካሙ  ታሪክ  ለእኛ  እያሉ  ታሪክን  እንደ  ሱቅ  ሸቀጣ ሸቀጥ  መከፋፈል  አይቻልም፡፡  ታሪኩን  ከአገሩ  ጋር  ካለፈው  ትውልድ  በጋራ  እንደተረከበው  በነበረው  ላይ  የበኩሉን  አበርክቶ  አገሪቱን  ከተጨማሪ  ታሪክ  ጋር  ለመጪው  ትውልድ  በጋራ  ያስረክባል፡፡  ማን  የታሪክ  ዕዳ  ከፋይ  ማን  ተከፋይ  መሆኑ  በውል  ሳይታወቅ  ሙት  ወቃሽ  ሆኖ  መኖር  አሁን  ያለውን  ትውልድ  በተበዳይነትና  ታናሽነት  ስሜት  ውስጥ  ሙት  እየወቀሰ  በድባጤ እንዲኖር  ማስገደድ  ተገቢ  አይደለም፡፡  ለቡድን  ጥቅም   ሲባል  ይህን  ኋላቀር  አስተሳሰብ  ለትውልድ  እያሸጋገሩ  ዘለዓለም  በቂም  በቀል  የሚፈላለግ፣  እርስ በርስ  የሚፋጅ  ትውልድ  መፍጠር  የታሪክ  ተወቃሽ  ያደርጋል፡፡  የትግሬና  ኦሮሞ  ብሔርተኞች  ከአማራ  ብሔርተኞች  ጋር  ያላቸው  አንዱ  የሐሳብ  ልዩነት  እዚህ  ላይ  የተመሠረተ  ‹‹የሱሪ  በአንገት  አውጡ››  ጥያቄ   ነው፡፡  ሱሪ  በእግር  በኩል  እንጂ  በአንገንት  በኩል  ሊወጣ  አይችልም፡፡  የአሁኑ  ወቅት  የአማራ  ትውልድ  ለብቻው  ሊከፍለው  የሚገባ  የታሪክ  ዕዳ  የለበትም፡፡  አሁን  ያለው  የአማራ  ትውልድ  ሕዝብ  እንደ  ሌሎች  ብሔረሰቦች  ትውልድ  ሕዝብ  አገሪቱ  የነበረባትን  ዕዳ  ያለ ብሔረሰብ  ልዩነት  በደም  በአጥንታቸው  በጋራ  የከፈሉ  ኢትዮጵያውያን  ትውልድ  ነው፡፡  ከሌሎች  ብሔረሰብ  አባላት  ትውልድ  ጋር  የተረከባት  የጋራ  አገር  ባለቤት  እንጂ  የተለየ  ዕዳ  ባለቤት  አይደለም፡፡  

መንግሥትን  በየተራ  ተቆጣጥሮ  ቀዳሚ  ተጠቃሚ  የመሆን  የቡድን  ዝንባሌ  የአገራችን  የፖለቲካ  አደጋ  ከሆነ  ቆየ፡፡  ይህም  አደጋ  የብሔር  ፖለቲካው  ውጤት  ነው፡፡  ብሔርተኝነት  በተራ  ለቡድን  አባላት  ጥቅም  በማከፋፈል  ብቻ  አይጠናቀቅም፡፡  ብሔርተኝነት  በተራ  የሚያስለቅስ፣  በተራ  የሚያወድስ  የማይታመን  ሙልጭልጭ  ፖለቲካ  ነው፡፡  ፖለቲካው  ጥቅም  በተራ  ያከፋፍላል  ሲባል  ቡድኑ  ከመላው  ኢትዮጵያ  ሕዝብ  ሀብት  ወስዶ  እወክለዋለሁ  ለሚለው  የብሔረሰብ  ሕዝብ  ያድላል  ማለት  አይደለም፡፡  በብሔረሰቡ  ስም  ለመነገድ  የቃልኪዳን  ሰነድ  ለተፈራረሙ  የቡድኑ  አባላት  በአቋራጭ  የመበልፀጊያ  መዋቅር  ሆኖ  ያገለግላል  ማለት  እንደሆነ  በግልጽ  መታወቅ  አለበት፡፡  በመንግሥት  መዋቅር  ላይ  በመመደብም  ሆነ  ከመዋቅር  ውጭ  ያሉ  የጥቅም  ግንኑነቶችን  በማስተሳሰር  ለቡድን  ፖለቲካው  ዘርፈ ብዙ  ተዋናዮች  የጥቅም  ማስገሪያና  ማከፋፈያ  መረብ  ይዘረጋል  ለማለት  ነው፡፡  የቡድኑ  ሠራዊት  በያዘው  የመዋቅር   ከፍታና  ጥራት  ልክ  የሚያካብተው  ጥቅም  ብቻ  ሳይሆን  በበኩሉ  ለሌላው  ፈሰስ  በማድረግ  የሚከፍለው  ወሮታ  ጭምር  አለበት፡፡  በዚህ  የተነሳ  የብሔር  ፖለቲካ  የመንግሥት  መመሪያ  በሆነበት  አገር  አገሪቱ  የምታፈራው  ሀብትና  ማንኛውም  መልካም  ዕድል  በፍትኃዊነትና  እኩልነት  ለሁሉም  ዜጎች  አይዳረስም፡፡  የዕድል  ባለቤት  ወይም  ተጠቃሚ  ለመሆን  የብሔር  ፖለቲካ  ፓርቲ  አባል  ወይም  ደጋፊ  መሆን  እንጂ  የዕውቀትና  ችሎታ  ባለቤት  መሆንን  አይጠይቅም፡፡  በሠለጠነ  ኅብረተሰብ  ውስጥ  የዕድል  ባለቤት  ለመሆን  የሚጠይቀው  መሥፈርት  ሰው  መሆንና  የችሎታ  ባለቤት  መሆንን  ብቻ  ነው፡፡  ዜጎችን  በዚህ  ሁኔታ  አንዱን  ተመጋቢ  ሌላውን  የበይ  ተመልካች  በማድረግ  ፖለቲካው  ኋላቀር  ፖለቲካ  መሆኑን  ያለ  በቂ  ምስክር  በራሱ  ያረጋጋጣል፡፡ የእርሱ  ብሔረሰብ  ገዥ  መደብ  እስከሚፈጠር ድረስ  የሌላ  ብሔረሰብ  አባል  የእኩል  ተጠቃሚነት  ዕድል  የመነመነ፣  የሌላ  ዙር  ተስፈኛ  በመሆን  በምሬት  ለመኖር  ይገደዳል፡፡

የብሔር  ፖለቲካ  የሥልጣን  መሣሪያ  በሆነበት  የባለብዙ  ብሔረሰብ  አገር  ለመሥራትም  ሆነ  ለመኖር  አስቸጋሪ  የሚሆነው  ለተራው  ዜጋ  ብቻ  ሳይሆን  ለፖለቲካ  መሪው  ጭምር  ነው፡፡  ፖለቲካው  በሚያስከትለው  የከፋና  የተስፋፋ  የኅብረተሰብ  ብሶት  የተነሳ  ፖለቲካውን  የሚጠሉ  ዜጎች  ጣት  ቀድሞ  የሚጠነቆለው  የሥርዓቱ  ቁንጮ  በሆነው  የአገር  መሪውና  በወጣበት  የብሔር  ድርጅት  ላይ  ነው፡፡  በብሔር  ፖለቲካ  ባህሪ  የተነሳ  በፖሊት  ቢሮው  ውስጥ  ተፅዕኖ  ፈጣሪው  ሰው  ‹‹ሁሉ  በእጁ  ሁሉ  በደጁ››  በመሆኑ  በዚያው  ልክ  በአገሪቱ  ውስጥ  ለሚደርሰው  ችግር  ሁሉ  ቀዳሚ  ተጠያቂ  ሆኖ  ይጠቀሳል፡፡  መሪው  ፖለቲካው  ባስከተለው  ጥፋትና  በደረሱ  ጉዳቶች  ሁሉ  ከመጠየቅ  በስተቀር  በተከናወኑ  መልካም  ሥራዎች  በአንዳቸውም  አይመሰገንም፡፡  ሊመሰገን  ቢችል  እንኳ  የጥቅም  ተጋሪ  ተረኛ  ገዥ  ብሔረሰብ  ነው  ተብሎ  በሚታወቀው  የመሪው  የብሔረሰብ  አባላት  መካከል  በጥቂት  ሰዎች  ብቻ  ይሆናል፡፡  የብሔር  ፖለቲካ  ሥርዓት፣  መሪ  በፈጸመው  ጥፋት  መጠየቅ  ያለበትን  ያህል  ባከናወነው  መልካም  ሥራ  መጠን  የማይመሰገንበት  ነውረኛ  የፖለቲካ  ሥርዓት  መሆኑ  የፖለቲካው  ኋላቀር ነት  ተጨማሪ  ማሳያ  ተደርጎ  ይታያል፡፡  የብሔር  ፖለቲካ  መሪ  በሥልጣን  ላይ  እስካለ  ድረስ  ብቻ  የሚወደስ፣  ለአከናወነው  መልካም  ተግባር  ምሥጋና  በነፃነት  የማይቸረው  እየተፈራና  እየታማ  ለጊዜው  የሚኖር ፣  የሞተ  ዕለት  ብቻ  ተለቅሶለት  በማግሥቱ  የሚረሳ፣  ያስቀመጠው  አሻራ  የሚደመሰስበት  ያልታደለ  መሪ  ነው፡፡  የቀድሞው  ጠቅላይ  ሚኒስትር  መለስ  ዜናዊን  ያጋጠመው  ይህ  ነው፡፡  ትንሽ  ገርገጭ  ሲል  ለጠላት  አሳልፎ  የሚሰጠው  እንጂ  ከጎኑ  የሚቆምለት  ግብረበላ  የለውም፡፡  ከዚህም  ውጭ   ዓለም  የብሔር  ፖለቲካን  እየነቀፈ  ባለበት  የሠለጠነ  ዘመን  የብሔር  ፖለቲካ  ሥርዓት  አራማጅ  አገር  መሪ  መሆን  መሪውን  የሚያስንቅ  እንጂ  የሚያስከብር  የፖለቲካ  ሥርዓት  አይደለም፡፡

የፖለቲካ  ችግር  ፒራሚድ

ፒራሚድ  ሰፊ  ታች  መደብ ና  ሾጣጣ  አናት  ያለው  ባለሦስት  ጎን  ሥዕል  ነው፡፡  የፒራሚድን  ቅርፅ  ተጠቅመን   የአገራችንን  የፖለቲካ  ችግር  ለመተንተን  ስንነሳ  የፒራሚዱ  ወርድ   የችግሩን  ስፋት፣  ቁመቱ  የችግሩን  ጥልቀት  እንደሚወክል  በማሰብ  ነው፡፡  ለፒራሚዱ  ታች  መደብ  ቀረብ  ባሉ  መደቦች  ላይ  የተቀመጡ  ችግሮች  ስፋት  እንጂ  ጥልቀት  የላቸውም፡፡  በተቃራኒው  ወደ  ፒራሚዱ  አናት  በተጠጉ  መደቦች  ላይ  የተቀመጡ  ችግሮች  በአነስተኛ  ስፋት  ከፒራሚዱ  ታች  መደብ  የተለያየ  ርቀት  ላይ  ስለሚቀመጡ  ጥልቀታቸው  ይለያያል፡፡  ከስፋት  ይልቅ  ጥልቀት  ግዙፍ  አደጋን  ይጋብዛል፡፡  የዚህን  እንደምታ  ለመረዳት  በሰፊ  መልካ  ይፈስ  የነበረን  የወንዝ  ወራጅ  ውኃ ወደ  ጥልቅ  ጉድጓድ  መርቶ  በማስገባት  ገብቶ  መዋኘት  ወይስ  በሰፊው  የወንዙ  ወራጅ  ውኃ  መልካ  መሻገር፣  የትኛው  አደጋ  ከባድ  ወይስ  ቀላል  እንደሆነ  እናሰላስል፡፡  ጥልቅ  የጉድጓድ  ውኃ  ከወራጅ  ውኃ ይልቅ  አደገኛ  መሆኑ  ግልጽ  ነው፡፡  ይህን  በሌላ  ምስለት  ለማየት  በዘአካላት  የምግብ  ሰንሰለት  የላይኛው  የፒራሚዱ  አናት  መደብ  ሥጋ  በል  እንስሳት  አደገኛነት  በተዋረድ  ከታች  ከሚቀመጡት  በደረጃ  ይለያያል፡፡  የላይኛው  አናት  መደብ  ሥጋ  በሎች  እጅግ  አደገኞች  ናቸው፡፡   የኢትዮጵያ  የፖለቲካ  ችግር  በፒራሚድ  ምስለት  ሲታይ  የላይኛው  መደብ  ችግሮች  በጥቂት  ኃይሎች  ቢፈጠሩም   በቀላሉ  የማይፈቱ  በጣም  አደገኛ  ችግሮች  ሲሆኑ  የታችኛው  መደብ  ችግሮች  ግን  የላይኛው  መደብ  ችግሮች  ሲፈቱ  በቀላሉ  የሚፈቱ  ጥልቀት  የሌላቸው  ችግሮች  ናቸው፡፡  አደገኞቹ  የአናት  መደብ  ችግሮች  ሳይፈቱ  በዘላቂነት  ሊፈታ  የሚችል  የታች  መደብ  ችግር  የለም፡፡  አገሪቱ  ያጋጠማትን  ውስብስብ  የፖለቲካ  ችግር  ለመፍታት  የችግሩን  አከርካሪ  እየለዩ  በቅደም  ተከተል  መፍትሔ  ለመሻት  ሊደረግ  የሚችል  የጋራ  ርብርብ  ከብሔር  ፖለቲካ  ችግር  የመውጫ  አዲስ  በር  ተደርጎ  ሊወሰድ  ይችላል፡፡  ይህ  የመውጫ  በር  ለአገራችን  ፖለቲካ  ብልሽት  አስተዋጽኦ  ያደረጉ  አካላት  ሁሉ  የሚያልፉበት  ክፍት  በር  ነው፡፡  በዚህ  በር  ሁሉም  ዜጋ  እንዲያልፍ  ማድረግ  ከፍተኛ  የፖለቲካ  ቁርጠኝነት  ይጠይቃል፡፡  የአናት  መደብ  ችግሮች  ከባድ  ስለሆኑ  ከአናት  መደብ  የሚጀምር  ትግል  ለታች  መደብ  ችግሮች  መፍቻ  አስቻይ  ሁኔታ  ሊፈጥር  ይችላል፡፡

ሲጠቃለል  ዓለምን  ጉድ  ያሰኘው  ሥሩን  በአገረ  ኢትጵያ  በጥልቀት  የሰደደውን  ኋላቀር   የብሔር  ፖለቲካ  ሥሩን  ነቅሎ  መጣል  አገር  የመታደግ  ብቸኛ  አማራጭ  ይመስላል፡፡  ይህ  ካልሆነ  በብሔረሰብ  ፖለቲካ  ነጋዴዎች  ተፅዕኖ  የተነሳ  ዜጎች  በሰውነታቸው  ታውቀውና  የዜግነት  ክብር  አግኝተው  መኖር  ፍፁም  አልቻሉም፡፡  የብሔር  ፖለቲካ  ላይ  መዝመት  የብሔረሰቦችን  መብት  መዳፈር  ነው  በማለት  የሚሞግቱ  የብሔር  ፖለቲካ  ስኳር  የቃሙ  የየብሔረሰቡ  ቡድኖች  እንዳሉ  ግልጽ  ነው፡፡  ይሁን  እንጂ  የአገራችን  ሕዝብ  የሠለጠነ  ፖለቲካ  መንፈስ  ርቆት  ከዓለም  የተለየ  በሆነ  ኋላቀር   የብሔር  ፖለቲካ  ጭስ  ሁልጊዜ  ታፍኖ  መኖርን  ሊመርጥ  አይገባም፡፡   ኢትዮጵያ  በክብር  ለዘለዓለም  ትኑር!

ከአዘጋጁ፡- ጸሐፊው የወሎ ዩኒቨርሲቲ መምህር ሲሆኑ፣ ጽሑፉ የእሳቸውን አመለካከት ብቻ የሚያንፀባርቅ መሆኑን እየገለጽን በኢሜይል አድራሻቸው adalhusm@gmail.com ማግኘት ይቻላል፡፡