ሊነጋጋ ሲል እስራኤል በቤይሩት በፈጸመችው ጥቃት የተነሳ ጭስ ሲወጣ እታያል
የምስሉ መግለጫ,ሊነጋጋ ሲል እስራኤል በቤይሩት በፈጸመችው ጥቃት የተነሳ ጭስ ሲወጣ እታያል

ከ 4 ሰአት በፊት

እስራኤል በማዕከላዊ ቤይሩት ላይ ከፍተኛ የአየር ድብደባ መፈጸሟን እና በርካታ ሰዎች መሞታቸውን የሊባኖስ መገናኛ ብዙኃን ገለፁ።

በዋና ከተማዋ ባስታ የሚገኝ ባለ ስምንት ፎቅ የመኖሪያ ሕንጻ በአምስት ሚሳኤሎች ተመትቶ ሙሉ በሙሉ መውደሙን የሊባኖስ ብሄራዊ ዜና አገልግሎት ዘግቧል።

የሄዝቦላህ አል ማናር ሚዲያ በበኩሉ የሊባኖስን ጤና ጥበቃ ሚኒስቴር ጠቅሶ እንደዘገበው በጥቃቱ አራት ሰዎች ሲገደሉ 23 ቆስለዋል።

የሕንፃውን ፍርስራሽ የሚያሳዩ ቪዲዮዎች መውጣት ጀምረዋል።

የእስራኤል ጦር ሊነጋጋ ሲል በፈጸመው ጥቃት ላይ እስካሁን ድረስ አስተያየት አልሰጠም።

የእስራኤል መከላከያ ሰራዊት በመስከረም ወር ላይ በሄዝቦላህ ላይ ከፍተኛ ጥቃት መሰንዘር የጀመረ ሲሆን፣ በርካታ የአየር ድብደባዎችን በመፈጸም ወታደሮቹን ወደ ደቡብ ሊባኖስ ልኳል።

ባለፈው ዓመት መስከረም መጨረሻ ሐማስ በደቡብ እስራኤል ላይ ጥቃት ከፈጸመ በኋላ፣ በኢራን የሚደገፈው ሔዝቦላህ አጋርነቱን ለማሳየት ተደጋጋሚ ሮኬቶችን ወደ እስራኤል አስወንጭፏል።

እስራኤል ከሔዝቦላህ ጋር በምታደርገው ጦርነት ካበቃ በኋላ በቡድኑ ጥቃት ምክንያት በሰሜን እስራኤል ይኖሩ የነበሩ እና የተፈናቀሉ ወደ 60,000 የሚጠጉ ነዋሪዎችን ለመመለስ አልማለች።

በሊባኖስ በተነሳው ግጭት ከ3,500 በላይ ሰዎች መሞታቸውን እና ከአንድ ሚሊዮን በላይ የሚሆኑትን ከቤት ንብረታቸው መፈናቀላቸውን የአገሪቱ ባለስልጣናት ተናግረዋል።

በዚህ ሳምንት መጀመሪያ ላይ አንድ የአሜሪካ አሸማጋይ ቡድን የተኩስ አቁም ስምምነትን ለማስፈን እስራኤል እና ሊባኖስን ጎብኝቷል።

ወደ ስፍራው ያቀኑት አሜሪካዊው ዲፕሎማት፣ አሞስ ሆቼስቴይን፣ አንዳንድ መሻሻሎች መኖራቸውን ቢገልፁም ነገር ግን ዝርዝር አስተያየት ከመስጠት ተቆጥበቀዋል።